Wednesday, October 16, 2019

ከዓለመ መጻሕፍት


ሃይማኖተ አበው ቀደምት

“ሃይማኖተ አበው ቀደምት” የተሰኘውና በቁም ጽሑፍ ተዘጋጅቶ የተባዛው መጽሐፍ፣ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ (ኪ.ወ.ክ.) ጽፈውት ለአቶ ደስታ ተክለ ወልድ በዐደራ የሰጡትና በዶ/ር ብርሃኑ አበበ አማካይነት ምዕራብ ጀርመን ፍራንክፈርት በሚገኘው በፍሬቤንዩስ ድርጅት የታተመ መኾኑን በመጽሐፉ ላይ ደስታ ተክለ ወልድ የሰጡት መግለጫ ያስረዳል። መጽሐፉ ምንም እንኳ በቤተ ክህነት ዐማርኛ በመምህራን ቋንቋ የተጻፈ መኾኑን ስለሚገልጥ፣ አንዳንድ ታሪኮችና ጸሎቶችም በግእዝ በመቅረባቸው በቀላሉ ለመረዳት አስቸጋሪ ቢኾንም፣ ከ15 የሚበልጥ ብዙ ዐይነት ምዕላድ በማየትና በመመልከት፣ በማስተዋልና በመመርመር፣ በማነጻጸርም የተዘጋጀ በመኾኑ ከፍ ያለ ግምት የሚሰጠው ሥራ ነው። 

በውስጡም የሦስቱን ማለትም የተዋሕዶን፣ የካራንና የቅባትን ባህላተ ትምህርት ምንነት ይዟል። በዘመናቸው የትምህርት ሕጸጽና የሃይማኖት ጕድለት፣ መከራና ስደት፣ ጠብና ክርክር ከዚሁ ጋር ተያይዞ በባህለ ሃይማኖት ልዩነት ምክንያት ምላስና ዐንገት እስከ መቍረጥ የደረሰ አሳዛኝ ቅጣት የፈጸሙ ነገሥታትና የኢትዮጵያ ግብጻውያን ጳጳሳት ታሪክም የተካተተበት መኾኑን መጽሐፉ ይገልጣል።