Wednesday, October 16, 2019

ከዓለመ መጻሕፍት


ሃይማኖተ አበው ቀደምት

“ሃይማኖተ አበው ቀደምት” የተሰኘውና በቁም ጽሑፍ ተዘጋጅቶ የተባዛው መጽሐፍ፣ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ (ኪ.ወ.ክ.) ጽፈውት ለአቶ ደስታ ተክለ ወልድ በዐደራ የሰጡትና በዶ/ር ብርሃኑ አበበ አማካይነት ምዕራብ ጀርመን ፍራንክፈርት በሚገኘው በፍሬቤንዩስ ድርጅት የታተመ መኾኑን በመጽሐፉ ላይ ደስታ ተክለ ወልድ የሰጡት መግለጫ ያስረዳል። መጽሐፉ ምንም እንኳ በቤተ ክህነት ዐማርኛ በመምህራን ቋንቋ የተጻፈ መኾኑን ስለሚገልጥ፣ አንዳንድ ታሪኮችና ጸሎቶችም በግእዝ በመቅረባቸው በቀላሉ ለመረዳት አስቸጋሪ ቢኾንም፣ ከ15 የሚበልጥ ብዙ ዐይነት ምዕላድ በማየትና በመመልከት፣ በማስተዋልና በመመርመር፣ በማነጻጸርም የተዘጋጀ በመኾኑ ከፍ ያለ ግምት የሚሰጠው ሥራ ነው። 

በውስጡም የሦስቱን ማለትም የተዋሕዶን፣ የካራንና የቅባትን ባህላተ ትምህርት ምንነት ይዟል። በዘመናቸው የትምህርት ሕጸጽና የሃይማኖት ጕድለት፣ መከራና ስደት፣ ጠብና ክርክር ከዚሁ ጋር ተያይዞ በባህለ ሃይማኖት ልዩነት ምክንያት ምላስና ዐንገት እስከ መቍረጥ የደረሰ አሳዛኝ ቅጣት የፈጸሙ ነገሥታትና የኢትዮጵያ ግብጻውያን ጳጳሳት ታሪክም የተካተተበት መኾኑን መጽሐፉ ይገልጣል።

Saturday, August 31, 2019

የዘመን ምስክር

READ PDF

አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ
ካለፈው የቀጠለ
መዝገበ ቃላት
ኪ.ወ.ክ. ሲነሡ ከስማቸው ጋር ተያይዞ በዋናነት የሚነሣው ዕውቅ ሥራቸው “መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ” ነው። የዚህ ንባቡ በግእዝ፣ ፍቺው በዐማርኛ የኾነ መዝገበ ቃላት ሥራ ጀማሪ በእርሳቸው ብርዕ፣ “በሮማውያን ዘንድ የከበሩ ትምህርት ከጥፈት ያስተባበሩ፥ በትምርታቸውም የተደነቁና የታወቁ፥ በሀገራቸው ግን እንደ ነቢያት የተናቁ እንደ ሐዋርያት የተጠቁ፥ እንደ ዮሴፍም ወንድሞቻቸው ጠልተው ተመቅኝተው ለማይረባ ዋጋ የሸጧቸው የአንኮበሩ ሊቅ” በማለት የተገለጡት መምህር ክፍለ ጊዮርጊስ ወልደ አባ ተክሌ ሲኾኑ፣ ፈጻሚው ደግሞ ኪ.ወ.ክ. መኾናቸው በመጽሐፉ ላይ ተጠቅሷል።

“ሥራን መንቀፍ በሥራ ነው እንጂ በቃል ብቻ መንቀፍ አይበቃም” የሚል ዐቋም የነበራቸው መምህር ክፍለ ጊዮርጊስ ይህን የግስ (የመዝገበ ቃላት) መጽሐፍ ለማዘጋጀት የተነሣሡት፣ ዲልማን የተባለው የውጭ አገር ሊቅ ያዘጋጀውን የግእዝ ግስ ከተመለከቱ በኋላ፣ በተለይ በሞክሼ ፊደላት (ሀሐኀ፣ ዐአ፣ ሠሰ እና ጸፀ) አጠቃቀም ላይ የታየውን ጕድለት በሥራቸው ለመንቀፍ (ትክክለኛውን ለማሳየት) ነው። ኾኖም ዲልማን የውጭ ዜጋ ኾኖ ግእዝን አጥንቶ መዝገበ ቃላት በማዘጋጀቱ ከፍ ያለ አክብሮትና አድናቆት እንደ ቸሩትም በመዝገበ ቃላታቸው ውስጥ እናነባለን። ሞክሼዎቹ ፊደላት እንደ ቀድሞው የድምፅ ልዩነት ባይኖራቸውም የመልክ ልዩነት ስላላቸውና ምስጢራቸውና ስማቸውም እንደ መልካቸው የተለያየ ስለ ኾነ ያ ተጠብቆ መጻፍ አለበት ይላሉ።

Thursday, August 29, 2019

የዘመን ምስክር


አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ
መግቢያ
በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ በተለይ የነገረ ሃይማኖት፣ የቋንቋና ሥነ ጽሑፍ፣ የባሕረ ሐሳብም (የዘመን ቍጥር) ጉዳይ ሲነሣ በጕልሕ ከሚጠቀሱት ሊቃውንት መካከል፣ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ግንባር ቀደም ናቸው። አንዳንዶች ስማቸውን በአኅጽሮት (ባጭሩ) ኪ.ወ.ክ. እያሉ ይጠራሉ። እኒህ የነገረ መለኮት፣ የሰዋስውና የመዝገበ ቃላት ሊቅ በዋናነት ነገረ ክርስቶስን አስመልክቶ በሚከተሉትና በኢትዮጵያ ቀዳሚው ኦርቶዶክሳዊ ባህለ ትምህርት በኾነውና ተቃዋሚዎቹ “ሦስት ልደት” (ጸጋ) እያሉ በሚጠሩት ባህለ ትምህርት ምክንያት በሥልጣን ላይ ያለው ቡድን በአንዳንድ ሥራዎቻቸው እየተጠቀመ ስማቸውን ግን በተገቢው መንገድ ለማንሣትና ተገቢውን ስፍራ ለመስጠት ቢቸገርም፣ ሊቅነታቸውን ግን በምንም መንገድ ሊያስተባብል አይችልም።

አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ከነገረ ክርስቶስ በተጨማሪ በአንዳንድ አስተምህሮቶችና ታሪኮች ላይም ለየት ያሉና አነጋጋሪ የሆኑ ጉዳዮችን በድፍረት ያቀርባሉ። ከዚህ የተነሣ እርሳቸውን ለማጣጣል የሚሞክሩ አንዳንድ ደፋሮች ባይጠፉም፣ እውነትን ደፍረው በመናገራቸውና እውነትን ይዘው ለብቻቸውም ቢኾን በመቆማቸው ተከታዮችና ደጋፊዎችን አላጡም። ስለ እርሳቸው ሊነገርና ሊጻፍ የሚገባው ብዙ ነገር ቢኖርም ጥቂቱንም እንኳ እንጻፍ ብንል ብዙ ይኾናል። በዚህ ጽሑፍ የገጠመንም ይኸው ነው። ለመኾኑ እኒህ ሊቅ ማናቸው? ሥራዎቻቸውስ የትኞቹ ናቸው? ለአገርና ለቤተ ክርስቲያን መታደስ ምን አበረከቱ? የሚሉትንና የመሳሰሉትን ጉዳዮች ቀጥሎ እንቃኛለን።

Tuesday, April 2, 2019

ምስባክ

“ዓሣ ከውሃ ከወጣ ነፍሱ ወጣ”
አንዳንድ ሰዎች ለወንጌል መሰል ስብከታቸው መንግሥተ ሰማያት ለማስገባት አንድ እርምጃ የሚቀር እስኪመስል ድረስ ለስብከታቸው የሚገርም ርእስ ይሰጣሉ። ወደ ስብከቱ ፍሬ ነገር ሲገባ ግን ውጤቱ አብዛኛውን ጊዜ የመኪናን ፍሬቻ መብራት ወደ ግራ አሳይቶ ወደ ቀኝ እንደ መታጠፍ ያኽል ነው፤ ወይም ወደ ቀኝ አሳይቶ ወደ ግራ እንደ መሄድ ይኾናል።

እኔና ክርስቲያን ወንድሜ (አሁን በሕይወተ ሥጋ የለም) በመንገድ ስናልፍ የምንሄድበትን ጉዳይ ትተን ይህን ስብከትማ ሳንስማ መሄድ የለብንም እንድንል ያደረገንን የስብከት ርእስ አንድ ቤተ ክርስቲያን የማስታወቂያ ሰሌዳ ላይ በትልቁ ተለጥፎ አየን። ርእሱ “ዓሣ ከውሃ ከወጣ ነፍሱ ወጣ” የሚል ነበር። ከዚያ ና እባክህ ይህን የወንጌል ቃል ተካፍለን እንሂድ፤ የሚገርም ርእስ ነው ተባብለን መልእክቱን ለመስማት ጎራ አልን። በጕጕት ስንጠብቅ የወንጌሉ ድምዳሜ “የዚህች ቤተ ክርስቲያን አባል ካልሆናችሁ ወደ መንግሥተ ሰማይ አትገቡም” የሚል ኾኖ አገኘነው። እኛም ሰባኪውን በመጨረሻ አግኝተን ማነጋገር አለብን ብለን ቈየንና አገኘነው፤ አነጋገርነውም። በተለይ ወንድሜ በሰል ያለ ሰው ነበርና እግዚአብሔርን፣ ሕዝቡንም ይቅርታ እንዲጠይቅና ከስሕተቱ እንዲመለስ አበክሮ መክሮት በሰላም ተለያየን። በእውነት ርእሱና የስብከቱ ሐተታና ድምዳሜ እንደ ወንጌሉ ቃል የተገናኙ አልነበሩም።

Monday, January 14, 2019

ዕቅበተ እምነት


"መድሎተ ጽደቅ" በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን

ክፍል አራት

ባለፉት ሦስት ተከታታይ ዕትሞችመድሎተ ጽድቅለተሰኘው መጽሐፍ ምላሽ ስንሰጥ መቈየታችን ይታወሳል። በዚህ ዕትምም ካለፈው ለቀጠለውና በጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ጽሑፍ ላይ ለተሰነዘረው መሠረተ ቢስ ትችት ምላሽ መስጠታችንን እንቀጥላለን።

በዚህ ዕትም መድሎተ ጽድቅገጽ 42 ላይ የሚገኘውና በተራ ቍጥር 1.3.3. ላይ፣ከእምነት ይልቅ በስሜት ሕዋሳት (በማየት፣ በመስማት፣ …) ላይ መመሥረትበሚለው ንኡስ ርእስ ሥር ለተጠቀሱት እንዲሁም “1.1.4 ተገቢ ያልኾኑ አባባሎችንና ጸያፍ አገላለጾችን መጠቀምበሚለው ንኡስ ርእስ ሥር ለቀረበው ሐሳብ ከዚህ እንደሚከተለው ምላሽ እንሰጣለን፦

በመጀመሪያው ንኡስ ርእስ ሥር መድሎተ ጽድቅጸሓፊ ለመተቸት የተጣጣረው፣አብርሃም በዐጸደ ነፍስ ባለበት ኹኔታ በምድር የሚደረገውን ኹሉ ያውቃል ማለት የሚታመን ቀርቶ የማይመስል ነው።” (ጮራ . 38 ገጽ 17) የሚለውን ሐሳብ ነው። 

Tuesday, January 1, 2019

ርእሰ አንቀጽ



ወሰላም በምድር - በምድር ሰላም

በኢየሩሳሌም የነገሠው የነቢዩ የዳዊት ልጅ ጠቢቡ ሰሎምን በመጽሐፈ መክብብ ውስጥ ለኹሉም ነገር ጊዜ እንዳለው በርካታ ክሥተቶችን በመጥቀስ ይናገራል። ለመወለድ፣ ለመትከል የተተከለውን ለመንቀል፣ ለመግደል ለመፈወስ፣ ለማፍረስ ለመሥራት፣ ለማልቀስ ለመሣቅ፣ ዋይ ለማለት ለመዝፈን፣ ድንጋይን ለመጣል ድንጋይን ለመሰብሰብ፣ ለመተቃቀፍ ከመተቃቀፍ ለመራቅ፣ ለመፈለግ ለማጥፋት፣ ለመጠበቅ ለመጣል፣ ለመቅደድ ለመስፋት፣ ዝም ለማለት ለመናገር፣ ለመውደድ ለመጥላት፣ ለጦርነት ለሰላም ጊዜ አለው በማለት ጠቢቡ ጊዜ በምሕዋሩ ውስጥ ልዩ ልዩ የሚቃረኑ ነገሮችን እንደሚያመላልስ ያስረዳል። በዚህ ሂደት ውስጥ የኹኔታዎች መለዋወጥ በጊዜ ቀመር የታቀበ ነው። ከዚህ ልውውጥ በስተ ጀርባም ነገሮችን የሚቈጣጠረው መጋቤ ኵሉ ወመሴስየ ኵሉ (ኹሉን የሚመግብና ደስ የሚያሰኝ)፣ ጊዜያትን የሚያመላልስና የሚያለዋውጥ አምላካችን እግዚአብሔር ነው፤ ክብር ለእርሱ ይሁን!

ለኹሉ ጊዜ አለው እንደ ተባለው፣ በለውጥ ኺደት ላይ የምትገኘው አገራችን ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ብዙ ያልተጠበቁና ያልታሰቡ ለውጦች ጊዜያቸውን ጠብቀው እየተከሠቱባት ትገኛለች። ስለዚህ ወቅቱ አገራችን ለውጡን ተከትሎ በተከሠቱ ኹኔታዎች ለለውጥ ተስፋ የተሰነቀችበት ብቻ ሳይኾን በለውጡ ሂደት ሰላሟ የደፈረሰበትም ጊዜ ነው። እየመጣ ያለውን ለውጥ ተከትሎ በብዙ ቦታዎች የሰላም መደፍረስና ሥጋት፣ የዜጎች መፈናቀል፣ በተወለዱበት፣ ባደጉበትና ንብረት ባፈሩበት ስፍራ አገሬ ብሎ የመኖር ዋስትና ማጣት፣ በሕግ ሳይኾን በመንጋ ኢፍትሓዊ ፍትሕ የሚሰጥበትና በርካታ አሳዛኝና አስከፊ ኹኔታዎች እየታዩ ነው። ከዚህ ቀደም የኾነውን ኹሉ ወደ ቦታው መመለስ አይቻልም፤ ወደ ፊት የባሰ ችግር እንዳይከሠትና እየታየ ያለው የተስፋ ጭላንጭል እንዳይጨልም ለመሥራት ግን ዕድሉ አለ።