Sunday, June 25, 2017

የሰራዊተ ክርስቶስ ማኅበርን የአገልግሎት ታሪክ የያዘ መጽሐፍ ተመረቀ

ከሰራዊተ ክርስቶስ ማኅበር ሚስዮናውያት አንዷ በነበሩት ዶሪስ ቤንሰን፣ “The Most Valuable Thing: The Word at Work in Ethiopia” ተብሎ በእንግሊዝኛ የተጻፈውና ወደ ዐማርኛ “ከሁሉ የበለጠ ዋጋ ያለው:- የእግዚአብሔር ቃል በሥራ ላይ በኢትዮጵያ” ተብሎ የተተረጐመው መጽሐፍ በርካታ የአገልግሎቱ የቀድሞ አባላትና ተሳታፊዎች በተገኙበት ሠኔ ፲፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም. በኢትዮጵያ ሥነ መለኮት ድኅረ ምረቃ ት/ቤት አዳራሽ ተመረቀ።

            በጸሎተ ወንጌል የተከፈተው የምረቃው ሥነ ሥርዐት ዝማሬዎችም የቀረቡበት ሲሆን፣ ቃለ ወንጌልም ተሰብኮበታል። የማኅበሩን አገልግሎት በተለይ ከመጽሐፉ ደራሲት ጋር በተገናኘ ቅኝት ያደረገ ጽሑፍም የመርሐ ግብሩ አካል የነበረ ሲሆን፣ በመጽሐፉ ላይ የተዘጋጀ ዳሰሳዊ ጽሑፍም ቀርቧል። በመጽሐፉ ላይ የታተመው ቀዳሚ ቃልም በንባብ ተሰምቷል። ቀዳሚ ቃሉ አንድ ታሪክ ሳይዛባና እውነተኛነቱ ተጠብቆ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ በተለይ ቤተ ክርስቲያን ትልቅ ኀላፊነት እንዳለባትና በሚታወቀው ታሪክ ላይ ሌሎች ሲዋሹ እውነተኛ ምስክር ሆና አለመቅረብ ትልቅ ትዝብት ላይ እንደሚጥላት አስረድቷል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በሰራዊተ ክርስቶስ ማኅበር ታሪክ ላይ የተፈጸመውን ታሪክን አዛብቶ የማቅረብ ክፉ ሥራ ይህ ከእንግሊዝኛ ወደ ዐማርኛ የተመለሰውና ለምረቃ የበቃው መጽሐፍ እንደሚያስተካክለው ተስፋ አድርጓል። አክሎም መጽሐፉን ማስተርጐምና ማሳተም ያስፈለገበትን ምክንያቶች ሲያብራራ፥

Thursday, June 15, 2017

የጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ፳፭ ዓመት የብር ኢዮቤልዩ በዓል በታላቅ መንፈሳዊ ሥነሥርዐት ተከበረ

በፈቃደ እግዚአብሔር በታላቁ ሊቅ አለቃ መሠረት ስብሐት ለአብ አሰባሳቢነት በተመሠረተው ማኅበረ በኵር ከነሐሴ 1983 ዓ.ም. አንሥቶ ስትታተምና ስትሠራጭ ላለፉት ፳፭ ዓመታት የዘለቀችውና ለብዙዎች የወንጌል ብርሃንን ስትገልጥ የቈየችው የጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ፳፭ኛ ዓመት የብር ኢዮቤልዩ በዓል ግንቦት ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም. በኢትዮጵያ ሥነ መለኮት ድኅረ ምረቃ ት/ቤት አዳራሽ የአገልግሎቱ አባላትና ደጋፊዎች፣ ጥሪ የተደረገላቸውም ወገኖች በተገኙበት ለልዑል እግዚአብሔር ክብርን በመስጠት ተከበረ።


በዚህ የመጽሔቷ የ፳፭ ዓመታት የአገልግሎት ጕዞ በተዘከረበት በዓል ላይ ልዩ ልዩ መንፈሳውያን መርሐ ግብሮች የቀረቡ ሲሆን፣ ማኅበሩን ለመሠረቱና እዚህ ላደረሱ አባቶች ዕውቅናም ተሰጥቷል። ጮራ መጽሔት ላይ ያተኰረ ዳሰሳም የቀረበ ሲሆን፣ ለዚህ በዓል የተዘጋጀውና በጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ላይ በተከታታይ ሲወጣ የነበረው የመሠረተ እምነት ዐምድ ተከታታይ ጽሑፎች ስብስብ ቅጽ አንድ መጽሐፍም ታትሞ ተመርቋል። መጽሐፉ በአሁኑ ጊዜ በመንፈሳውያን መጻሕፍት መሸጫ መደብሮች አማካይነት በመሠራጨት ላይ ይገኛል።



የመጽሔቷን አገልግሎት ለማጠናከርና ለማስፋት በተያዘው ዕቅድ መሠረትም የጮራ መጽሔት የአባልነት ቅጽና መታወቂያ ተዘጋጅቶ በዕለቱ የተዋወቀ ሲሆን፣ የጮራ አንባብያንና አገልግሎቱን መደገፍ የሚፈልጉ መሙላትና አባል መሆን ጀምረዋል። ወደፊትም በአገር ውስጥና በውጭ አገር ያሉ የአገልግሎቱ ደጋፊዎች የመጽሔቱ አባል እንዲሆኑ ጥሪ ቀርቧል። በዕለቱ የቀረቡ ጥናታዊና ዳሰሳዊ ጽሑፎች፣ የአባልነቱም ቅጽ  እንደ አስፈላጊነቱ በቀጣዩ ጮራ ዕትም እንደሚቀርቡ ይጠበቃል።