Wednesday, August 26, 2015

“መድሎተ ጽድቅ” በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን - ክፍል አራት

Read in PDF

“መድሎተ ጽድቅ” በምዕራፍ አንድ፥ በ1.1 ላይ “የተሐድሶዎች መነሻዎችና መሠረቶች” በሚለው ርእስ ሥር የሚገኘውን ንኡስ ርእስ “1.1.1 በ ‘መሰለኝ’ ማመን” ብሎታል፡፡ በዚህ ንኡስ ርእስ ሥር የቀረበው ሐተታ፥ እኛ ሃይማኖትን ያኽል መሠረታዊና ጥልቅ ጕዳይ “ለእኛ የመሰለንን” እያልን እንደ ስብሰባ አስተያየት እምነታችን ለእኛ የመሰለን ሐሳብ ወይም ግምት እንደ ኾነ አድርገን እንደ ጻፍን በማስመሰል፥ በልል ግስ የተጻፉትንና ማስረጃ የሚላቸውን ከየ መጽሔቱና ከየ መጻሕፍቱ ጠቃቅሷል፡፡ ስለዚህ በዚህ ክፍል ይህን ጕዳይ እንመረምራለን፡፡ በመጀመሪያ የጠቀሰው የሚከተለውን ነው፡፡   
·        ለያንዳንዳችን የመሰለንንና ያመንበትን ከሊቃውንትም የተማርነውን ሐሳብ እውነት መኾኑንና ጠቃሚነቱን ከተቀበልነው ዘንድ ለሌሎች ማስገንዘብ ይገባል በማለት እነሆ ጮራ የተሰኘውን መንፈሳዊ መጽሔት ለማሳተም ተነሥተናል፡፡” (ጮራ ቊጥር 1 ገጽ 3)
በመሠረቱ እምነት በመሰለኝ የሚቆም ነገር አለ መኾኑ ለማንም ግልጥ ነው፡፡ ሰው ከወላጆቹ ከሚወርሰው ሃይማኖት ባሻገር በሃይማኖቱ ውስጥ ሲኖር በራሱ ያወቀውንና የተረዳውን እውነት ያምናል፡፡ ከተገለጠለትና በቃሉ መሠረት ማረጋገጫ ከቀረበለት እውነት ውጪ ያሉትንና ማረጋገጫ ያልተገኘላቸውን ጕዳዮች ለመመርመር ሲሞክር ግን በመሰለኝ ነው እንጂ “ነው” በሚል ርግጠኛነት አይደለም፡፡ ስለዚህ ገለጣው “እንዲህ ሊኾን ይችላል” “እንዲህ ይመስላል” ወዘተ. የሚል ይኾናል፡፡ ለምሳሌ “መድሎተ ጽድቅ” በገጽ 34 ላይ የጠቀሰውና ከጮራ ቊጥር 11 ገጽ 5 ላይ የወሰደውን እንመልከት፡፡ በዚህ ክፍል ስለ ሰብአ ሰገል መምጣትና ስለ ማንነታቸው ተጽፏል፡፡ የሰብአ ሰገል ወደ ቤተ ልሔም መምጣት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመዘገበ እውነት በመኾኑ ርግጠኛ በኾነ ቃል “ጠቢባኑ (ሰብአ ሰገል) ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም መጡ” ተብሎ ነው የተገለጠው እንጂ፥ በመሰለኝ “መጥተው ሊኾን ይችላል” ወይም “ሳይመጡ አልቀረም” ወዘተ. ተብሎ በአስተያየት መልክ አይደለም የቀረበው፡፡ ስለ ማንነታቸው ግን መጽሐፍ ቅዱስ “ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም” መምጣታቸውን ብቻ ነው እንጂ አገራቸው የት እንደ ኾነ፥ ከማን ወገን እንደ ኾኑ ወዘተ. ርግጠኛውን ነገር አይናገርም፡፡
ይህን በተመለከተ ልናደርግ የምንችለው የመጀመሪያው ነገር መጽሐፍ ቅዱስ የገለጠውንና “ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም መጡ” የሚለውን ብቻ ተቀብሎ ማመንና መጽሐፉ ያልገለጠውን ነገር ለመግለጥ አለ መሞከር ነው፡፡ ኾኖም መጽሐፍ ቅዱስ የሚሰጠንን ፍንጭ መነሻ በማድረግ ነገሩን ማጥናትና መላ ምታችንን ማስቀመጥ የምንችልበት ዕድል የተዘጋ አይደለም፡፡ ስለዚህ ኹለተኛውን አማራጭ የምንከተል ከኾነ የደረስንበትን መላ ምት “ነው” በሚል ርግጠኛ ቃል ሳይኾን፥ “ሊኾን ይችላል” በሚል ልል ግስ ነው መግለጥ ያለብን፡፡ በጮራ የተደረገውም ይኸው ነው፡፡ ርግጡንና የታመነውን ነገር “ነው” እንላለን፤ ርግጠኛ ያልተኾነበትንና በእኛ መረዳት የደረስንበትን ጕዳይ ግን “ሊኾን ይችላል” እንላለን፡፡ ይህም እምነታችንን ርግጠኛ ባልኾነና በመሰለን ነገር ላይ እንዳሳረፍን ተደርጎ የሚወሰድና የሚያስወቅሠን ሊኾን አይገባም፡፡
ሊቀ ጠበብት አያሌው ታምሩ “የኢትዮጵያ እምነት በሦስቱ ሕግጋት” የተሰኘውን መጽሐፍ ለመጻፍ ካነሣሡአቸው ምክንያቶች መካከል አንዱ የውጪ አገር ታሪክ ጸሐፊዎች የጻፏቸውን ተርጕመው ያሳተሙና ያሠራጩ ኢትዮጵያውያን ጸሓፊዎች “ሰብአ ሰገል ኢትዮጵያውያን መኾናቸውንና የትንቢቱ ባለቤቶች መኾናቸውን ክደው የሌላ አገር ሰዎች በድንገት የተጠሩ አረመኔዎች እንደ ነበሩ” መናገራቸው መኾኑን ገልጠው ነበር (1953፣ 17፡ 111)፡፡ እንደ እርሳቸው እምነት ሰብአ ሰገል ኢትዮጵያውያን ሊኾኑ ይችላሉ ሳይኾን በርግጠኛነት ኢትዮጵያውያን “ናቸው”፡፡ ኢትዮጵያውያን ናቸው ለማለትም በሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ ከእነርሱ ጋር ተያይዘው ያልተጠቀሱና “ኢትዮጵያ” የሚል ስም ይዘው የተጻፉ የብሉይ ኪዳን ትንቢቶችን አስደግፈው ሰብአ ሰገል ኢትዮጵያውያን መኾናቸውን ለማሳመን ይሞክራሉ፡፡ ይኹን እንጂ ሰብአ ሰገል ወደ ቤተ ልሔም የመጡት ከምሥራቅ መኾኑ ስለ ተገለጠ፥ ከኢየሩሳሌም ወደ ደቡብ 9 ኪሎ ሜትር ርቃ ለምትገኘው ቤተ ልሔም (የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት 1972፣ ገጽ 97) ኢትዮጵያ በምሥራቅ ልትገኝ አትችልምና ሰብአ ሰገል ኢትዮጵያውያን ናቸው የሚለውን መቀበል ያስቸግራል፡፡
በሊቀ ጠበብት አያሌውና ይህን ትውፊት ትረካ እንደ እምነት በተቀበሉቱ ዘንድ ኢትዮጵያውያን መኾናቸው ብቻም ሳይኾን ስማቸው ጭምር የታወቀ በመኾኑ በስም ጠቅሰዋቸዋል፡፡ ይህ በትውፊት ሲነገር የቈየና በአንድምታ ትርጓሜ የተገለጠ ከመኾኑ በቀር ምንጩን አልጠቀሱም፡፡ ምናልባት የ“መድሎተ ጽድቅ” ጸሓፊ ይህን ትውፊታዊ ትረካ በ“ሊኾን ይችላል” ሳይኾን በ“ነው” ይኾናልና የሚያምነው እዚህ ላይ ልዩነት አለን፡፡ ልዩነታችንም መጽሐፍ ቅዱስ ያላረጋገጠውንና መነሻውን መጽሐፍ ቅዱስ አድርጎ ተጨማሪ ማብራሪያ የተሰጠበትን ጕዳይ እንደ አንድ አስተያየት ከመውሰድ በቀር “ነው” ብሎ በርግጠኛነት መቀበልና ማመን ስለማይቻል ነው፡፡ 

Sunday, August 16, 2015

ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ

በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት ላይ በዚህ ዐምድ በተከታታይ የወጡትን ጽሑፎች አስመልክተው፣ የተለያዩ አንባብያን የስልክ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን ለዝግጅት ክፍሉ አቅርበዋል። ከአንባብያኑ መካከል አንዳንዶቹ የክርስቶስን መካከለኛነት ላለመቀበልና ለሌሎች ቅዱሳን ለመስጠት አለን ያሉትን ማስረጃ በማቅረብ ጭምር ለመከራከር ሞክረዋል። ለክርክራቸው እንዲረዳቸውም፣ “ስለዚህ እኛ ከአሁን ጀምሮ ማንንም በሥጋ እንደሚሆን አናውቅም፤ ክርስቶስንም በሥጋ እንደ ሆነ ያወቅነው ብንሆን እንኳ፥ አሁን ግን ከእንግዲህ ወዲህ እንደዚህ አናውቀውም” (2ቆሮ. 5፥16) የሚለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል የጠቀሱ ሲሆን፣ በመጨረሻም፣ “አሁን እርሱ መካከለኛ መሆኑ ቀርቷል፤ አሁን አምላክ ነው” ሲሉ ደምድመዋል። ክርስቶስን ከመካከለኛነቱ ስፍራ አንሥተውም፣ “አሁን መካከለኛው ሥጋ ወደሙ ነው” ሲሉም አክለዋል። ስለ ሥጋ ወደሙ የተባለውን ለቀጣዩ ዕትም እናቈየውና በጥቅሱ ላይ የተላለፈውንና ክርስቶስ አሁን አምላክ እንጂ ሰው አይደለም የሚለውን አውጣኪያዊ ትምህርት በመመርመር የክርስቶስን መካከለኛነት መጽሐፍ ቅዱስንና የአበውን ምስክርነት በመጥቀስ ወደ ማሳየት እንለፍ።
ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ ብቻ ነበረ እንጂ አሁን ወደ ክብሩ ከገባ በኋላ መካከለኛ አይደለም’ የሚሉት በትምህርተ ሥጋዌ ላይ በቂ ዕውቀት የሌላቸው ብቻ ሳይሆኑ፣ ተምረዋል የሚባሉትም ጭምር እንደ ሆኑ ይታወቃል። በተለይም የተማሩት ክፍሎች እንዳልተማሩቱ አፋቸውን ሞልተው አሁን አምላክ ብቻ ነው እንጂ ሰውም አይደለም አይሉም፤ ክርስቶስ ዛሬም ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑን እናምናለን ይላሉ። ክርስቶስ አሁን በአብ ቀኝ ተቀምጦ ባለበት ሁኔታ ግብረ አምላክን (የአምላክን ሥራ) እንጂ ግብረ ትስብእትን (የሰውነትን ሥራ) አይፈጽምም ስለሚሉ ግን በክብር የሆነውን ግብረ ትስብእትን ያስተባብላሉ። ለምሳሌ፣ … ነቢረ የማን (በአብ ቀኝ መቀመጥ) ክርስቶስ ግብረ ትስብእት ከፈጸመ በኋላ እንደ ገና የሰውነትን ሥራ የማይሠራ፥ ነገር ግን ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በክብር መለኮታዊ ሥራውን እየሠራ የሚኖር መሆኑን የሚያስረዳ ቃል ነው”[1] ያሉ ይገኛሉ። አባባሉ ኢየሱስ ክርስቶስ በአብ ቀኝ እስኪቀመጥ ድረስ መለኮት ሥራውን ለትስብእት ትቶ ትስብእት ብቻ ይሠራ ነበር፤ ትስብእት ደግሞ አሁን በተራው የሥራ ጊዜውን ስለ ፈጸመ ሥራውን ለመለኮት ተወ ያሰኛል። እንዲህ ከሆነም ክርስቶስ በዚህ ምድር ሳለ ግብረ ትስብእትን ብቻ እንጂ ግብረ መለኮትን አይፈጽምም ነበር የሚል አንድምታ ያለው ይመስላል። ቅዱሳት መጻሕፍትና በእነርሱ ላይ የተመሠረቱ የአበው ምስክርነቶች ግን የሚነግሩን ከዚህ የተለየ እውነት ነው።

“መድሎተ ጽድቅ” በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን - ክፍል ሦስት


ካለፈው የቀጠለ -
ዳዊት እስቶክስና የሠራዊተ ክርስቶስ ማኅበር
ብንደግፈውም ብንቃወመውም፥ ቢስማማንም ባይስማማንም አንድን የተፈጸመንና የራሱን አሻራ ትቶ ያለፈን እውነተኛ ታሪክ መለወጥ አንችልም። ታሪኩን ለመለወጥና ሌላ መልክ ሰጥተን ለመግለጥ ብንሞክር ግን በታሪክ ተወቃሽ ከመኾን አናመልጥም። እንዲህ ሲባል ግን ታሪክን አዛብቶ ማቅረብና ያን የተዛባ ታሪክ ሰዎች እውነተኛ ታሪክ መስሏቸው ለጊዜውም ቢኾን እንዲቀበሉት ማድረግ አይቻልም ማለት አይደለም። ለምሳሌ፦ ሞትን ድል አድርጎ የተነሣውን የጌታችንን የትንሣኤ የምሥራች፥ ከሞት መነሣቱ ኪሳራ የሚያደርስባቸው መኾኑን የተረዱ የካህናት አለቆችና ሽማግሌዎች በሌላ የፈጠራ ታሪክ እንደ ተኩትና፥ ‘ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ሰረቁት እንጂ፥ ኢየሱስ ከሙታን ተለይቶ አልተነሣም’ የሚለው የፈጠራ ታሪክ እውነት መስሎ ወንጌላዊው ማቴዎስ ወንጌሉን እስከ ጻፈበት ጊዜ ድረስ እንኳ በአይሁድ ዘንድ ሲወራ እንደሚኖር ጽፏል (ማቴ. 28፥11-15)። ስለ ዴቪድ እስቶክስ ከዚህ ቀደም በማኅበረ ቅዱሳን፥ አኹን ደግሞ በ“መድሎተ ጽድቅ” እየተተረከ ያለው የተዛባ ታሪክ ከዚህ የተለየ አይደለም።
ታላቁ ሰው ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ ስለ ታሪክ አጻጻፍ ያስቀመጡት መርሕ እዚህ ላይ ቢወሳ መልካም ነው። እንዲህ ነበር ያሉት፥
ታሪክን መማር ለኹሉ ሰው ይበጃል፤ … የታሪክ ትምህርት ግን የሚጠቅም የውነተኛ ታሪክ ትምህርት ሲኾን ነው። እውነተኛንም ታሪክ ለመጻፍ ቀላል ነገር አይደለም። የሚከተሉትን ሦስት የእግዚአብሔር ስጥወታዎች ያስፈልጋልና። መጀመሪያ ተመልካች ልቦና፥ የተደረገውን ለማስተዋል፤ ኹለተኛ የማያደላ አእምሮ፥ በተደረገው ለመፍረድ፤ ሦስተኛ የጠራ የቋንቋ አገባብ፥ የተመለከቱትንና የፈረዱትን ለማስታወቅ። ያገራችን የታሪክ ጻፎች ግን በነዚህ ነገሮች ላይ ኀጢአት ይሠራሉ። በትልቁ ፈንታ ትንሹን ይመለከታሉ። ለእውነት መፍረድንም ትተው በአድልዎ ልባቸውን ያጠባሉ። አጻጻፋቸውም ድብልቅልቅ እየኾነ ላንባቢው አይገባም (2002፣ገጽ 1)።
በ“መድሎተ ጽድቅ” ስለ ዳዊት እስቶክስ የተጻፈው በአብዛኛው ይህን መስፈርት ያላሟላ ከመኾኑም በላይ፥ ታሪክን ያላገናዘበ፥ በእውነታው ላይ ያልተመሠረተና ምንጭ የሌለው፥ በጭፍን ጥላቻ ላይ የተመሠረተ ተራ ስም ማጥፋት ተደርጎ የሚወሰድ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ ቀደም “የገሃነም ደጆች” በሚል ርእስ በስምዐ ጽድቅ ልዩ ዕትም ጋዜጣ ላይ በተከታታይ ባወጣው ጽሑፍ፥ በተለይ በመጋቢት 1995 ዓ.ም. ዕትሙ የብዙዎችን ስም አክፍቶ በጻፈ ጊዜ፥ እንዲሁም “የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ” በሚል ርእስ በ2003 ዓ.ም. ባሳተመው አነስተኛ መጽሐፍ ላይ፥ የዳዊት እስቶክስን ታሪክ ያቀረበው በዚሁ መንገድ ነው። ዳዊት እስቶክስና ማኅበራቸውን “የሠራዊተ ክርስቶስ ማኅበር”ን አገልግሎት በተሳሳተ መንገድ ነው ያቀረቡት። ይህም የሚያሳየው ለዐላማቸው መሳካት ሲሉ የነበረውን ታሪክ ለውጠው በማቅረብ እውነተኛውን ታሪክ እያጠፉና ራሳቸው የፈጠሩትን ዐዲስ ታሪክ አሥርገው እያስገቡ መኾናቸውን ነው።
ዳዊት እስቶክስና “የሠራዊተ ክርስቶስ ማኅበር” በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያከናወኑት ተግባርና ያበረከቱት አስተዋፅኦ ብዙ ቢኾንም፥ በዚህ ጽሑፍ ግን ለአብነት ያኽል እጅግ ጥቂቱን ለመጠቃቀስ እንሞክራለን። (ለዚህ ምንጫችን በዋናነት፥ “The Most Valuable Thing: The Word at Work in Ethiopia” በተሰኘ መጽሐፋቸው ከሚሲዮናውያቱ አንዷ የነበሩት ዶሪስ ቤንሶን የጻፉት የማኅበሩ የአገልግሎት ታሪክ ነው። በተጨማሪ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በትምህርቶቻቸው ከተሳተፉትና በሕይወት ካሉት፥ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥና በሌላም ስፍራ በልዩ ልዩ የሥራ መስክ ላይ ከሚገኙት ከአንዳንዶቹ ያገኘነውን መረጃም በምንጭነት ተጠቅመናል።)

“Bible Church Men’s Society” (BCMS) በእንግሊዝ አገር በሎንደን የተቋቋመ ማኅበር ሲኾን፥ አባላቱ በአብዛኛው ከአንግሊካን ቤተ ክርስቲያን ናቸው። በኢትዮጵያ ተቋቁሞ ይሠራ የነበረው የዚህ ማኅበር ቅርንጫፍ፥ “የሠራዊተ ክርስቶስ ማኅበር” በመባል ይታወቅ ነበር። ማኅበሩ በኢትዮጵያ የ”BCMS” ቅርንጫፍ ኾኖ ይሠራ የነበረው በመንግሥት ፈቃድና ድጋፍ ሲኾን፥ በተለይ ደግሞ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋር በቅርብ በመተባበር ነበር። ይልቁንም በጎንደር ከሰሜንና በጌምድር ሀገረ ስብከት፥ በአሥመራ ከኤርትራ ሀገረ ስብከት፥ በመቀሌ ከትግራይ ሀገረ ስብከትና በሸዋ ለመዘዋወር ከሀገረ ስብከቱ ፈቃድና ስምምነት እያገኘ ሲኾን፥ በአዲስ አበባ ከመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ጋር ወዳጅና አጋር በመኾን ከፍተኛ የወንጌል አገልግሎት አበርክቷል።

“መድሎተ ጽድቅ” በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን - ክፍል ሁለት

Read in PDF
ካለፈው የቀጠለ -
“ሦስቱ የተሐድሶ ስልቶች” በ“መድሎተ ጽድቅ”
ጸሓፊው በመቅድሙ ላይ የሚያነሣቸውና ምላሽ ሊሰጣቸው የሚገቡ ሌሎቹ ፍሬ ነገሮች፥ ሦስቱ የተሐድሶ ስልቶች የተባሉት ናቸው። በቅድሚያ ተሐድሶ በሚለው ቃል ላይ በእርሱ በኩል የተሳሳቱ ምልከታዎች መኖራቸውንና የተዛቡ አስተያየቶች መሰጠታቸውን መግለጥ ያስፈልጋል። ተሐድሶ በዚህ ምድር ላይ ላለችው ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ የንስሓ ዕድል እንጂ ዐዲስ ሃይማኖት አይደለም፤ ወይም እርሱ እንደሚለው ኦርቶዶክስን ፕሮቴስታንት የሚያደርግ እንቅስቃሴ አይደለም። ተሐድሶ፥ እግዚአብሔር በገዛ ደሙ የዋጃት ቤተ ክርስቲያኑ ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ እንድትገኝለት የሚያደርግበት የተቀደሰ አሠራሩ ነው (ሐ.ሥ. 20፥28፤ ኤፌ. 5፥25-27)። ይኹን እንጂ እርሱ ተሐድሶን እኛ ለመፍጠር እየሞከርነው ያለ ዐዲስ ሃይማኖት አድርጎ ያቀርባል (2007፣ ገጽ 33)። በተጨማሪም ራሳችንን ተሐድሶ ብለን እንደምንጠራና ቃሉ (ተሐድሶ) መጠሪያ ስማችን እንደ ኾነ አድርጎ ጽፏል (ዝኒ ከማሁ፣ ገጽ 12)።
ተሐድሶ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሚታወቅና ሲሠራበት የቈየ የተለመደ ቃል ነው። ይልቁንም የራሷን ኢትዮጵያዊ ፓትርያርክ መሾሟን ተከትሎ ያ ክሥተት “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን መታደስ” ተብሎ ተጠርቷል። ከዚያ ወዲህ ባሉ ዓመታትም በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ በርካታ ተሐድሶኣዊ እንቅስቃሴዎች ተደርገዋል፤ ውጤቶችም ታይተዋል። በየልሳኖቿም ተሐድሶን የተመለከቱ ጽሑፎች ይወጡ ነበር። በተለይ ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ፓትርያርክ ከኾኑ ወዲህ በርካታ ተሐድሶኣዊ እንቅስቃሴዎች እንደ ነበሩና በርካታ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ፊት የሚያራምዱ ተግባራት እንደ ተከናወኑ ይታወቃል። ይህን በሚመለከት በጮራ ቊጥር 41 ላይ ከቀረበው ጽሑፍ ውስጥ የሚከተለውን መጥቀስ ለዚህ ጽሑፍ አንባብያን ይረዳል ብለን እናምናለን። 
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ፓትርያርክ ኾነው ሲሾሙ በብዙዎች ዘንድ ተስፋ የተደረገው፥ በሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ እየታየ የነበረው ተሐድሶ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ዘንድ እውን እንደሚኾን ነበር። ፓትርያርክ ኾነው በተሾሙ ጊዜ የዛሬዪቱ ኢትዮጵያ የተሰኘው አንጋፋ ጋዜጣ እንዲህ ብሎ ነበር፤ ‘የሌሎች አገሮች አብያተ ክርስቲያኖች እንደ ታደሱ ኹሉ የእኛም እንደ ዘመኑ መራመድ ይኖርባታል። የዐሥራ ዐምስተኛው ክፍለ ዘመን ሰዎች አስተሳሰብና የኻያኛው ክፍለ ዘመን ፍልስፍና በጣም የተራራቀና የተለያየ ስለ ኾነ፥ ሊያሳምን በሚችል በዐዲስ ዘዴ መቅረቡ የተሻለ ውጤት ያስገኛል። ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ይህን ኹሉ በማመዛዘን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በመንፈስ፣ በአሠራር፣ በአስተሳሰብና በአፈጻጸም የታደሰችና የዘመኑን ሥርዐት የተከተለች እንደሚያደርጓት ከፍተኛ ኀላፊነት ይጠብቃቸዋል’ (1963፣ ገጽ 2)።
ካለፉት ስድስት ዐሥርት ዓመታት በላይ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልሳን ኾኖ የሚያገለግለው ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ፥ ከ1960ዎቹ መጨረሻ አንሥቶ እስከ መስከረም 1982 ዓ.ም. ድረስ የተሐድሶ ዐምድ ነበረው። የዐምዱ ስያሜ በመጀመሪያ ‘ለተሐድሶ ዓምድ ለውይይት’ የሚል ነበር። በኋላ ‘ተሐድሶ ዐምድ ለውይይት’ ኾኗል። በዚህ ስያሜ እስከ ነሐሴ 1979 ዓ.ም. ድረስ ቀጥሏል። ከዚያ እስከ መስከረም 30/1982 ዓ.ም. ድረስ ‘የተሐድሶ ዐምድ ለውይይትና ለትምህርት’ ተብሎ ቀጥሎ የነበረ ሲኾን፥ ከዚያ ወዲህ ግን ዐምዱ ቀርቷል። የቀረበት ምክንያት የቤተ ክርስቲያቱ ተሐድሶ ተጠናቆ ነው በማለት ይኹን፥ ወይም ወቅቱ ከአስተዳደራዊ ተሐድሶ በላይ፥ ወሳኙ መንፈሳዊ ተሐድሶ እየመጣ የነበረበት ወቅት ስለ ኾነ፥ ያን በመፍራት ይኹን የታወቀ ነገር የለም። ከዚያ ወዲህ ግን ቀድሞ በበጎ ይታይና ለቤተ ክርስቲያኒቱ አስፈላጊነቱ ታምኖበት ይሞካሽ የነበረው ተሐድሶ፥ ፀረ ተሐድሶ ዐቋም ባላቸው ወገኖች፥ መጥፎ ገጽታን እንዲላበስና እንዲጠላ ተደርጎ ብዙ ስለ ተነገረበትና በሌሎችም ምክንያቶች አንዳንዶች ዛሬም ተሐድሶ የሚለውን ስም በበጎ ጎኑ አይመለከቱትም።

“መድሎተ ጽድቅ” በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን - ክፍል አንድ

መንደርደሪያ
ታላቁ ሊቅ አለቃ መሠረት ስብሐት ለአብ “ስምዐ ጽድቅ ብሔራዊ” በተባለውና መሠረታውያን የኾኑ የክርስትና ትምህርቶችን በእግዚአብሔር ቃል መሠረትና የጥንት አበውን ምስክርነት በመጥቀስ ባዘጋጁት መጽሐፋቸው መቅድም ላይ፥ መጽሐፉ የተጻፈበትን ምክንያት ካተቱ በኋላ እንዲህ ብለው ነበር፤
… ይህን ሁሉ ማተታችን መምህራኑ የማያውቁት ኾነው እነርሱን ለማስተማር አይደለም። ነገር ግን የዚህን ሐሳብና ምስጢር ቃለ መጻሕፍትን መመገብ የሚያዘወትሩ ሊቃውንት እያወቁት ሳለ፥ ብዛት ያላቸው መሃይምናን አያውቁትም። አያውቁምና መምህራን ለማነጽ ጠቃሚ መኾኑን ተረድተው የሚደግፉትን፥ ‘ለሕዝበ ክርስቲያንም ይረባል’ ሲሉ የሚያቅዱትን ጥልቅ አስተያየት፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ያልጸና የመሃይምናኑ አእምሮ እንደማይደርስበት የታወቀ ቢኾንም (፩ቆሮ. ፪፥፲፩)፥መሃይምናኑ ራሳቸው ስለ ሃይማኖት ያላቸው ዕውቀት ዝቅተኛ መኾኑን መዝነው ስፍራውን ይለቅቁላቸው ዘንድ ተገቢ በሚኾንበት ፈንታ፥ ሊቃውንቱን በመናፍቃን ስም ቀብተው ‘አብዝኆ መጻሕፍት ያዘነግዕ ልበ።’  የሚል የአረማዊውን የፊስጦስን ቃል እየጠቀሱ (የሐዋ ፳፮፥፳፬) ወዲያውኑ እንደ ተለመደው በሠለስቱ ምእት ሊቃውንት ወንበር ላይ ተቀምጠው ሊፈርዱባቸው እንዳይቸኵሉና በዚሁ አስገራሚ አኳኋን የቤተ ክርስቲያንዋ መሻሻል ዕድል እንዳይሰበር አሥጊ መኾኑን ብቻ ለማሳሰብ ነው። (መሠረት 1951፣ ገጽ 15 አጽንዖት የግል)
በርግጥም አለቃ ያሉት የደረሰ ይመስላል። ዛሬ ትልቁ ችግር መሃይምናኑ የሊቃውንቱን ስፍራ መንጠቃቸውና በእነርሱ ወንበር ላይ ተቀምጠው ሊቃውንቱን “መናፍቅ” የሚል ስም ቀብተው ለመፍረድ መቸኰላቸው ነው። ይህም እርሳቸው እንዳሉት የቤተ ክርስቲያንን መሻሻል ወደ ኋላ የሚጐትት እንዳይኾን ያሠጋል። በዚህ አጋጣሚ ሌላውን ቀድሞ መናፍቅ ማለት አማኝ ለመኾን ማረጋገጫ እንዳልኾነ፥ በዚህ መንገድ መናፍቅ በመባልም መናፍቅ መኾን እንደሌለ መግለጥ እንወዳለን።  

ለዚህ ጽሑፍ መነሻው ያረጋል አበጋዝ የተባለ ዲያቆን “መድሎተ ጽድቅ” በሚል ርእስ የጻፈውና አሳትሞ መጋቢት 2007 ዓ.ም. ለገበያ ያቀረበው መጽሐፍ ነው። መጽሐፉ ተሐድሶኣዊ አገልግሎት ላይ ያተኰሩትን፦ “ስምዐ ጽድቅ ብሔራዊ”ን፥ “ጮራ መንፈሳዊ መጽሔት”ን፥ የተቀበረ መክሊት”ን፥ “የለውጥ ያለህ!!!”ን እና ሌሎችንም የሥነ ጽሑፍ ውጤቶች በመተቸት የተዘጋጀ ነው። ጸሓፊው በእነዚህ ሥራዎች ላይ ትችት ለማቅረብ ሲነሣ፥ ዝም ብሎ እንዳልተነሣና እነዚህ ሥራዎች በሕዝቡ ውስጥ ያሳደሩት ተጽዕኖ ቀላል አለ መኾኑን ስለ ተገነዘበ እንደ ኾነ እንረዳለን። እርሱ ግን፥ የተቻቸው መጽሔትና መጻሕፍት ውጤት እንዳልተገኘባቸው አስመስሎ ቢጽፍም፥ እውነታው እንደዚያ እንዳልኾነና እርሱንም ይህን መጽሐፍ እንዲጽፍ ግድ እንዳለው መካድ አይቻልም። ጽሑፎቻችንን ተችቶ ሲጽፍ፥ በአንድ በኩል እኛ ተሐድሶ ያስፈልጋቸዋል ብለን የገለጥናቸውን ትምህርቶች በመደገፍ፥ በቤተ ክርስቲያን ዐውደ ምሕረትም ኾነ በማኅበሩ ውስጥ ለመናገር የማይደፍራቸውን እውነቶች፥ እነዚህን የጽሑፍ ሥራዎች ተተግኖና ‘ቤተ ክርስቲያን የማትለውን ትላለች ይላሉ’ የሚል ምክንያት በመስጠት በነጻነት ለመግለጥ ሰፊ ዕድል እንዳገኘ ተገንዝበናል።
መጽሐፉን ስንመለከተው በአንድ በኩል ዛሬ አብዛኛው ሰው የማያውቀውንና የማያምነውን፥ ብዙዎች የቤተ ክርስቲያን ልጆችም “መናፍቅ”፥ “ተሐድሶ” እየተባሉ የተወገዙበትንና ዛሬም የሚወገዙበትን እውነት የኾነውን ትምህርት እውነተኛነት አጽድቆ የጻፈበት ኹኔታ ስለሚታይ፥ ይህን ገጽታውን እንደ ተሐድሶኣዊ ዐቋም ወስደንለታል። በአንጻሩ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት የሌላቸውንና ከጊዜ በኋላ የተፈጠሩ የስሕተት ትምህርቶችንና ልምምዶችን በግድ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ለማድረግ የታገለበት ኹኔታም ስለሚስተዋል፥ ያን ዐቋሙን ፀረ ተሐድሶኣዊና ኢመጽሐፍ ቅዱሳዊ መኾኑን ተረድተናል። በዚህ ምላሻዊ ጽሑፍ እነዚህን የተለያዩ ዐቋሞች በየፈርጁ ለማቅረብና ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት እንሞክራለን።