በማስተዋል ዐብራችሁ ኑሩ
የይሥሐቅን የጋብቻ ሁኔታ ለማየትና ከዚህ ጋብቻ ልንማረው የሚገባንን ትምህርት ለመገንዘብ በቅድሚያ ይሥሐቅ
ጠንካራ ሥነ ምግባርና እምነት ከነበረው ከአብርሃም የተወለደ ልጅ መሆኑን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ ይሥሐቅ የተወለደው አብራሃም በሸመገለበት
ጊዜና እምነቱ በከፍተኛ ደረጃ ከተፈተነ በኋላ ነው፡፡ “የምትወደውን አንድ ልጅህን ይሥሐቅን ይዘህ … ሂድ” ይህ ቃል አብርሃም
አንድ ልጁን ይሥሐቅን በመሥዋዕትነት እንዲያቀርብ እግዚአብሔር ለአብርሃም የተናገረው እጅግ ፈታኝ የሆነ ቃል ነው፡፡
ይኸውም አብርሃም ለይሥሐቅ የነበረውን የተለየ ፍቅር እግዚአብሔር ራሱ ያውቀው ስለ ነበረ የመሥዋዕትነቱ ጥሪ
የቀረበው አባትና ልጅ የነበራቸው ጥልቅ ፍቅር ከግምት ውስጥ ገብቶ መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ የይሥሐቅን ሕይወት በሚመለከት ከተመዘገቡት
ሁለት ጠቃሚ ታሪካዊ ድርጊቶች ውስጥ በተለይ በእግዚአብሔር ፈቃድና በአብርሃም አነሣሽነት መሥዋዕት ለመሆን ወደ መሠዊያው ቦታ ያለምንም
ተቃውሞ መሄድ መቻሉና የሚያገባትን ሚስት ፍልጎ በማግኘቱ ረገድ የታየው ሁኔታ ይሥሐቅም በበኩሉ ለአባቱ ለአብርሃም እጅግ ታማኝና
ታዛዥ እንደ ነበረ ያሳያል፡፡