Monday, November 24, 2014

አለቃ ነቅዐ ጥበብ

በደቂቀ እስጢፋኖስ መንፈሳዊ ኮሌጅ አዳራሽ ውስጥ በተዘጋጀው የመዘምራን ጉባኤ ለሚታደሙ ዘማርያንና ዘማርያት፥ እንዲሁም ለሌሎች ታዳሚዎች በመዝሙር ላይ ትምህርት እንዲያቀርቡ በተቀጠረው ቀን አለቃ ነቅዐ ጥበብ ወደ ስፍራው የደረሱት በሰዓቱ ነው። አዳራሹ በሰው ግጥም ብሎ ሞልቷል። አብዛኛው ታዳሚ ለመስማት ብቻ ሳይኾን በመዝሙር ላይ አለኝ የሚለውን ጥያቄ ለመጠየቅ ተዘጋጅቶ የመጣ ነው የሚመሰለው። አለቃ ስለ መዝሙር ምንነት፥ ስለ ይዘቱ፥ መዝሙር መቅረብ ያለበት ለማን እንደ ኾነና ስለ መሳሰለው ኹሉ ትምህርት ለመስጠት ዝግጅታቸውን አጠናቀዋል።

ጉባኤው በጸሎት ከተከፈተና ሊቀ መዘምራን ያሬድ በጆሮ ሲንቈረቈር ለነፍስ ትልቅ ርካታን በሚሰጠው መልካም ድምፃቸው ኹለት እግዚአብሔርን የሚወድሱና ምእመናንን ለአምልኮ የሚቀሰቀሱ ዝማሬዎችን ካቀረቡ በኋላ፥ የመድረኩ መሪ አለቃን ወደ መድረክ ጋበዙ። አለቃም አትሮንሱ ላይ መጽሐፍ ቅዱሳቸውንና የያዙትን ማስታወሻ ካሰቀመጡ በኋላ ለጉባኤው ሰላምታ ሰጡ። በመቀጠልም ለዚህ ጉባኤ በመዝሙር ዙሪያ ትምህርት እንዲያቀርቡ ስለ ተሰጣቸው ዕድል የጉባኤውን አዘጋጆች በማመስገን በቀጥታ ወደ ትምህርታቸው ዐለፉ።

Thursday, November 6, 2014

ርእሰ አንቀጽ

“ንፈቅድ ንርአዮ ለእግዚእ ኢየሱስ - ጌታ ኢየሱስን ልናይ እንወዳለን” (ዮሐ. 12፥21)
ከግሪክ ወደ ኢየሩሳሌም ለፋሲካ በዓል መጥተው የነበሩ የግሪክ ሰዎች ለሐዋርያው ፊልጶስ ያቀረቡት ሐሳብ ነው። ፊልጶስም ለእንድርያስ ነግሮት ኹለቱም ለኢየሱስ መጥተው የሰዎቹን መሻት አወሩለት። ጌታም፥ “የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ ሰዓቱ ደርሶአል። እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች፤ ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ ታፈራለች” አለ። በዚህ መስተጋብር ውስጥ በተለይ ኢየሱስን ማየት የሚፈልጉ ሰዎችንና ለእነርሱ ኢየሱስን ማሳየት የቻሉ አገልጋዮችን መመልከት እንችላለን።

ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ኢየሱስን የሚፈልጉና ኢየሱስን ከፈላጊዎቹ ጋር የሚያገናኙ ምን ያኽል ናቸው? የሚለውን ጥያቄ ማንሣት ይኖርብናል። በዚህ ዘመን በቤተ ክርስቲያን እየታየ ያለው አንዱ ችግር፥ ጌታ ኢየሱስን የሚፈልግ ምእመንና እርሱን የሚያሳይ አገልጋይ ቍጥር እየተመናመነ መምጣቱ ነው። ርግጥ የምእመናን የልባቸው መሻትና የነፍሳቸው ጥያቄ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ብዙዎቹ አገልጋዮች ግን ዕረፍተ ነፍስ ወደ ኾነው ጌታ ምእመናኑን ማድረስ ሲገባቸው ወደ ራሳቸው ይስቧቸዋል። በዚህ ምክንያት ምእመናን የክርስቶስ ተከታዮች ሳይኾኑ የእነርሱ ተከታይና አድናቂ እንዲኾኑ፥ ክርስቶስን ሳይኾን እነርሱን እንዲመለከቱ፥ የሕይወታቸው ዋና ምሳሌም ክርስቶስ ሳይኾን አገልጋዮቹ እንዲኾኑ በማድረግ፥ ኢየሱስን ፈልገው የመጡትን ምእመናን ወደ ኢየሱስ ሳያደርሷቸው እነርሱ ዘንድ በማስቀረት የእነርሱ ሎሌ ያደረጓቸው አገልጋዮች ጥቂቶች አይደሉም። 

Sunday, October 5, 2014

ማስታወቂያ

ጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ቍጥር 46 ለንባብ በቃ


ርእሰ አንቀጽ፦
“ኢየሱስን ልናይ እንወዳለን” በሚል ርእስ የቀረበው ርእሰ አንቀጽ ኢየሱስን ማሳየት ትተው ራሳቸውን የሚያሳዩትን አገልጋዮችና ኢየሱስን ማየት ትተው አገልጋዮችን እየተመለከቱ የሚመላለሱትን ሁሉንም ኢየሱስን አሳዩ ወደ ኢየሱስም ተመልከቱ ይላል፡፡

መሠረተ እምነት፦
ኢየሱስ ክርስቶሰ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ በሚል ርእስ ሲቀርብ የነበረው ተከታታይ ትምህርት የመጨረሻ ክፍል “ኢየሱስ መካከለኛ ነው ማለት ሥጋ ወደሙ መካከለኛ ነው ማለት ነው” የሚለውን የአንዳንዶች አመለካከት በመጽሐፍ ቅዱሰ የመረመረበትን ጽሑፍ አቅርቧል፡፡

ጥያቄዎቻችሁና መልሶቻቸው፦
በዚህ ዐምድ ደግሞ ስለ ጥንተ አብሶ በሊቃውንት መካከል ያለውን ክርክር መሠረት ያደረገ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡

አለቃ ነቅዐ ጥበብ፦
በመዝሙር ላይ እየታዩ ያሉትን ችግሮች በተመለከተ የሰጡትን ትምህርትና በትምህርታቸው ላይ የተደረገውን ውይይት ይዟል፡፡

ታላላቅ መንፈሳውያን ቃላት
ስለክርስቲያናዊ ኅብረት ምንነት መሠረተ ሐሳብና ተመሳሳይ ጕዳዮች መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርት አቅርቧል፡፡

ሌሎችም ጽሑፎችን ይዛለች፤ መጽሔቷን እንዲያነቡ ስንጋብዝ በመንፈሳዊና ተሐድሶኣዊ መልእክቶቿ እንደሚጠቀሙ ተስፋ እናደርጋለን፡፡

ዝግጅት ክፍሉ

Sunday, September 7, 2014

አለቃ ነቅዐ ጥበብ

ትረካ፡- ከነቅዐ ጥበብ

በቅርቡ ወደ ርእሰ ሕይወት መድኀኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን የጕዞ መርሐ ግብር ተዘጋጅቶ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ ለብዙ ዓመታት በተከፈለ መንፈሳዊ ተጋድሎ ከተለያዩ የስሕተት ትምህርቶችና ከመናፍስት አሠራሮች ነጻ የወጣና ምንም ያልተቀላቀለበት ንጹሕ ወንጌል የሚሰበክበት፣ ያልተቀያየጠ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚፈጸምበት ደብር ነው፡፡ ደብሩን የሚያውቁት በዚያ ያሉ ወንድሞችንና እኅቶችን ለመጐብኘትና ከእነርሱ ጋር መንፈሳዊ ነገርን ለመከፋፈል÷ ዝናውን የሰሙት ደግሞ የተባለው እውነት መሆኑን ለማረጋገጥ የጕዞው እድምተኞች ሆነዋል፡፡
  
አለቃ ነቅዐ ጥበብና ከደቀ መዛሙርቶቻቸው ጥቂቶች÷ እንዲሁም ወደ ስፍራው ለመሄድ የተዘጋጁ ሌሎች ወገኖችም ማልደው በስፍራው ተገኝተዋል፡፡ ወደሚጓዙበት አውቶቡስ ከገቡ በኋላ ጕዞ ከመጀመሩ በፊት÷ ቀሲስ ፍሬ ጽድቅ ጕዟቸውን ለታመነው ፈጣሪ ለእግዚአብሔር በጸሎት ዐደራ ሰጡና ጕዞው ቀጠለ፡፡

Monday, August 11, 2014

መሠረተ እምነት

Read PDF;- Meserete Emnet
ከነቅዐ ጥበብ
ባለፈው ዕትም ስለ መካከለኛነቱ ራሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረውን፥ በተግባርም እየጸለየ፣ እየለመነና እየማለደ ያሳየውን፥ በዝርዝር ተመልክተናል። አብም፣ ወልድም፣ መንፈስ ቅዱስም ይማልዳሉ የሚል ንባብ በመጽሐፍ ቅዱስ አለና፥ ሦስቱም ይማልዳሉ ከተባለ ወደ ማን ነው የሚማልዱት? በሚል አንዳንዶች ለሚያነሧቸው ክርክሮችም መልስ ለመስጠት ተሞክሯል።

የዚህን ትምህርት እውነተኛነት ለማረጋገጥ ከራሱ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በላይ ማንም ሊናገር አይችልም። ከመጽሐፍ ቅዱስ በላይም ሌላ ምስክር አይኖርም። ይሁን እንጂ ይህ ጌታችን ያስተማረው፣ ሐዋርያትም ከእርሱ ተቀብለው ያስተላለፉት እውነተኛ ትምህርት፥ ከእነርሱ በኋላ በተነሡ አበው ዘንድም የታወቀ መሆኑን ማሳየት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል። ይህን የምናደርገው የእነዚህ አበው ምስክርነት በመጽሐፍ ቅዱስ ከተመዘገበው የጌታችን ትምህርት፣ ከእርሱ ተቀብለው ሐዋርያት ከሰጡትም ምስክርነት የሚበልጥ ምስክር ሆኖ አይደለም። ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን ብቸኛ መካከለኛ ነው የሚለው ትምህርት “እንደ ውሃ ፈሳሽ፣ እንደ እንግዳ ደራሽ” በድንገት ብቅ ያለ ዐዲስ ትምህርት ሳይሆን፣ ከጥንት የነበረ፣ በአበውም ትምህርት ውስጥ በስፋት የተንጸባረቀ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርት መሆኑን ለማሳየትም ጭምር ነው።

Sunday, June 1, 2014

አለቃ ነቅዐ ጥበብ

የጥያቄና መልስ ጊዜ

ሥርዐተ አምልኮው እንደ ተፈጸመ፥ ለጥያቄዎች መልስ የሚሰጥበት ጊዜ መሆኑን ዲያቆን ምስግና እንዳስታወቀ፥ አለቃ ነቅዐ ጥበብ የተመደበላቸውን ስፍራ ያዙ፡፡ የዛሬው ጥያቄና መልስ በምን ርእስ ላይ እንደሚያተኵር አለቃ ሲጠይቁ፥ ከሳምንታት በፊት ስለ ምልጃ ከተማርን በኋላ ቀሪውን በሌላ ጊዜ እንመለስበታለን ተብሎ እንደ ነበረ ዲያቆን ምስግና አስታወሳቸው፡፡ አለቃም መነጽራቸውን ካስተካከሉና መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ካመቻቹ በኋላ “መልካም” አሉ፡፡ “መልካም ባለፈው ጊዜ በሐዲስ ኪዳን ተገቢ ሊቀ ካህናት፥ ነቢይ፥ ንጉሥ፥ መካከለኛ ሆኖ የተሾመው፤ ሰውም እግዚአብሔርም የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ እንደ ሆነ የሚናገሩትን ጥቅሶች ከመጽሐፍ ቅዱስ እያወጣን ተመልክተን ነበር፡፡ በጥቅሶቹም አስረጅነት በመሐላ የተሾመው፥ ክህነቱ የማይሻረው ዘላለማዊው ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ የመሥዋዕት ማቅረቡን ሥራ ጨርሶ በአብ ቀኝ ተቀምጦ ባለበት ጊዜም እያማለደን መሆኑን የሚያስጨብጥ ግንዛቤ አግኝተን እንደ ነበረ ይታወሳል” በማለት ጀመሩ (ጮራ ቍ. 4 እና 5)፡፡

ለሚቀጥለው ሐሳብ መግቢያ የሚሆነውን ሲያብራሩም እንዲህ አሉ፤ “የእስራኤል ልጆች ለእግዚአብሔር የተለየ ሕዝብ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ የቃል ኪዳን ማኅተም ይሆን ዘንድ የእንስሳ ደም ተረጭቶባቸው ነበር (ዘፀ. 24፥6-8)፡፡ ደም ሕዝቡ የእግዚአብሔር፥ እግዚአብሔርም የሕዝቡ ለመሆናቸው ጽኑዕ የትስስርና የውርርስ ቃል ኪዳን ማረጋገጫ ነው፡፡ ሆኖም ሕዝቡ በተለያዩ መንገዶች ቢበድሉ በመቅሠፍት እንዳይቀጡና የእግዚአብሔር ሕዝብነታቸውን ዐድሰው እንዲኖሩ የመሥዋዕት ሕግ ተደነገገላቸው፡፡ እስራኤላዊው የእግዚአብሔርን ሕግ ቢተላለፍ የኀጢአት ደመወዝ ሞት ነውና ሞት የሚያስፈርድበትን ኀጢአቱን የሚሸከምለትንና በምትኩ ይሞትለት ዘንድ የሚሠዋለትን እንስሳ ወደ መገናኛው ድንኳን መውሰድ ነበረበት፡፡ ሊቀ ካህናቱ ቢበድል (ዘሌ. 4፥1-12)፥ ማኅበሩ ቢበድል (ዘሌ. 4፥13-21)፥ የማኅበሩ መሪ ቢበድል (ዘሌ. 4፥22-26)፥ የማኅበሩ አባል ቢበድል (ዘሌ. 4፥27-35) እንደ ታዘዘው መፈጸም ነበረባቸው፡፡

Thursday, May 1, 2014

አለቃ ነቅዐ ጥበብ

Read in PDF:- Aleka nekeatebebe
አለቃ ነቅዐ ጥበብና አገልግሎታቸው

ከነቅዐ ጥበብ

የአለቃ ነቅዐ ጥበብ አገልግሎት ከእልፍኛቸው ከወጣ ሰንብቷል፡፡ የወንጌል አገልግሎታቸው ለቤተ ሰብ ብቻ መሆኑ ቀርቶ የአካባቢውን ኅብረተ ሰብ የሚያቅፍ ሆኗል፡፡ በቤተ ክርስቲያን፥ በገበያ፥ በዕድር ስብሰባ፥ በልዩ ልዩ ሸንጎ ሁሉ የአለቃ ነቅዐ ጥበብ አገልግሎት ዜና ተስፋፍቶ ይወራል፡፡ “ጠበል ይረጫሉን?” አይ የለም የሰውን ውስጣዊ አካል ማየ ሕይወት በሆነ በእግዚአብሔር ቃል ይረጫሉ፥ ያጥባሉ እንጂ!” የሚለው ጥያቄና መልስ ከሕዝብ ለሕዝብ ሆኗል፡፡

“ኤጭ! ከአያት፥ ከቅድም አያት የወረስነውን ባህለ ሃይማኖታችንንና አድባራችንን፥ አውሌያችንን፥ ጨሌያችንን… አስማምተን ይዘን እንደ ቈየን መቀጠል ይበጃል እንጂ ከሰልባጅ ጋር የመጣ መጽሐፍ ቅዱስ አያዋጣንም” አለ ተቈርቋሪ መሳዩ የደብተራ ምንተስኖት ልጅ፡፡

Tuesday, April 22, 2014

ክርስትና በኢትዮጵያ

የእግዚአብሔር መንግሥት ታሪክ

ከነቅዐ ጥበብ
ካለፈው የቀጠለ

Read In PDF

ዐሥራ ሦስተኛ - የፍሬምናጦስ ሌሎች ሥራዎች

በፍሬምናጦስ ትጋት፥ በኢትዮጵያ በተቋቋመችው የእግዚአብሔር መንግሥት ወይም ማኅበረ ጽዮን ሰማያዊት ውስጥ በዘመኑ ከተፈጸሙት ድንቅ ሥራዎች መካከል ሳይመዘገቡ የታለፉ፥ ተመዝግበው ከነበሩትም በቅብብሎሽ (በትውፊት) እንኳ ዘመናትን አቋርጠው ከእኛ ዘንድ ሳይደርሱ ከጊዜ ርዝመትም ከሁኔታዎች መለዋወጥም የተነሣ በዘመናት እርከናት ላይ እየወደቁ የተረሱና እንዳልነበሩ የሚቈጠሩ እጅግ ጠቃሚ የሥራ ውጤቶች በብዛት ሊኖሩ እንደሚችሉ ይታሰባል፡፡ የሚታወሱት ግን በጣም ጥቂቶች ናቸው፡፡ ከእነዚህ መካከል ጥቂቶቹ የሚከተሉት እንደ ሆኑ ይታመናል፡፡

1.    መካሪ፥ አበ ነፍስ፥ ወይም አበ ንስሓ መመደብ

በኢትዮጵያ ክርስትናን የተቀበለው ሕዝብ እንደ ማንኛውም ሌላ ሕዝብ ኑሮው የተመሠረተበትን የዕለት ተዕለት ሥራ የእደ ጥበብ፥ የግብርናና የንግድ ሥራን ለመከታተል ያመቸው ዘንድ ቦታ እየመረጠ ተበታትኖ የሰፈረ በመሆኑ፥ በቅዱሳት መጻሕፍት ጠለቅ ያለ ዕውቀት እንደ ነበራቸው እንደዚያ ጊዜ ዲያቆናት፥ ቀሳውስት፥ ጸሐፍት… ትምህርተ እምነታቸውን ለማሳደግ ሁኔታው ያላመቻቸው ክርስቲያኖች፥ ብዙኃን እንደ ነበሩ በእግረ ልቡና ወደ ኋላ ተመልሶ ግምት መውሰድ ይቻላል፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም እንደ አኹኑ በየሰው እጅ የሚገቡበት ዕድል አልነበረም፡፡ የማንበብና የመጻፍም ችሎታ የጥቂት ሰዎች መታደል ብቻ ሆኖ ይቈጠር ነበር፡፡ በእነዚህና በመሳሰሉ ምክንያቶች የተፈጠረውን ችግር ለማስወገድ ከምሁራኑ መካከል በየመንደሩና በየቀበሌው መካሪና አስተማሪ አድርጎ መመደብ ጊዜያዊ መፍትሔ ሆኖ ተገኘ፡፡

Sunday, March 9, 2014

ክርስትና በኢትዮጵያ


የእግዚአብሔር መንግሥት ታሪክ
ከነቅዐ ጥበብ
ካለፈው የቀጠለ

Read In PDF

ፍሬምናጦስ  በሐዋርያዊ ስብከቱ ለመሠረታት ለማኅበረ ጽዮን ሰማያዊት ካከናወናቸው ዐበይት ሥራዎች ጥቂቱን ባለፉት ዕትሞች ተመልክተናል፡፡ በረጅም ዓመታት ጕዞ ውስጥ የሚታዩና የማይታዩ መሰናክሎችን ዐልፋ ከእኛ ዘንድ በደረሰችው የእግዚአብሔር መንግሥት ምክንያት ባለውለታችን የሆነው ሐዋርያ በአሁኑ ጊዜ ስንት የሥራው መታሰቢያዎች በስሙ ተመዝግበው እንደሚገኙ በተጠየቅን ጊዜ እኛም ጠይቀን የተሰጠንን መልስ ለጠያቂዎቻችን ነግረናል፡፡ ሆኖም አላረካቸውም፡፡ ጠያቂዎቹ ከትምህርት ተቋማት፥ ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት፥ ከመሰብሰቢያዎች (አደባባዮች) ከሐውልቶች፥ ከመንገዶች… ጥቂቱ ስሙ የሚጠራባቸውና ሥራው የሚታሰብባቸው ቢሆኑ አይበዛበትም ባዮች ናቸው፡፡ አሁን ግን የዚህኑ የደገኛውን ሐዋርያ ሥራ መግለጹን እንቀጥላለን፡፡

ስምንተኛ - ኤጲስ ቆጶስ መሾም

የኢየሱስ ክርስቶስን አዳኝነቱንና ጌትነቱን ለአይሁድም ለአረማውያንም ከሰበከ በኋላ፥ አማኞችን አሰባስቦ “ማኅበረ ጽዮን ሰማያዊት” በሚል መጠሪያ ክርስቲያናዊ ድርጅቱን እንዳቋቋመ፥ በኋላም ከምእመናን መካከል በቅዱስ መጽሐፍ ላይ በመሠረተው ትምህርተ ሃይማኖት የላቀ ዕውቀት ያላቸውን እንደየጸጋ ስጦታቸው ዲያቆናት፥ ጸሐፍት፥ ቀሳውስት በሚል የሥራ ደረጃ እንደ መደበ ተመልክተን  ነበር፡፡

Sunday, February 16, 2014

መሠረተ እምነት

ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ
ባለፈው ዕትም በዚህ ክፍል ውስጥ የዕብራውያንን መልእክት መሠረት በማድረግ የኢየሱስ ክርስቶስን መካከለኛነት ለማሳየት ሞክረናል። በተከታታይ እያቀረብን ያለነው የክርስቶስን መካከለኛነት የተመለከተው ይህ ትምህርት ከክርስቶስ ትምህርነት መጀመር እንደ ነበረበት አልዘነጋነውም፤ ሆኖም በክርስቶስ መካከለኛነት ዙሪያ ዋና መከራከሪያ ሆነው የሚገኙት መጽሐፍ ቅዱሳውያን ክፍሎች መልእክታተ ሐዋርያት በመሆናቸው፥ በዚያ መጀመሩ መልካም መስሎ ስለ ታየን ከዚያ ጀመርን። እስካሁን ያየነውና በሐዋርያት ምስክርነት ላይ የተመሠረተው የክርስቶስ የመካከለኛነቱ ትምህርት ምንጭ ራሱ ክርስቶስ መሆኑን በዚህ ዕትም ለማሳየት እንሞክራለን። ከኢየሱስ መካከለኛነት ጋር ተያይዞ መካከለኛነቱን ማስቀረት ላይቻል፥  በአንዳንድ ወገኖች ለማምታታት ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በተያያዘ የሚቀርቡ መከራከሪያዎችንም እንዳስሳለን።

የክርስቶስን መካከለኛነት ማስተዋል ከስሕተት የሚያድንና ወደ ዘላለም ሕይወት የሚያመጣ ዋና እና መሠረታዊ የክርስትና ትምህርት ነው። ይህን የትምህርት መንገድ የሳተ ሰው ፍጻሜው ጥፋትና የዘላለም ሞት ይሆናል። ምክንያቱም ያ ሰው ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሰውን ብቸኛና ቀና መንገድ ስቶ ሌላ አቅጣጫን ተከትሏልና።

Monday, January 20, 2014

የመዳን ትምህርት

ካለፈው የቀጠለ
የእማሆይ ኤልሳቤጥ ስብከት

አንዳንድ ሰዎች፥ ኢየሱስን ተቀበሉና ለተቀበሉት ሁሉ ያዘጋጀው የእግዚአብሔር ልጅነት መብት ይኑራችሁ ሲባሉ፥ ስቀድስ፥ ስወድስ የኖርኩ ክርስቲያን ነኝ፤ ወላጆቼ፥ አያቶቼ … ከክርስቲያን ቤተሰብና ዘር የተወለዱ ናቸው፤ እንዴት እንደ አረመኔ ቈጥረህ ኢየሱስን ተቀበል ትለኛለህ? ይላሉ፡፡

ከእነዚህ ጋር የወገንክ ወዳጄ ስማኝ ልንገርህ! ኢየሱስ ክርስቶስን ወላጆችህ ሲጠሩት መጽሐፍ ሲነበብ፥ ስሙን ሰምተህ፥ ታሪኩንም ዐውቀህ ይሆናል፡፡ ይህ በቤተ ክርስቲያን ታሪክም በዓለም ታሪክም የተመዘገበ ታሪካዊ እውነት ስለሆነ ታሪኩን በማንኛውም መንገድ ልታገኘው ትችላለህ፡፡ ከኢየሱስ ክርስቶስ ታሪካዊነት በላይ ተፈላጊው ጉዳይ ለአንተ የሆነልህንና ያደረገልህን ዐውቀህና አምነህ መቀበልህና በተቀበልኸውም መጠቀምህ ነው፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም መወለዱንና በዓለም ውስጥ ሲያስተምር ቆይቶ መሞቱን የዓለም ሕዝብ ሁሉ ማለት ወዳጆቹ፥ በጠላትነት የተሰለፉበት፥ ገለልተኞች የሆኑት ሁሉ ከመጽሐፉ ይረዱታል፤ ሊክዱትም አይችሉም፡፡ ነገር ግን ከኀላፊ ታሪክ ሁሉ የሚለየው ጠቃሚ ቁም ነገር ለምን መጣ? በነቢያት ትንቢት መሠረት መጣ፡፡ በሰጠው ተስፋና በገባው ቃል ኪዳን መሠረት መጣ፡፡ ከዚህ የኔ ድርሻና ጥቅም ምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ የሚሰጠው ልባዊና እውነታዊ መልስ ነው፡፡ 

Thursday, January 16, 2014

የመዳን ትምህርት

Read IN PDF
የመዳን ትምህርት ማጠቃለያ

 ከናሁ ሠናይ
ካለፈው የቀጠለ

በጥበቡ ሰማያትን የፈጠረ፥ በኀይሉም ምድርን ያጸና፥ የፈቀደውንም ሁሉ በባሕርያዊ ቃሉ ያደረገ፤ ምንም የማይሳነው ልዑል እግዚአብሔር፥ ኀጢአተኛውን የሰው ዘር ለማዳን አንድ መንገድ ብቻ ማዘጋጀቱን (ዮሐ. 14፥6) ባለፈው ዕትም አንብበናል፤ ሌላ አማራጭ የሌለው ብቸኛው መንገድም፥ የሚታመኑበትን ሁሉ ያድን ዘንድ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በኀጢአተኛ ሰው ምትክ እንዲሞት መደረጉን፡፡ ኀጢአተኛን ለማዳን ከዚህ በስተቀር ሌላ መንገድ ስላልተዘጋጀ፥ ስለሌለም፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ባንተ ምትክ ተሰቅሏል፤ ሞቷል፤ ተነሥቷል፤ የምሥራች! በሚለው የስብከት ሞኝነት የሚታመኑትን ሁሉ ከኀጢአትና በኀጢአት ምክንያት ከመጣ ቍጣ እንዲድኑ በእግዚአብሔር የመወሰኑ ርግጠኛነት በቃሉ ተደግፎ ቀርቦ አንብበናል (1ጢሞ. 1፥15)፡፡ በዛሬውም ዕትም በእግዚአብሔር ጸጋ ሰውን ስለሚያድነው ሕያው እምነትና በእምነት ለሚገኘው መዳን ምንጩ ስለ ሆነው ስለ እግዚአብሔር ጸጋ ዐጭር መግቢያ እንዲሁም ከቍ. 1 እስከ 7 በወጡት ጮራ መጽሔቶች በዚህ ርእስ ሥር በተከታታይ የቀረበውን ትምህርት ከተከታተሉት መካከል እማሆይ ማርያማዊትና ወይዘሪት ልዕልት ነቅዐ-ጥበብ እንደ ማጠቃለያ ያቀረቧቸውን መግለጫዎች እንደሚከተለው አቅርበናል፡፡

ሕያው እምነትና ዐዲስ ፍጥረት
የተሰበከላቸውን የወንጌሉን ቃል ይቀበሉ ዘንድ ጌታ እግዚአብሔር ልባቸውን የከፈተላቸውና (ሐ.ሥ. 16፥14) ቃሉን በእምነት ከልባቸው ጋር ያዋሐደላቸው እውነተኛ ክርስቲያኖች፥ “ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለው ሞት እኔ ኀጢአተኛው ልሞተው ይገባኝ የነበረ ሞት ነው፤ ትንሣኤውም በኀጢአት ምክንያት ምዉት የነበርኩ እኔ ሕያው እሆን ዘንድ፥ ዛሬ የመንፈስ ትንሣኤን ያገኘሁበት፤ በመጨረሻው ቀንም የሥጋ ትንሣኤ የሚሰጠኝን ሕያው ተስፋ የጨበጥሁበት አለኝታዬ ነው” በማለት ሲያምኑ፥ እምነታቸው ከጌታ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር የሞቱና የትንሣኤው ተባባሪ ያደርጋቸዋል (ሮሜ 6፥1-8)፡፡ ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃንም ለመዛወራቸው የሚያረጋግጥ ለውጥ ይታይባቸዋል (ቈላ. 1፥13-14)፡፡ ከዚህ የተነሣ ከሞት ወዲህ ማዶ ያለ የትንሣኤን ሕይወት እየኖሩ ነው ማለት ይቻላል (ሮሜ 8፥9-11)፡፡

Thursday, January 2, 2014

መሠረተ እምነት

Read IN PDf

(ከነቅዐ ጥበብ)

ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ለተሰኘበት ኩነቱና ወልድ ለተሰኘበት ልደቱ ተስማሚ በሆነው በመልእክተኛነት (ተፈናዊነት) እና በታዛዥነት ሥራ መደብ ተገልጾ አባቶችንና የእስራኤልን ሕዝብ በሥጋ ወደሚገለጽበት ጊዜና ስፍራ እስኪያደርሳቸው ድረስ በመንገድ መሪነትና በጠቅላይ ጦር አዛዥነት ሲሠራ (ዘፀ. 23፥20፤ 33፥14-16፤ ኢያ. 5፥13-15፤ 1ሳሙ. 17፥45) የመልአከ እግዚአብሔርን ምስያ፥ አርኪ ውሃን በማፍለቅ የዐለትን ምስያ በመንሣት (ገንዘብ በማድረግ 1ቆሮ. 10፥4) መርቷቸው የነበረ መሆኑን ባለፉት ዕትሞች (ጮራ ቍጥር 6 እና 7 አንብበናል፡፡

ከዚህም ጋር በማያያዝ በእስራኤል ሕዝብ መሪነት የተገለጸው መልአክ ፍጡር መልአክ ሊቀበለው የማይገባውን ስግደትን፥ አምልኮትን፥ ውዳሴን፥ የመቀበል መብት ያለው ኤል፥ (አምላክ - መለክ) ይሆዋ፤ (የነበረ ያለና የሚኖር) ኤልሻዳይ፥ (ሁሉን የሚችል የሚሳነው የሌለ) የሆነ መለኮታዊ ባለ ሥልጣንነቱን የሚያስጨብጡ ጥቅሶችን ማንበባችንን እናስታውሳለን (ዘፍ. 17፥1፤ 28፥1-4፤ 35፥9-15፤ ዘፀ. 3፥13-15፤ 6፥2-8)፡፡ ዛሬም በመቀጠል ኢየሱስ ክርስቶስ የአብ ቃልና ጥበብ የሆነበትንና የተባለበትን ኩነቱንና የባሕርያዊ ግብሩን መግለጫ በጥቂቱ እንመረምራለን፡፡