Tuesday, April 2, 2019

ምስባክ

“ዓሣ ከውሃ ከወጣ ነፍሱ ወጣ”
አንዳንድ ሰዎች ለወንጌል መሰል ስብከታቸው መንግሥተ ሰማያት ለማስገባት አንድ እርምጃ የሚቀር እስኪመስል ድረስ ለስብከታቸው የሚገርም ርእስ ይሰጣሉ። ወደ ስብከቱ ፍሬ ነገር ሲገባ ግን ውጤቱ አብዛኛውን ጊዜ የመኪናን ፍሬቻ መብራት ወደ ግራ አሳይቶ ወደ ቀኝ እንደ መታጠፍ ያኽል ነው፤ ወይም ወደ ቀኝ አሳይቶ ወደ ግራ እንደ መሄድ ይኾናል።

እኔና ክርስቲያን ወንድሜ (አሁን በሕይወተ ሥጋ የለም) በመንገድ ስናልፍ የምንሄድበትን ጉዳይ ትተን ይህን ስብከትማ ሳንስማ መሄድ የለብንም እንድንል ያደረገንን የስብከት ርእስ አንድ ቤተ ክርስቲያን የማስታወቂያ ሰሌዳ ላይ በትልቁ ተለጥፎ አየን። ርእሱ “ዓሣ ከውሃ ከወጣ ነፍሱ ወጣ” የሚል ነበር። ከዚያ ና እባክህ ይህን የወንጌል ቃል ተካፍለን እንሂድ፤ የሚገርም ርእስ ነው ተባብለን መልእክቱን ለመስማት ጎራ አልን። በጕጕት ስንጠብቅ የወንጌሉ ድምዳሜ “የዚህች ቤተ ክርስቲያን አባል ካልሆናችሁ ወደ መንግሥተ ሰማይ አትገቡም” የሚል ኾኖ አገኘነው። እኛም ሰባኪውን በመጨረሻ አግኝተን ማነጋገር አለብን ብለን ቈየንና አገኘነው፤ አነጋገርነውም። በተለይ ወንድሜ በሰል ያለ ሰው ነበርና እግዚአብሔርን፣ ሕዝቡንም ይቅርታ እንዲጠይቅና ከስሕተቱ እንዲመለስ አበክሮ መክሮት በሰላም ተለያየን። በእውነት ርእሱና የስብከቱ ሐተታና ድምዳሜ እንደ ወንጌሉ ቃል የተገናኙ አልነበሩም።