Monday, January 20, 2014

የመዳን ትምህርት

ካለፈው የቀጠለ
የእማሆይ ኤልሳቤጥ ስብከት

አንዳንድ ሰዎች፥ ኢየሱስን ተቀበሉና ለተቀበሉት ሁሉ ያዘጋጀው የእግዚአብሔር ልጅነት መብት ይኑራችሁ ሲባሉ፥ ስቀድስ፥ ስወድስ የኖርኩ ክርስቲያን ነኝ፤ ወላጆቼ፥ አያቶቼ … ከክርስቲያን ቤተሰብና ዘር የተወለዱ ናቸው፤ እንዴት እንደ አረመኔ ቈጥረህ ኢየሱስን ተቀበል ትለኛለህ? ይላሉ፡፡

ከእነዚህ ጋር የወገንክ ወዳጄ ስማኝ ልንገርህ! ኢየሱስ ክርስቶስን ወላጆችህ ሲጠሩት መጽሐፍ ሲነበብ፥ ስሙን ሰምተህ፥ ታሪኩንም ዐውቀህ ይሆናል፡፡ ይህ በቤተ ክርስቲያን ታሪክም በዓለም ታሪክም የተመዘገበ ታሪካዊ እውነት ስለሆነ ታሪኩን በማንኛውም መንገድ ልታገኘው ትችላለህ፡፡ ከኢየሱስ ክርስቶስ ታሪካዊነት በላይ ተፈላጊው ጉዳይ ለአንተ የሆነልህንና ያደረገልህን ዐውቀህና አምነህ መቀበልህና በተቀበልኸውም መጠቀምህ ነው፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም መወለዱንና በዓለም ውስጥ ሲያስተምር ቆይቶ መሞቱን የዓለም ሕዝብ ሁሉ ማለት ወዳጆቹ፥ በጠላትነት የተሰለፉበት፥ ገለልተኞች የሆኑት ሁሉ ከመጽሐፉ ይረዱታል፤ ሊክዱትም አይችሉም፡፡ ነገር ግን ከኀላፊ ታሪክ ሁሉ የሚለየው ጠቃሚ ቁም ነገር ለምን መጣ? በነቢያት ትንቢት መሠረት መጣ፡፡ በሰጠው ተስፋና በገባው ቃል ኪዳን መሠረት መጣ፡፡ ከዚህ የኔ ድርሻና ጥቅም ምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ የሚሰጠው ልባዊና እውነታዊ መልስ ነው፡፡ 

Thursday, January 16, 2014

የመዳን ትምህርት

Read IN PDF
የመዳን ትምህርት ማጠቃለያ

 ከናሁ ሠናይ
ካለፈው የቀጠለ

በጥበቡ ሰማያትን የፈጠረ፥ በኀይሉም ምድርን ያጸና፥ የፈቀደውንም ሁሉ በባሕርያዊ ቃሉ ያደረገ፤ ምንም የማይሳነው ልዑል እግዚአብሔር፥ ኀጢአተኛውን የሰው ዘር ለማዳን አንድ መንገድ ብቻ ማዘጋጀቱን (ዮሐ. 14፥6) ባለፈው ዕትም አንብበናል፤ ሌላ አማራጭ የሌለው ብቸኛው መንገድም፥ የሚታመኑበትን ሁሉ ያድን ዘንድ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በኀጢአተኛ ሰው ምትክ እንዲሞት መደረጉን፡፡ ኀጢአተኛን ለማዳን ከዚህ በስተቀር ሌላ መንገድ ስላልተዘጋጀ፥ ስለሌለም፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ባንተ ምትክ ተሰቅሏል፤ ሞቷል፤ ተነሥቷል፤ የምሥራች! በሚለው የስብከት ሞኝነት የሚታመኑትን ሁሉ ከኀጢአትና በኀጢአት ምክንያት ከመጣ ቍጣ እንዲድኑ በእግዚአብሔር የመወሰኑ ርግጠኛነት በቃሉ ተደግፎ ቀርቦ አንብበናል (1ጢሞ. 1፥15)፡፡ በዛሬውም ዕትም በእግዚአብሔር ጸጋ ሰውን ስለሚያድነው ሕያው እምነትና በእምነት ለሚገኘው መዳን ምንጩ ስለ ሆነው ስለ እግዚአብሔር ጸጋ ዐጭር መግቢያ እንዲሁም ከቍ. 1 እስከ 7 በወጡት ጮራ መጽሔቶች በዚህ ርእስ ሥር በተከታታይ የቀረበውን ትምህርት ከተከታተሉት መካከል እማሆይ ማርያማዊትና ወይዘሪት ልዕልት ነቅዐ-ጥበብ እንደ ማጠቃለያ ያቀረቧቸውን መግለጫዎች እንደሚከተለው አቅርበናል፡፡

ሕያው እምነትና ዐዲስ ፍጥረት
የተሰበከላቸውን የወንጌሉን ቃል ይቀበሉ ዘንድ ጌታ እግዚአብሔር ልባቸውን የከፈተላቸውና (ሐ.ሥ. 16፥14) ቃሉን በእምነት ከልባቸው ጋር ያዋሐደላቸው እውነተኛ ክርስቲያኖች፥ “ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለው ሞት እኔ ኀጢአተኛው ልሞተው ይገባኝ የነበረ ሞት ነው፤ ትንሣኤውም በኀጢአት ምክንያት ምዉት የነበርኩ እኔ ሕያው እሆን ዘንድ፥ ዛሬ የመንፈስ ትንሣኤን ያገኘሁበት፤ በመጨረሻው ቀንም የሥጋ ትንሣኤ የሚሰጠኝን ሕያው ተስፋ የጨበጥሁበት አለኝታዬ ነው” በማለት ሲያምኑ፥ እምነታቸው ከጌታ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር የሞቱና የትንሣኤው ተባባሪ ያደርጋቸዋል (ሮሜ 6፥1-8)፡፡ ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃንም ለመዛወራቸው የሚያረጋግጥ ለውጥ ይታይባቸዋል (ቈላ. 1፥13-14)፡፡ ከዚህ የተነሣ ከሞት ወዲህ ማዶ ያለ የትንሣኤን ሕይወት እየኖሩ ነው ማለት ይቻላል (ሮሜ 8፥9-11)፡፡

Thursday, January 2, 2014

መሠረተ እምነት

Read IN PDf

(ከነቅዐ ጥበብ)

ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ለተሰኘበት ኩነቱና ወልድ ለተሰኘበት ልደቱ ተስማሚ በሆነው በመልእክተኛነት (ተፈናዊነት) እና በታዛዥነት ሥራ መደብ ተገልጾ አባቶችንና የእስራኤልን ሕዝብ በሥጋ ወደሚገለጽበት ጊዜና ስፍራ እስኪያደርሳቸው ድረስ በመንገድ መሪነትና በጠቅላይ ጦር አዛዥነት ሲሠራ (ዘፀ. 23፥20፤ 33፥14-16፤ ኢያ. 5፥13-15፤ 1ሳሙ. 17፥45) የመልአከ እግዚአብሔርን ምስያ፥ አርኪ ውሃን በማፍለቅ የዐለትን ምስያ በመንሣት (ገንዘብ በማድረግ 1ቆሮ. 10፥4) መርቷቸው የነበረ መሆኑን ባለፉት ዕትሞች (ጮራ ቍጥር 6 እና 7 አንብበናል፡፡

ከዚህም ጋር በማያያዝ በእስራኤል ሕዝብ መሪነት የተገለጸው መልአክ ፍጡር መልአክ ሊቀበለው የማይገባውን ስግደትን፥ አምልኮትን፥ ውዳሴን፥ የመቀበል መብት ያለው ኤል፥ (አምላክ - መለክ) ይሆዋ፤ (የነበረ ያለና የሚኖር) ኤልሻዳይ፥ (ሁሉን የሚችል የሚሳነው የሌለ) የሆነ መለኮታዊ ባለ ሥልጣንነቱን የሚያስጨብጡ ጥቅሶችን ማንበባችንን እናስታውሳለን (ዘፍ. 17፥1፤ 28፥1-4፤ 35፥9-15፤ ዘፀ. 3፥13-15፤ 6፥2-8)፡፡ ዛሬም በመቀጠል ኢየሱስ ክርስቶስ የአብ ቃልና ጥበብ የሆነበትንና የተባለበትን ኩነቱንና የባሕርያዊ ግብሩን መግለጫ በጥቂቱ እንመረምራለን፡፡