Thursday, December 31, 2015

ጮራ መጽሔትን ያንብቡ

ጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ቍጥር 47 ለንባብ በቃ

                  
                         በዚህ ዕትም፦ 

  • ዕቅበተ እምነት በተሰኘው ዐምድ ለ"መድሎተ ጽድቅ" ክፍል ፩ ምላሽ ይሰጣል፡፡  ምላሹ በ www.chorra.net ቀርቦ የነበረው ተሻሽሎና ዳብሮ ቀርቧል፡፡
  • በ "የዘመን ምስክር" ዐምድ የሠራዊተ ክርስቶስ ማኅበርን ታሪክና ለእናት ቤተ ክርስቲያን ያበረከቱትን በጎ አስተዋፅኦ በማውሳት በ "መድሎተ ጽድቅ" እና በሌሎችም ቡድኖች ስለ እነርሱ እየቀረበ ያለውን የተሳሳተ መረጃ ከእውነታው ጋር በማነጻጸር አቅርቧል፡፡ 
  • አለቃ ነቅዐ ጥበብ በሥዕል ዙሪያ ለተነሣ የሁለት ሰዎች ክርክር ምላሽ ይሰጣሉ፡፡
  • በፍካሬ መጻሕፍት ዐምድ በ2ጢሞ. 3፥15-17 ለተጻፈውና ብዙ ጊዜ ስለ አዋልድ መጻሕፍት እንደ ተነገረ ተደርጎ ለሚጠቀሰው ክፍል ዐውዳዊ ፍቺ ይሰጣል፡፡ 
  • "ታላላቅ መንፈሳውያን ቃላት" የተሰኘው ዐምድም ስለ ተሰፋ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መልእክት ያቀርባል፡፡

                               
መጽሔቱን በየመንፈሳውያን መጻሕፍት መደብሮች ያገኙታል።

Tuesday, November 10, 2015

ከተማረ አይሳደብም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ የተማረ ሰው ይወዱ ነበር። ስለሆነም በርካታ የቤተ ክርስቲያን ልጆች ለክፍተኛ ትምህርት ወደ ውጪ አገር እየሄዱ እንዲማሩ አድርገዋል። አንድ ጊዜ ተማሪዎች የነፃ ትምህርት ዕድል አግኝተው ወደ ውጪ ሲላኩ እሳቸውን የማይወድ፣ እየዞረ ስማቸውን የሚያጠፋና የሚሳደብ አንድ ተማሪም ዕድሉን አግኝቶ ወደ ውጪ አገር ለመሄድ ተፍ ተፍ ይላል። ይህ ተማሪ ለአቡነ ቴዎፍሎስ በጎ ነገር የማያስብ መሆኑን የሚያውቁ ተቆርቋሪ ሰዎች ይቀርቧቸውና የተማሪውን ስም እየጠቀሱ፡-
“እንዴት እሱን ወደ ውጪ አገር ልከው ያስተምሩታል?” ይሏቸዋል።
“እኮ እንዴት ለምንድን ነው የማይሄደው?” በማለት ይጠይቃሉ።
“እርሱ እኮ ለእርስዎ የማይተኛ እየዞረ ስምዎን የሚያጠፋ፣ የሚሳደብ ነው” ይሏቸዋል።
“የሚሳደበው እኮ ስላልተማረ ነው፡፡ ይሂድና ይማር፤ ከተማረ አይሳደብም” አሉ ይባላል።

በጮራ ቊጥር 41 ላይ የቀረበ

Monday, November 2, 2015

ጥያቄዎችና መልሶቻቸው

በዚህ ዓምድ ለአንባብያን ጥያቄዎች ምላሾች ይሰጣሉ
ጥያቄ፡- ከቀሲስ ወልዱ አስተርአየ
1ኛ. ጮራዎች ሐመር የተባለው የማኅበረ ቅዱሳን ልሳን የሆነው መጽሔት በጥርና በየካቲት 2003 ዓ.ም. ዕትሞቹ ላይ፥ “ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅና የተሐድሶዎች ቅሰጣ” በሚል ርእስ ተከታታይ ጽሑፎችን አስነብቧል። በጽሑፎቹም እናንተ የዮሐንስ አፈ ወርቅን ትምህርት መጥቀሳችሁን ኰንኖ፥ እናንተና እርሱ በትምህርት አለመመሳሰላችሁን፥ እርሱን አባታችን እያላችሁ የምትጠቅሱትም ለማደናገር እንጂ በትክክል ልጆቹ አለመሆናችሁን በስፋት ዐትቷል። ለዚህም ያሳይልኛል ያለውን ማሰረጃ ከድርሳኑ ጠቅሶ ትንታኔ ሰጥቷል። በዚህ ጕዳይ ላይ ምን ምላሽ አላችሁ?
2ኛ. ይኸው ማኅበር “የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላይ” በሚል ርእስ ባሳተመው መጽሐፍ ገጽ 67 ላይ ታላቁንና በብዙ ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት ዘንድ አንቱ የተባሉትን ስመ ጥር ሊቅ አለቃ መሠረት ስብሐት ለአብን “አንተ” እያለ በማንኳሰስ ጽፏል። በዚህ ላይ አንድ ነገር ብትሉ መልካም ነው። 

1ኛ መልስ፡- በመምህርት ሲያዴ
በቅድሚያ ቀሲስ ወልዱን ስለ ጥያቄዎ ከልብ እናመሰግናለን። እርስዎ የጠቀሷቸውን መጽሔቶች ተመልክተናቸዋል። ከጥንት ጀምሮ ሐሰተኞች እውነተኞች ነን በሚል፥ የእውነተኞችን ጩኸት እየቀሙ እውነተኞችን ሐሰተኞች ሲሉና ሲያሰኙ ኖረዋል፤ ዛሬም ይኸው አካሄድ እንደ ቀጠለ ነው። 

Sunday, October 25, 2015

" ... የናቁሽም ሁሉ ወደ እግርሽ ጫማ ይሰግዳሉ፤ ..." (ኢሳ. 60፥14)

“ወይመጽኡ ኀቤኪ እንዘ ይፈርሑ ወያመጽኡ አምኀ ደቂቆሙ እልኩ እለ አምዕዑኪ ወይሰግዱ ቅድመ መከየደ እግርኪ ወትሰመዪ ሀገረ እግዚአብሔር ቅዱሰ እስራኤል ጽዮን - የአስጨናቂዎችሽም ልጆች አንገታቸውን ደፍተው ወደ አንቺ ይመጣሉ፥ የናቁሽም ሁሉ ወደ እግርሽ ጫማ ይሰግዳሉ፤ የእግዚአብሔርም ከተማ፥ የእስራኤል ቅዱስ የሆንሽ ጽዮን ይሉሻል” (ኢሳ. 60፥14)።?
ውሸት ሲደጋገም እውነት ይሆናል የሚል ፍልስፍና ያላቸው ወገኖች አሉ። እንዲህ ለማለት ያበቃቸው በተደጋጋሚ የሚያቀርቡትን ውሸት፥ ሰዎች እውነት ነው ብለው የተቀበሏቸው ስለ መሰላቸው ነው።  ውሸት፥ ውሸት ነው፤ እውነት ደግሞ እውነት ነው። ዐሥር ወንፊት ቢደራረብ አንድ ብልቃጥ ውሃ መያዝ እንደማይችል ሁሉ፥ ውሸት የቱንም ያህል የእውነት ጠብታ ቢጨመርበት ድምር ውጤቱ ውሸት ነው ውሸት በምንም ተኣምር ወደ እውነትነት የሚለወጥበት ዕድል ከቶ የለም፤ አለ ከተባለ ግን እውነትን አለማወቅ፣ እውነትን ማራከስና ዋጋ ማሳጣት ይሆናል። ስለዚህ ውሸት ሲደጋግም እውነት ይመስላል እንጂ እውነት ሊሆን በፍጹም አይችልም።
ኢሳ. 60፥14 ስለ ማን ይናገራል?
ስድሳ ስድስት ምዕራፎች ያሉት ትንቢተ ኢሳይያስ በሦስት ዐበይት ክፍሎች ሊከፈል እንደሚችል የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ይናገራል (1972፣ ገጽ 149)። የመጀመሪያው ክፍል ከምዕራፍ 1-39 ድረስ ያለው ሲሆን፥ ነቢዩ ኢሳይያስ በነበረበት ዘመን የተከናወኑትን ድርጊቶች መሠረት በማድረግ የተጻፈ ነው። ሁለተኛው ክፍል ደግሞ፥ ከምዕራፍ 40-55 ድረስ ያለውና ከኢሳይያስ ዘመን በኋላ ስለ ተፈጸመው ስለ ባቢሎን ምርኮ የተነገረ ትንቢት ነው። የመጨረሻው ክፍልም ከምዕራፍ 55-66 ደግሞ ወደ ፊት ማለትም ከባቢሎን ምርኮ ፍጻሜ በኋላ ስለሚሆነው የጽዮን ክብር ይናገራል። በመነሻው ላይ የተጠቀሰው ጥቅስ የተወሰደውም በዚህ በሦስተኛው ክፍል ከሚገኘው ትንቢተ ኢሳይያስ ምዕራፍ 60 ቊጥር 14 ላይ ነው።

Monday, October 19, 2015

“ልበ ነጹሖች ብፁዓን ናቸው፥ እግዚአብሔርን ያዩታልና” (ማቴ. 5፥8)

ከደምፀ ቃለ አብ

ጌታችን አየሱስ ክርስቶስ በተራራው ላይ ያስተማራቸው ትምህርቶች ደስታ ለሞላበት አኗኗር መሠረት ናቸው፡፡ ትምህርቶቹ በተራራ ላይ የተሰበኩ ሲሆኑ የመንፈሳዊ ከፍታም መገለጫዎች ናቸው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት ለማደግ ምትሐታዊ ቊጥሮች የምስጢር ቊልፎች የሉም፡፡ የመንፈሳዊ ከፍታ መመዘኛው የተራራው ስብከት ነው፡፡ የተራራው ስብከት የውስጥ መጠይቅ በመሆኑ ሰው ራሱን የሚያይበትና የሚያስውብበት ልዩ ክፍል ነው፡፡ በተራራው ስብከት ዓለም ትልቅ ስፍራ የምትሰጣቸው ነገሮች ውድቅ ሆነዋል፡፡ ዓለም፡-
*     ራስህን አክብር ትላለች፤ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- በመንፈስ ድኾች የሆኑ ብፁዓን ናቸው$ መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና (ማቴ. 5፥3) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ደግሞ ራስህን አክብር፤ ዓለም ያንተ ናትና የሚል ይመስላል፡፡
*     ደስተኛ ብቻ ሁን ትላላች፤ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- የሚያዝኑ ብፁዓን ናቸው$ መጽናናትን ያገኛሉና፥ማቴ. 5$4) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ደግሞ፡- ደስተኛ ብቻ ሁን፤ ስለ ሌላው ምን አገባህ ትላለች፡፡
*     በደልን አትርሳ ትላለች፡፡ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- የዋሆች ብፁዓን ናቸው፥ ምድርን ይወርሳሉና (ማቴ. 5፥5) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ደግሞ፡- በደልን አትርሳ፤ አጥምደህ ያዘው፤ ላንተ ይገዛልና ትላላች፡፡
*     እንደ ጊዜው ኑር ትላለች፡፡ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- ስለ ጽድቅ የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው፥ ይጠግባሉና (ማቴ. 5፥6) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ደግሞ፡- ተመሳስለህ ኑር፤ ከሁሉም ትጠቀማለህ ትላለች፡፡
*     ተቀበል እንጂ የአንተን አታካፍል ትላለች፡፡ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- “የሚምሩ ብፁዓን ናቸው፥ ይማራሉና” (ማቴ. 5፥7) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ግን፡- “አጠራቅም ይበዛልሃል” የሚል ነው፡፡
*     ንጽሕናህን ጠብቅ ትላለች፡፡ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- ልበ ንጹሖች ብፁዓን ናቸው እግዚአብሔርን ያዩታልና” (ማቴ. 58) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ግን፡- “ውስጥህን ማንም አያውቅም፤ ውጫዊ ንጽሕናህን ጠብቅ” ይላል፡፡

Monday, October 12, 2015

አለቃ ነቅዐ ጥበብ

ትረካ፡- ከነቅዐ ጥበብ

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ታሪካቸው የተመዘገበው ኒቆዲሞስና ዮሴፍ ዘአርማትያስ (ዮሐ. 3፥2፤ 19፥38) ያደርጉት እንደ ነበረው፥ መሪጌታ ብርሃነ መስቀልም ጨለምለም ሲል ራሳቸውን ለወጥ አድርገው ወደ አለቃ ነቅዐ ጥበብ እየሄዱ ከሚማሩ ስውር ደቀ መዛሙርት መካከል አንዱ ነው፡፡ በሚያገለግልበት ደብር ውስጥ እርሱ ከሚኖርበት የመቃብር ቤት ጥቂት ዕልፍ ብሎ በሚገኘው በሌላው መቃበር ቤት ውስጥ ለሚኖረው ባልንጀራው ለመሪጌታ በትረ ጽዮን ግን ወዴት እንደሚሄድ አይነግረውም ነበር፡፡ ምክንያቱም ካሁን ቀደም በወንጌል ስለ ተገለጠው የእግዚአብሔር ጽድቅ ሊያስረዳው ቢሞክር፥ ፍጹም ተቃዋሚና እርሱንም አሳልፎ ሊሰጠው የሚችል ዐይነት ሰው ሆኖ ስለ ተመለከው፥ በሌላው ጕዳይ ካልሆነ በቀር ለጊዜው በዚህ ነገር ዳግም ላያነጋግረው ወስኖ ነበር፡፡

ብዙ ጊዜ እንደ ነገ የሚቆሙትን የማሕሌት ቀለም እንደ ዛሬ ዐብረው ሲመለከቱ፥ የወንጌልን እውነት ለመግለጥ በር የሚከፍት ቃል ካጋጠመው፥ ወይም ከእግዚአብሔር ቃል ፍጹም ተቃራኒ የሆነ ስሕተት ካገኘ አያልፍም፤ በዚያ መነሻነት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ ውይይትና ክርክር ያደርጉ ነበር፡፡ ባለማቋረጥ የሚንጠባጠብ የውሃ ጠብታ ከታች ያለውን ዐለት እንደሚቦረቡረው፥ መሪጌታ ብርሃነ መስቀል በመሪጌታ በትረ ጽዮን ጆሮ የሚያንቈረቊረው መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነት ከጊዜ ወደ ጊዜ ልቡን እየሸረሸረው መምጣቱ አልቀረም፡፡ ይሁን እንጂ የያዘውን ነገር በቀላሉ ለመልቀቅ ስለሚቸገርና ሽንፈትም ስለሚመስለው በቶሎ እጅ አይሰጥም፡፡ በዚህ ሁኔታ ብዙ ጊዜያት አልፈዋል፡፡

Tuesday, October 6, 2015

የራስ ኩራት

በግር አይቀመስ፣
በአፍ አይዳሰስ፣
በእጅ አይተነፈስ፣
ፊኛ ደም አይረጭም፣
ኩላሊት አይፈጭም
ጥፍርም አያጎርስም፣
አይኬድ በምላስ፣
በጥርስ አይለቀስ፡፡
ልብ አያጨበጭብ፣
አያስብም ቅንድብ፣
ሳንባም አይዋብ፡፡
ዐይንም አይሰማ፣
ጆሮ አይል እማማ፣
ደም አያጠልቅ ጫማ፡፡
የጅ ጣት ቀለበት፣
አይከተት ባንገት፣
ጉትቻ የጆሮ፣
አይሆን ለጉሮሮ፣
ጉርም በየተራ
አይጎርስም እንጀራ፡፡
ሰልካካ አፍንጫ
አይችልም ሩጫ፡፡
ደረት . . . ሱሪ ለብሶ
እግር ከንፈር ነክሶ
ጣፊያን ተንተርሶ
ተረከዝ ተናዶ
ግንባር ከስር ወርዶ
ትከሻ ሲሳለቅ
ወገብ እንባ ሲለቅ
ባት ሲተፋ ምራቅ
ማነው ይህን ያየ፤
እንደዚህ የለየ፤
ይሄ ሁሉ ድንቅ!
ታይቶም አይታወቅ፡፡
ደግሞ ይሄ ብሶ
ጥርስ ምላስ ነክሶ
ፍርድ ቤት ተከሶ
እግር እግርን ገጭቶ
በደንብ ተመታቶ
ሲለያይ ተፋቶ
እጅ ካፍ ተጣልቶ
ሳያጎርሰው ቀርቶ
አላየሁም ከቶ፡፡
ጨጓራ ለአንጀት
ምግብ ሳይልክለት
ለራሱ በልቶበት
ሟጦ ጨርሶበት፡፡
ልብ ደም ሳይሰጠው
ኩላሊት ሲያፋጠው
በቡጢ ሲመታው
መቼ ታየ ለሰው፡፡
ቅንድብ አይን ሲገጭ
ዐይን ሲነጫነጭ
በውሳኔ እንዲላጭ
ሲሳልለት ምላጭ
ማን ያውቃል ሰምቶ፤
በጆሮው አጣርቶ፤
መዳፍም ቀንቶበት
ጣት ሲያጠልቅ ቀለበት
አጡዞት በቡጢ
ብሎትም መናጢ
መዝልጎ ቆንጥጦ
ገዝቶትም ረግጦ
ማነው ይህን ያየ፤
እንደዚህ የለየ፤
ሁሉም አለው ሥራ
ለራሱ ሚያኮራ፡፡
ጆሮም ማዳመጡ
እግርም መሯሯጡ
እጅም መዳሰሱ
ምላስም መቅመሱ
ሳንባም መተንፈሱ
ጨጓራም መፍጨቱ
አፍንጫም ማሽተቱ
አይንም መልከት መልከት
ይሄ ነው ሚያምርበት
የሌላው ይቅርበት
የራሱ ነው ኩራት፡፡
ዐይን ቢል አላይም
አፍንጫ አላሸትም
እጅ አይወጣውም
ስጦታው የለውም
ሁሉም አለው ሥራ
ለራሱ ሚያኮራ
ብርቱና ጠንካራ፡፡

(ከአዲስ መስቀሌ)


በጮራ ቍጥር 39 ላይ የቀረበ

Monday, September 28, 2015

የክርስቶስ ተከታዮችና መለያቸው

መስበኪያ ቦታ የሚል ፈቺ ባለው በዚህ ዐምድ ወንጌል ይሰበካል፡፡
መምሬ ባሮክ
ሰዎች ከጥንት ጀምሮ ለሚያምኑበት ነገር መለያ ወይም መታወቂያ ማበጀታቸው የተለመደ ነው፡፡ የጥንት ክርስቲያኖች በግሪኩ መስቀልና “ክቱስ” (የዓሳ ምስል) የክርስቲያንነታቸው መታወቂያ ነበር፡፡ በቅርቡ ኮሚኒስቶች ማጭድና መዶሻ የሚያምኑበት ነገር መገለጫ ሆነው አገልግለዋል፡፡ በእናት ቤተ ክርስቲያንም አንድ ሰው ክርስቲያን መሆኑን ለመግለጽ በአንገቱ ላይ ማተብ (ክር) ማሰሩ የተለመደ ትውፊት ነው፡፡

ከጌታ ዕርገት በኋላ ስለ ሐዋርያት÷ የሐዋርያት ሥራ 4÷13 የክህናት አለቆች በድርጊታቸው ከኢየሱስ ጋር እንደ ነበሩ ዐወቋቸው ሲለን÷ ምዕራፍ 11÷26 ደግሞ እነዚህ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ለመጀመሪያ ጊዜ በአንጾኪያ “ክርስቲያን” እንደ ተባሉ ይነግረናል፡፡ ለመሆኑ አንድ የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይ ወይም ደቀ መዝሙር መታወቂያው ምንድን ነው? ብንል÷ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ዐሥራ ዐምስት ላይ ያስተማረው ይህን እውነት የሚገልጥ ነው፡፡ እንደምናውቀው የዮሐንስ ወንጌል ከምዕራፍ 13 እስከ ምዕራፍ 17 ጌታ በሕማማቱ ሳምንት ያስተማረው ትምህርት ሲሆን÷ እንደሚሰናበት ሰው ለደቀ መዛሙርቱ አደራና መመሪያ የሰጠባቸው ምዕራፎች ናቸው፡፡ በእነዚህ ምዕራፎች ተለይቶአቸው የሚሄድ በመሆኑ ደቀ መዛሙርቱ ማዘናቸውንና ጌታም እነርሱን ማጽናናቱን÷ ተልእኮውንም አስረግጦ መግለጡንና ሊያደርጉ የሚገባቸውንም ማሳሰቡን እናነባለን፡፡ ከእነዚህ ዐምስት ምዕራፎች በተለይ ምዕራፍ ዐሥራ ዐምስት ላይ አጽንኦት የሰጠው የእርሱ ተከታዮች (ደቀ መዛሙርት) በሌሎች ሊታወቁ ወይም ሊገለጡ ስለሚችሉባቸው ሦስት መሠረታውያን መለያዎች ነው፡፡ 

Sunday, September 20, 2015

ኢየሱስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ

ስለ ጌታችን፥ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት ባለፉት ተከታታይ ዕትሞች ትምህርቶች ሲተላለፉ ቈይተዋል። ዛሬ የመጨረሻውን ክፍል የምንመለከት ሲሆን፥ “የክርስቶስ መካከለኛነት በሥጋ ወደሙ በኩል የሚፈጸም ነው” የሚለውን የአንዳንዶች አመለካከት በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ለመመርመር እንሞክራለን። በርግጥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፥ “ክርስቶስ መካከለኛ ነው ማለት ሥጋ ወደሙ መካከለኛ ነው ማለት ነው” ብላ እንደምታስተምር በግልጥ የተጻፈ ነገር አልተገኘም። በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የሚሰብኩ አንዳንድ ሰባክያን ግን ትምህርቱን ባፍም በመጣፍም ሲያስተምሩት መገንዘብ ችለናል።

መምህር ታሪኩ አበራ የተባሉ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ምሩቅ “ኢየሱስ ማነው?” በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ፥ “ዛሬ ኢየሱስ ለእኛ ጠበቃ ነው ስንል በሰማይ ከዲያብሎስ ጋር፥ ዕለት በዕለት የሚጨቃጨቅ የሚከራከር ጠበቃ ሆኖ አይደለም፤ አንድ ጊዜ በፈጸመው የማዳን ሥራ የጌታን ሥጋና ደም ከተቀበልን … ያ ሥጋና ደም … ጠበቃ ሆኖ ከዲያብሎስ ክስ ነጻ ያወጣናል። ለዚህ ነው ሥጋዬን የበላ ደሜን የጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው ያለው” ሲሉ ጽፈዋል (ገጽ 119 አጽንዖት የግል)። እርሳቸው እንዲህ ያሉት፥ “ልጆቼ ሆይ፥ ኀጢአትን እንዳታደርጉ ይህን እጽፍላችኋለሁ። ማንም ኀጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን፤ እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው” (1ዮሐ. 2፥1) ለሚለው መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል ማብራሪያ እሰጣለሁ ብለው ነው።

Monday, September 7, 2015

ብዙ ተስፋ


ተስፋ የሚለው ቃል ሲጠራ በራሱ ተስፋ ይለመልማል። ልብ በሐሤት ይሞላል። የሰው እግር በድል የሚራመደው ልቡ በተስፋ ሲሞላ ነው። ተስፋ ከሌለ እግር ሽባ ይሆናል። ተስፋ ግን ሽባውን እግር የሚያረታ፥ ከተጠበቀው በላይ የሚያራምድ ነው። ተስፋ ያጣ ሰው ምንም ሳይሆን ብዙ የሆነ ይመስለዋል። ገና ቀን ሳለ ሌሊት መስሎት ይተክዛል። ትጥቁና ስንቁ እያለ ጦርነቱን በሽንፈት /በበቃኝ/ ይደመድማል። ተስፋ መዳረሻ ነው። ከምሳ ሰዓት በኋላ እስከ እራት ያለው ጊዜ ረጅም ነው። ሠርክ ላይ ትንሽ ምግብ ይቀመሳል። ያ መክሰስ ወይም መዳረሻ ነው። ተስፋም እንዲሁ ነው። እግዚአብሔር ያሰበልን ነገር ላይ ለመድረስ መዳረሻ /መቈያ/ ነው።

ተስፋ በመጀመሪያ በፅንሰቱ ኋላም በልደቱ ደስ ያሰኛል። ተስፋ ያደረጉት ነገር ሲፈጸም ልብ ሙሉ ይሆናል፤ መኖርም ምክንያታዊ ይመስላል። እግዚአብሔር የተስፋ አምላክ፥ የተስፋ መሠረት፥ የተስፋ ፍጻሜ ነው። እግዚአብሔር ተስፋን የሚሰጠው ከራሱ የፍቅርና የቸርነት ባሕርይ በመነሣት ነው። ይህ ሁለት ነገሮችን ያስተምረናል።
1.    ተስፋን የሰጠን በራሱ ፈቃድ ስለ ሆነ ለመፈጸም አይቸገርም።
2.   የተስፋ መነሻ ፍቅር ነው፤ ፍቅር ሲኖረን ቸሮች ብቻ ሳይሆን ባለተስፋም እንሆናለን።

Wednesday, August 26, 2015

“መድሎተ ጽድቅ” በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን - ክፍል አራት

Read in PDF

“መድሎተ ጽድቅ” በምዕራፍ አንድ፥ በ1.1 ላይ “የተሐድሶዎች መነሻዎችና መሠረቶች” በሚለው ርእስ ሥር የሚገኘውን ንኡስ ርእስ “1.1.1 በ ‘መሰለኝ’ ማመን” ብሎታል፡፡ በዚህ ንኡስ ርእስ ሥር የቀረበው ሐተታ፥ እኛ ሃይማኖትን ያኽል መሠረታዊና ጥልቅ ጕዳይ “ለእኛ የመሰለንን” እያልን እንደ ስብሰባ አስተያየት እምነታችን ለእኛ የመሰለን ሐሳብ ወይም ግምት እንደ ኾነ አድርገን እንደ ጻፍን በማስመሰል፥ በልል ግስ የተጻፉትንና ማስረጃ የሚላቸውን ከየ መጽሔቱና ከየ መጻሕፍቱ ጠቃቅሷል፡፡ ስለዚህ በዚህ ክፍል ይህን ጕዳይ እንመረምራለን፡፡ በመጀመሪያ የጠቀሰው የሚከተለውን ነው፡፡   
·        ለያንዳንዳችን የመሰለንንና ያመንበትን ከሊቃውንትም የተማርነውን ሐሳብ እውነት መኾኑንና ጠቃሚነቱን ከተቀበልነው ዘንድ ለሌሎች ማስገንዘብ ይገባል በማለት እነሆ ጮራ የተሰኘውን መንፈሳዊ መጽሔት ለማሳተም ተነሥተናል፡፡” (ጮራ ቊጥር 1 ገጽ 3)
በመሠረቱ እምነት በመሰለኝ የሚቆም ነገር አለ መኾኑ ለማንም ግልጥ ነው፡፡ ሰው ከወላጆቹ ከሚወርሰው ሃይማኖት ባሻገር በሃይማኖቱ ውስጥ ሲኖር በራሱ ያወቀውንና የተረዳውን እውነት ያምናል፡፡ ከተገለጠለትና በቃሉ መሠረት ማረጋገጫ ከቀረበለት እውነት ውጪ ያሉትንና ማረጋገጫ ያልተገኘላቸውን ጕዳዮች ለመመርመር ሲሞክር ግን በመሰለኝ ነው እንጂ “ነው” በሚል ርግጠኛነት አይደለም፡፡ ስለዚህ ገለጣው “እንዲህ ሊኾን ይችላል” “እንዲህ ይመስላል” ወዘተ. የሚል ይኾናል፡፡ ለምሳሌ “መድሎተ ጽድቅ” በገጽ 34 ላይ የጠቀሰውና ከጮራ ቊጥር 11 ገጽ 5 ላይ የወሰደውን እንመልከት፡፡ በዚህ ክፍል ስለ ሰብአ ሰገል መምጣትና ስለ ማንነታቸው ተጽፏል፡፡ የሰብአ ሰገል ወደ ቤተ ልሔም መምጣት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመዘገበ እውነት በመኾኑ ርግጠኛ በኾነ ቃል “ጠቢባኑ (ሰብአ ሰገል) ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም መጡ” ተብሎ ነው የተገለጠው እንጂ፥ በመሰለኝ “መጥተው ሊኾን ይችላል” ወይም “ሳይመጡ አልቀረም” ወዘተ. ተብሎ በአስተያየት መልክ አይደለም የቀረበው፡፡ ስለ ማንነታቸው ግን መጽሐፍ ቅዱስ “ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም” መምጣታቸውን ብቻ ነው እንጂ አገራቸው የት እንደ ኾነ፥ ከማን ወገን እንደ ኾኑ ወዘተ. ርግጠኛውን ነገር አይናገርም፡፡
ይህን በተመለከተ ልናደርግ የምንችለው የመጀመሪያው ነገር መጽሐፍ ቅዱስ የገለጠውንና “ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም መጡ” የሚለውን ብቻ ተቀብሎ ማመንና መጽሐፉ ያልገለጠውን ነገር ለመግለጥ አለ መሞከር ነው፡፡ ኾኖም መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠንን ፍንጭ መነሻ በማድረግ ነገሩን ማጥናትና መላ ምታችንን ማስቀመጥ የምንችልበት ዕድል የተዘጋ አይደለም፡፡ ስለዚህ ኹለተኛውን አማራጭ የምንከተል ከኾነ የደረስንበትን መላ ምት “ነው” በሚል ርግጠኛ ቃል ሳይኾን፥ “ሊኾን ይችላል” በሚል ልል ግስ ነው መግለጥ ያለብን፡፡ በጮራ የተደረገውም ይኸው ነው፡፡ ርግጡንና የታመነውን ነገር “ነው” እንላለን፤ ርግጠኛ ያልተኾነበትንና በእኛ መረዳት የደረስንበትን ጕዳይ ግን “ሊኾን ይችላል” እንላለን፡፡ ይህም እምነታችንን ርግጠኛ ባልኾነና በመሰለን ነገር ላይ እንዳሳረፍን ተደርጎ የሚወሰድና የሚያስወቅሠን ሊኾን አይገባም፡፡
ሊቀ ጠበብት አያሌው ታምሩ “የኢትዮጵያ እምነት በሦስቱ ሕግጋት” የተሰኘውን መጽሐፍ ለመጻፍ ካነሣሡአቸው ምክንያቶች መካከል አንዱ የውጪ አገር ታሪክ ጸሐፊዎች የጻፏቸውን ተርጕመው ያሳተሙና ያሠራጩ ኢትዮጵያውያን ጸሓፊዎች “ሰብአ ሰገል ኢትዮጵያውያን መኾናቸውንና የትንቢቱ ባለቤቶች መኾናቸውን ክደው የሌላ አገር ሰዎች በድንገት የተጠሩ አረመኔዎች እንደ ነበሩ” መናገራቸው መኾኑን ገልጠው ነበር (1953፣ 17፡ 111)፡፡ እንደ እርሳቸው እምነት ሰብአ ሰገል ኢትዮጵያውያን ሊኾኑ ይችላሉ ሳይኾን በርግጠኛነት ኢትዮጵያውያን “ናቸው”፡፡ ኢትዮጵያውያን ናቸው ለማለትም በሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ ከእነርሱ ጋር ተያይዘው ያልተጠቀሱና “ኢትዮጵያ” የሚል ስም ይዘው የተጻፉ የብሉይ ኪዳን ትንቢቶችን አስደግፈው ሰብአ ሰገል ኢትዮጵያውያን መኾናቸውን ለማሳመን ይሞክራሉ፡፡ ይኹን እንጂ ሰብአ ሰገል ወደ ቤተ ልሔም የመጡት ከምሥራቅ መኾኑ ስለ ተገለጠ፥ ከኢየሩሳሌም ወደ ደቡብ 9 ኪሎ ሜትር ርቃ ለምትገኘው ቤተ ልሔም (የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት 1972፣ ገጽ 97) ኢትዮጵያ በምሥራቅ ልትገኝ አትችልምና ሰብአ ሰገል ኢትዮጵያውያን ናቸው የሚለውን መቀበል ያስቸግራል፡፡
በሊቀ ጠበብት አያሌውና ይህን ትውፊት ትረካ እንደ እምነት በተቀበሉቱ ዘንድ ኢትዮጵያውያን መኾናቸው ብቻም ሳይኾን ስማቸው ጭምር የታወቀ በመኾኑ በስም ጠቅሰዋቸዋል፡፡ ይህ በትውፊት ሲነገር የቈየና በአንድምታ ትርጓሜ የተገለጠ ከመኾኑ በቀር ምንጩን አልጠቀሱም፡፡ ምናልባት የ“መድሎተ ጽድቅ” ጸሓፊ ይህን ትውፊታዊ ትረካ በ“ሊኾን ይችላል” ሳይኾን በ“ነው” ይኾናልና የሚያምነው እዚህ ላይ ልዩነት አለን፡፡ ልዩነታችንም መጽሐፍ ቅዱስ ያላረጋገጠውንና መነሻውን መጽሐፍ ቅዱስ አድርጎ ተጨማሪ ማብራሪያ የተሰጠበትን ጕዳይ እንደ አንድ አስተያየት ከመውሰድ በቀር “ነው” ብሎ በርግጠኛነት መቀበልና ማመን ስለማይቻል ነው፡፡ 

Sunday, August 16, 2015

ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ

በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት ላይ በዚህ ዐምድ በተከታታይ የወጡትን ጽሑፎች አስመልክተው፣ የተለያዩ አንባብያን የስልክ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን ለዝግጅት ክፍሉ አቅርበዋል። ከአንባብያኑ መካከል አንዳንዶቹ የክርስቶስን መካከለኛነት ላለመቀበልና ለሌሎች ቅዱሳን ለመስጠት አለን ያሉትን ማስረጃ በማቅረብ ጭምር ለመከራከር ሞክረዋል። ለክርክራቸው እንዲረዳቸውም፣ “ስለዚህ እኛ ከአሁን ጀምሮ ማንንም በሥጋ እንደሚሆን አናውቅም፤ ክርስቶስንም በሥጋ እንደ ሆነ ያወቅነው ብንሆን እንኳ፥ አሁን ግን ከእንግዲህ ወዲህ እንደዚህ አናውቀውም” (2ቆሮ. 5፥16) የሚለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል የጠቀሱ ሲሆን፣ በመጨረሻም፣ “አሁን እርሱ መካከለኛ መሆኑ ቀርቷል፤ አሁን አምላክ ነው” ሲሉ ደምድመዋል። ክርስቶስን ከመካከለኛነቱ ስፍራ አንሥተውም፣ “አሁን መካከለኛው ሥጋ ወደሙ ነው” ሲሉም አክለዋል። ስለ ሥጋ ወደሙ የተባለውን ለቀጣዩ ዕትም እናቈየውና በጥቅሱ ላይ የተላለፈውንና ክርስቶስ አሁን አምላክ እንጂ ሰው አይደለም የሚለውን አውጣኪያዊ ትምህርት በመመርመር የክርስቶስን መካከለኛነት መጽሐፍ ቅዱስንና የአበውን ምስክርነት በመጥቀስ ወደ ማሳየት እንለፍ።
ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ ብቻ ነበረ እንጂ አሁን ወደ ክብሩ ከገባ በኋላ መካከለኛ አይደለም’ የሚሉት በትምህርተ ሥጋዌ ላይ በቂ ዕውቀት የሌላቸው ብቻ ሳይሆኑ፣ ተምረዋል የሚባሉትም ጭምር እንደ ሆኑ ይታወቃል። በተለይም የተማሩት ክፍሎች እንዳልተማሩቱ አፋቸውን ሞልተው አሁን አምላክ ብቻ ነው እንጂ ሰውም አይደለም አይሉም፤ ክርስቶስ ዛሬም ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑን እናምናለን ይላሉ። ክርስቶስ አሁን በአብ ቀኝ ተቀምጦ ባለበት ሁኔታ ግብረ አምላክን (የአምላክን ሥራ) እንጂ ግብረ ትስብእትን (የሰውነትን ሥራ) አይፈጽምም ስለሚሉ ግን በክብር የሆነውን ግብረ ትስብእትን ያስተባብላሉ። ለምሳሌ፣ … ነቢረ የማን (በአብ ቀኝ መቀመጥ) ክርስቶስ ግብረ ትስብእት ከፈጸመ በኋላ እንደ ገና የሰውነትን ሥራ የማይሠራ፥ ነገር ግን ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በክብር መለኮታዊ ሥራውን እየሠራ የሚኖር መሆኑን የሚያስረዳ ቃል ነው”[1] ያሉ ይገኛሉ። አባባሉ ኢየሱስ ክርስቶስ በአብ ቀኝ እስኪቀመጥ ድረስ መለኮት ሥራውን ለትስብእት ትቶ ትስብእት ብቻ ይሠራ ነበር፤ ትስብእት ደግሞ አሁን በተራው የሥራ ጊዜውን ስለ ፈጸመ ሥራውን ለመለኮት ተወ ያሰኛል። እንዲህ ከሆነም ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ ግብረ ትስብእትን ብቻ እንጂ ግብረ መለኮትን አይፈጽምም ነበር የሚል አንድምታ ያለው ይመስላል። ቅዱሳት መጻሕፍትና በእነርሱ ላይ የተመሠረቱ የአበው ምስክርነቶች ግን የሚነግሩን ከዚህ የተለየ እውነት ነው።

“መድሎተ ጽድቅ” በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን - ክፍል ሦስት


ካለፈው የቀጠለ -
ዳዊት እስቶክስና የሠራዊተ ክርስቶስ ማኅበር
ብንደግፈውም ብንቃወመውም፥ ቢስማማንም ባይስማማንም አንድን የተፈጸመንና የራሱን አሻራ ትቶ ያለፈን እውነተኛ ታሪክ መለወጥ አንችልም። ታሪኩን ለመለወጥና ሌላ መልክ ሰጥተን ለመግለጥ ብንሞክር ግን በታሪክ ተወቃሽ ከመኾን አናመልጥም። እንዲህ ሲባል ግን ታሪክን አዛብቶ ማቅረብና ያን የተዛባ ታሪክ ሰዎች እውነተኛ ታሪክ መስሏቸው ለጊዜውም ቢኾን እንዲቀበሉት ማድረግ አይቻልም ማለት አይደለም። ለምሳሌ፦ ሞትን ድል አድርጎ የተነሣውን የጌታችንን የትንሣኤ የምሥራች፥ ከሞት መነሣቱ ኪሳራ የሚያደርስባቸው መኾኑን የተረዱ የካህናት አለቆችና ሽማግሌዎች በሌላ የፈጠራ ታሪክ እንደ ተኩትና፥ ‘ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ሰረቁት እንጂ፥ ኢየሱስ ከሙታን ተለይቶ አልተነሣም’ የሚለው የፈጠራ ታሪክ እውነት መስሎ ወንጌላዊው ማቴዎስ ወንጌሉን እስከ ጻፈበት ጊዜ ድረስ እንኳ በአይሁድ ዘንድ ሲወራ እንደሚኖር ጽፏል (ማቴ. 28፥11-15)። ስለ ዴቪድ እስቶክስ ከዚህ ቀደም በማኅበረ ቅዱሳን፥ አኹን ደግሞ በ“መድሎተ ጽድቅ” እየተተረከ ያለው የተዛባ ታሪክ ከዚህ የተለየ አይደለም።
ታላቁ ሰው ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ ስለ ታሪክ አጻጻፍ ያስቀመጡት መርሕ እዚህ ላይ ቢወሳ መልካም ነው። እንዲህ ነበር ያሉት፥
ታሪክን መማር ለኹሉ ሰው ይበጃል፤ … የታሪክ ትምህርት ግን የሚጠቅም የውነተኛ ታሪክ ትምህርት ሲኾን ነው። እውነተኛንም ታሪክ ለመጻፍ ቀላል ነገር አይደለም። የሚከተሉትን ሦስት የእግዚአብሔር ስጥወታዎች ያስፈልጋልና። መጀመሪያ ተመልካች ልቦና፥ የተደረገውን ለማስተዋል፤ ኹለተኛ የማያደላ አእምሮ፥ በተደረገው ለመፍረድ፤ ሦስተኛ የጠራ የቋንቋ አገባብ፥ የተመለከቱትንና የፈረዱትን ለማስታወቅ። ያገራችን የታሪክ ጻፎች ግን በነዚህ ነገሮች ላይ ኀጢአት ይሠራሉ። በትልቁ ፈንታ ትንሹን ይመለከታሉ። ለእውነት መፍረድንም ትተው በአድልዎ ልባቸውን ያጠባሉ። አጻጻፋቸውም ድብልቅልቅ እየኾነ ላንባቢው አይገባም (2002፣ገጽ 1)።
በ“መድሎተ ጽድቅ” ስለ ዳዊት እስቶክስ የተጻፈው በአብዛኛው ይህን መስፈርት ያላሟላ ከመኾኑም በላይ፥ ታሪክን ያላገናዘበ፥ በእውነታው ላይ ያልተመሠረተና ምንጭ የሌለው፥ በጭፍን ጥላቻ ላይ የተመሠረተ ተራ ስም ማጥፋት ተደርጎ የሚወሰድ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ ቀደም “የገሃነም ደጆች” በሚል ርእስ በስምዐ ጽድቅ ልዩ ዕትም ጋዜጣ ላይ በተከታታይ ባወጣው ጽሑፍ፥ በተለይ በመጋቢት 1995 ዓ.ም. ዕትሙ የብዙዎችን ስም አክፍቶ በጻፈ ጊዜ፥ እንዲሁም “የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ” በሚል ርእስ በ2003 ዓ.ም. ባሳተመው አነስተኛ መጽሐፍ ላይ፥ የዳዊት እስቶክስን ታሪክ ያቀረበው በዚሁ መንገድ ነው። ዳዊት እስቶክስና ማኅበራቸውን “የሠራዊተ ክርስቶስ ማኅበር”ን አገልግሎት በተሳሳተ መንገድ ነው ያቀረቡት። ይህም የሚያሳየው ለዐላማቸው መሳካት ሲሉ የነበረውን ታሪክ ለውጠው በማቅረብ እውነተኛውን ታሪክ እያጠፉና ራሳቸው የፈጠሩትን ዐዲስ ታሪክ አሥርገው እያስገቡ መኾናቸውን ነው።
ዳዊት እስቶክስና “የሠራዊተ ክርስቶስ ማኅበር” በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያከናወኑት ተግባርና ያበረከቱት አስተዋፅኦ ብዙ ቢኾንም፥ በዚህ ጽሑፍ ግን ለአብነት ያኽል እጅግ ጥቂቱን ለመጠቃቀስ እንሞክራለን። (ለዚህ ምንጫችን በዋናነት፥ “The Most Valuable Thing: The Word at Work in Ethiopia” በተሰኘ መጽሐፋቸው ከሚሲዮናውያቱ አንዷ የነበሩት ዶሪስ ቤንሶን የጻፉት የማኅበሩ የአገልግሎት ታሪክ ነው። በተጨማሪ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በትምህርቶቻቸው ከተሳተፉትና በሕይወት ካሉት፥ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥና በሌላም ስፍራ በልዩ ልዩ የሥራ መስክ ላይ ከሚገኙት ከአንዳንዶቹ ያገኘነውን መረጃም በምንጭነት ተጠቅመናል።)

“Bible Church Men’s Society” (BCMS) በእንግሊዝ አገር በሎንደን የተቋቋመ ማኅበር ሲኾን፥ አባላቱ በአብዛኛው ከአንግሊካን ቤተ ክርስቲያን ናቸው። በኢትዮጵያ ተቋቁሞ ይሠራ የነበረው የዚህ ማኅበር ቅርንጫፍ፥ “የሠራዊተ ክርስቶስ ማኅበር” በመባል ይታወቅ ነበር። ማኅበሩ በኢትዮጵያ የ”BCMS” ቅርንጫፍ ኾኖ ይሠራ የነበረው በመንግሥት ፈቃድና ድጋፍ ሲኾን፥ በተለይ ደግሞ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋር በቅርብ በመተባበር ነበር። ይልቁንም በጎንደር ከሰሜንና በጌምድር ሀገረ ስብከት፥ በአሥመራ ከኤርትራ ሀገረ ስብከት፥ በመቀሌ ከትግራይ ሀገረ ስብከትና በሸዋ ለመዘዋወር ከሀገረ ስብከቱ ፈቃድና ስምምነት እያገኘ ሲኾን፥ በአዲስ አበባ ከመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ጋር ወዳጅና አጋር በመኾን ከፍተኛ የወንጌል አገልግሎት አበርክቷል።

“መድሎተ ጽድቅ” በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን - ክፍል ሁለት

Read in PDF
ካለፈው የቀጠለ -
“ሦስቱ የተሐድሶ ስልቶች” በ“መድሎተ ጽድቅ”
ጸሓፊው በመቅድሙ ላይ የሚያነሣቸውና ምላሽ ሊሰጣቸው የሚገቡ ሌሎቹ ፍሬ ነገሮች፥ ሦስቱ የተሐድሶ ስልቶች የተባሉት ናቸው። በቅድሚያ ተሐድሶ በሚለው ቃል ላይ በእርሱ በኩል የተሳሳቱ ምልከታዎች መኖራቸውንና የተዛቡ አስተያየቶች መሰጠታቸውን መግለጥ ያስፈልጋል። ተሐድሶ በዚህ ምድር ላይ ላለችው ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ የንስሓ ዕድል እንጂ ዐዲስ ሃይማኖት አይደለም፤ ወይም እርሱ እንደሚለው ኦርቶዶክስን ፕሮቴስታንት የሚያደርግ እንቅስቃሴ አይደለም። ተሐድሶ፥ እግዚአብሔር በገዛ ደሙ የዋጃት ቤተ ክርስቲያኑ ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ እንድትገኝለት የሚያደርግበት የተቀደሰ አሠራሩ ነው (ሐ.ሥ. 20፥28፤ ኤፌ. 5፥25-27)። ይኹን እንጂ እርሱ ተሐድሶን እኛ ለመፍጠር እየሞከርነው ያለ ዐዲስ ሃይማኖት አድርጎ ያቀርባል (2007፣ ገጽ 33)። በተጨማሪም ራሳችንን ተሐድሶ ብለን እንደምንጠራና ቃሉ (ተሐድሶ) መጠሪያ ስማችን እንደ ኾነ አድርጎ ጽፏል (ዝኒ ከማሁ፣ ገጽ 12)።
ተሐድሶ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሚታወቅና ሲሠራበት የቈየ የተለመደ ቃል ነው። ይልቁንም የራሷን ኢትዮጵያዊ ፓትርያርክ መሾሟን ተከትሎ ያ ክሥተት “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን መታደስ” ተብሎ ተጠርቷል። ከዚያ ወዲህ ባሉ ዓመታትም በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ በርካታ ተሐድሶኣዊ እንቅስቃሴዎች ተደርገዋል፤ ውጤቶችም ታይተዋል። በየልሳኖቿም ተሐድሶን የተመለከቱ ጽሑፎች ይወጡ ነበር። በተለይ ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ፓትርያርክ ከኾኑ ወዲህ በርካታ ተሐድሶኣዊ እንቅስቃሴዎች እንደ ነበሩና በርካታ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ፊት የሚያራምዱ ተግባራት እንደ ተከናወኑ ይታወቃል። ይህን በሚመለከት በጮራ ቊጥር 41 ላይ ከቀረበው ጽሑፍ ውስጥ የሚከተለውን መጥቀስ ለዚህ ጽሑፍ አንባብያን ይረዳል ብለን እናምናለን። 
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ፓትርያርክ ኾነው ሲሾሙ በብዙዎች ዘንድ ተስፋ የተደረገው፥ በሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ እየታየ የነበረው ተሐድሶ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ዘንድ እውን እንደሚኾን ነበር። ፓትርያርክ ኾነው በተሾሙ ጊዜ የዛሬዪቱ ኢትዮጵያ የተሰኘው አንጋፋ ጋዜጣ እንዲህ ብሎ ነበር፤ ‘የሌሎች አገሮች አብያተ ክርስቲያኖች እንደ ታደሱ ኹሉ የእኛም እንደ ዘመኑ መራመድ ይኖርባታል። የዐሥራ ዐምስተኛው ክፍለ ዘመን ሰዎች አስተሳሰብና የኻያኛው ክፍለ ዘመን ፍልስፍና በጣም የተራራቀና የተለያየ ስለ ኾነ፥ ሊያሳምን በሚችል በዐዲስ ዘዴ መቅረቡ የተሻለ ውጤት ያስገኛል። ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ይህን ኹሉ በማመዛዘን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በመንፈስ፣ በአሠራር፣ በአስተሳሰብና በአፈጻጸም የታደሰችና የዘመኑን ሥርዐት የተከተለች እንደሚያደርጓት ከፍተኛ ኀላፊነት ይጠብቃቸዋል’ (1963፣ ገጽ 2)።
ካለፉት ስድስት ዐሥርት ዓመታት በላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልሳን ኾኖ የሚያገለግለው ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ፥ ከ1960ዎቹ መጨረሻ አንሥቶ እስከ መስከረም 1982 ዓ.ም. ድረስ የተሐድሶ ዐምድ ነበረው። የዐምዱ ስያሜ በመጀመሪያ ‘ለተሐድሶ ዓምድ ለውይይት’ የሚል ነበር። በኋላ ‘ተሐድሶ ዐምድ ለውይይት’ ኾኗል። በዚህ ስያሜ እስከ ነሐሴ 1979 ዓ.ም. ድረስ ቀጥሏል። ከዚያ እስከ መስከረም 30/1982 ዓ.ም. ድረስ ‘የተሐድሶ ዐምድ ለውይይትና ለትምህርት’ ተብሎ ቀጥሎ የነበረ ሲኾን፥ ከዚያ ወዲህ ግን ዐምዱ ቀርቷል። የቀረበት ምክንያት የቤተ ክርስቲያቱ ተሐድሶ ተጠናቆ ነው በማለት ይኹን፥ ወይም ወቅቱ ከአስተዳደራዊ ተሐድሶ በላይ፥ ወሳኙ መንፈሳዊ ተሐድሶ እየመጣ የነበረበት ወቅት ስለ ኾነ፥ ያን በመፍራት ይኹን የታወቀ ነገር የለም። ከዚያ ወዲህ ግን ቀድሞ በበጎ ይታይና ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስፈላጊነቱ ታምኖበት ይሞካሽ የነበረው ተሐድሶ፥ ፀረ ተሐድሶ ዐቋም ባላቸው ወገኖች፥ መጥፎ ገጽታን እንዲላበስና እንዲጠላ ተደርጎ ብዙ ስለ ተነገረበትና በሌሎችም ምክንያቶች አንዳንዶች ዛሬም ተሐድሶ የሚለውን ስም በበጎ ጎኑ አይመለከቱትም።

“መድሎተ ጽድቅ” በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን - ክፍል አንድ

መንደርደሪያ
ታላቁ ሊቅ አለቃ መሠረት ስብሐት ለአብ “ስምዐ ጽድቅ ብሔራዊ” በተባለውና መሠረታውያን የኾኑ የክርስትና ትምህርቶችን በእግዚአብሔር ቃል መሠረትና የጥንት አበውን ምስክርነት በመጥቀስ ባዘጋጁት መጽሐፋቸው መቅድም ላይ፥ መጽሐፉ የተጻፈበትን ምክንያት ካተቱ በኋላ እንዲህ ብለው ነበር፤
… ይህን ሁሉ ማተታችን መምህራኑ የማያውቁት ኾነው እነርሱን ለማስተማር አይደለም። ነገር ግን የዚህን ሐሳብና ምስጢር ቃለ መጻሕፍትን መመገብ የሚያዘወትሩ ሊቃውንት እያወቁት ሳለ፥ ብዛት ያላቸው መሃይምናን አያውቁትም። አያውቁምና መምህራን ለማነጽ ጠቃሚ መኾኑን ተረድተው የሚደግፉትን፥ ‘ለሕዝበ ክርስቲያንም ይረባል’ ሲሉ የሚያቅዱትን ጥልቅ አስተያየት፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ያልጸና የመሃይምናኑ አእምሮ እንደማይደርስበት የታወቀ ቢኾንም (፩ቆሮ. ፪፥፲፩)፥መሃይምናኑ ራሳቸው ስለ ሃይማኖት ያላቸው ዕውቀት ዝቅተኛ መኾኑን መዝነው ስፍራውን ይለቅቁላቸው ዘንድ ተገቢ በሚኾንበት ፈንታ፥ ሊቃውንቱን በመናፍቃን ስም ቀብተው ‘አብዝኆ መጻሕፍት ያዘነግዕ ልበ።’  የሚል የአረማዊውን የፊስጦስን ቃል እየጠቀሱ (የሐዋ ፳፮፥፳፬) ወዲያውኑ እንደ ተለመደው በሠለስቱ ምእት ሊቃውንት ወንበር ላይ ተቀምጠው ሊፈርዱባቸው እንዳይቸኵሉና በዚሁ አስገራሚ አኳኋን የቤተ ክርስቲያንዋ መሻሻል ዕድል እንዳይሰበር አሥጊ መኾኑን ብቻ ለማሳሰብ ነው። (መሠረት 1951፣ ገጽ 15 አጽንዖት የግል)
በርግጥም አለቃ ያሉት የደረሰ ይመስላል። ዛሬ ትልቁ ችግር መሃይምናኑ የሊቃውንቱን ስፍራ መንጠቃቸውና በእነርሱ ወንበር ላይ ተቀምጠው ሊቃውንቱን “መናፍቅ” የሚል ስም ቀብተው ለመፍረድ መቸኰላቸው ነው። ይህም እርሳቸው እንዳሉት የቤተ ክርስቲያንን መሻሻል ወደ ኋላ የሚጐትት እንዳይኾን ያሠጋል። በዚህ አጋጣሚ ሌላውን ቀድሞ መናፍቅ ማለት አማኝ ለመኾን ማረጋገጫ እንዳልኾነ፥ በዚህ መንገድ መናፍቅ በመባልም መናፍቅ መኾን እንደሌለ መግለጥ እንወዳለን።  

ለዚህ ጽሑፍ መነሻው ያረጋል አበጋዝ የተባለ ዲያቆን “መድሎተ ጽድቅ” በሚል ርእስ የጻፈውና አሳትሞ መጋቢት 2007 ዓ.ም. ለገበያ ያቀረበው መጽሐፍ ነው። መጽሐፉ ተሐድሶኣዊ አገልግሎት ላይ ያተኰሩትን፦ “ስምዐ ጽድቅ ብሔራዊ”ን፥ “ጮራ መንፈሳዊ መጽሔት”ን፥ የተቀበረ መክሊት”ን፥ “የለውጥ ያለህ!!!”ን እና ሌሎችንም የሥነ ጽሑፍ ውጤቶች በመተቸት የተዘጋጀ ነው። ጸሓፊው በእነዚህ ሥራዎች ላይ ትችት ለማቅረብ ሲነሣ፥ ዝም ብሎ እንዳልተነሣና እነዚህ ሥራዎች በሕዝቡ ውስጥ ያሳደሩት ተጽዕኖ ቀላል አለ መኾኑን ስለ ተገነዘበ እንደ ኾነ እንረዳለን። እርሱ ግን፥ የተቻቸው መጽሔትና መጻሕፍት ውጤት እንዳልተገኘባቸው አስመስሎ ቢጽፍም፥ እውነታው እንደዚያ እንዳልኾነና እርሱንም ይህን መጽሐፍ እንዲጽፍ ግድ እንዳለው መካድ አይቻልም። ጽሑፎቻችንን ተችቶ ሲጽፍ፥ በአንድ በኩል እኛ ተሐድሶ ያስፈልጋቸዋል ብለን የገለጥናቸውን ትምህርቶች በመደገፍ፥ በቤተ ክርስቲያን ዐውደ ምሕረትም ኾነ በማኅበሩ ውስጥ ለመናገር የማይደፍራቸውን እውነቶች፥ እነዚህን የጽሑፍ ሥራዎች ተተግኖና ‘ቤተ ክርስቲያን የማትለውን ትላለች ይላሉ’ የሚል ምክንያት በመስጠት በነጻነት ለመግለጥ ሰፊ ዕድል እንዳገኘ ተገንዝበናል።
መጽሐፉን ስንመለከተው በአንድ በኩል ዛሬ አብዛኛው ሰው የማያውቀውንና የማያምነውን፥ ብዙዎች የቤተ ክርስቲያን ልጆችም “መናፍቅ”፥ “ተሐድሶ” እየተባሉ የተወገዙበትንና ዛሬም የሚወገዙበትን እውነት የኾነውን ትምህርት እውነተኛነት አጽድቆ የጻፈበት ኹኔታ ስለሚታይ፥ ይህን ገጽታውን እንደ ተሐድሶኣዊ ዐቋም ወስደንለታል። በአንጻሩ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት የሌላቸውንና ከጊዜ በኋላ የተፈጠሩ የስሕተት ትምህርቶችንና ልምምዶችን በግድ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ለማድረግ የታገለበት ኹኔታም ስለሚስተዋል፥ ያን ዐቋሙን ፀረ ተሐድሶኣዊና ኢመጽሐፍ ቅዱሳዊ መኾኑን ተረድተናል። በዚህ ምላሻዊ ጽሑፍ እነዚህን የተለያዩ ዐቋሞች በየፈርጁ ለማቅረብና ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት እንሞክራለን።