Friday, January 19, 2018

ፍካሬ መጻሕፍት

“የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም!” (ዮሐ. 2፥3)
     ይህን ቃል የተናገረችው የጌታ እናት ቅድስት ማርያም ናት። የተናገረችውም በቃና ዘገሊላ ሰርግ ቤት እርስዋ፣ ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስና ደቀ መዛሙርቱ ታድመው ባሉበት፣ ለሰርጉ የተዘጋጀው የወይን ጠጅ ባለቀ ጊዜ ነው። በብዙዎች ዘንድ ይህ የቅድስት ማርያም ቃል የእርሷ “ምልጃ” ተደርጎ እየታመነበትና ስለ ምልጃዋ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ ተደርጎ እየተጠቀሰ ይገኛል።

     በአንድ ወቅት ከነበሩ የቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የመጻሕፍት ተማሪዎች መካከል አንዱ ወደ መንደር ኼዶ ከወንጌላውያን አማኞች ጋር ስለ ማርያም ምልጃ ሲከራከር ቈይቶ ወደ ኮሌጁ ይመለስና፣ ሌሎች ደቀ መዛሙርት ባሉበት ለመምህሩ ስለ ክርክራቸው ይነግራቸዋል። መምህሩም “ምን ጠቅሰህ ተከራከርህ?” ይሉታል። ደቀ መዝሙሩም “የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ኹለትን ጠቀስሁላቸው” ብሎ መለሰላቸው። እርሳቸውም “ሰው ሳይጣላ ማስታረቅ አለ ወይ? ማንና ማን ተጣልቶ ነው ይህን ስለ ምልጃ ማስረጃ ብለህ ያቀረብኸው? ሰዎቹ ከጌታ ጋር አልተጣሉ፤ ጌታ እንዲያውም የተጠራው ወዳጅ ኾኖ ነው እኮ! ስለዚህ ይህን ስለ ምልጃ መጥቀስህ ልክ አይደለም” አሉት።  

Saturday, January 6, 2018

ርእሰ አንቀጽ



መድኀኒት፥ እርሱም ክርስቶስ ጌታ ተወልዶላችኋል! ! !
            “ወመ በጽሐ ዕድሜሁ ፈነወ እግዚአብሔር ወልዶ፤ ወተወልደ እምብእሲት…” ቀጠሮው በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ልጁን ወደ ቅድስት ድንግል ማርያም እንደ ላከና እርሱም ከሕግ በታች ያሉትን ይዋጅ ዘንድ ከሕግ በታች እንደ ተወለደ የእግዚአብሔር ቃል ይናገራል (ገላ. 4፥4-5፤ ከዘፍ. 3፥15 እና ከኢሳ. 7፥14 ጋር ይነበባል)።
“ንጹሕ ይኾን ዘንድ ሰው ምንድር ነው? ከሴትስ የተወለደ ጻድቅ ይኾን ዘንድ እንዴት ይቻላል? ከርኩስ ነገር ንጹሕን ሊያወጣ ማን ይችላል? አንድ እንኳ የሚችል የለም።” (ኢዮ. 14፥4፤ 15፥14-16) ተብሎ በተነገረው መሠረት ሳይኾን፥ ከድንግል በሥጋ የሚወለደው “ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ” ይባል ዘንድ ታቀደ። ስለዚህም መንፈስ ቅዱስና አብ በቅድሚያ ወደ እርሷ በመምጣት በእግዚአብሔራዊ እኔነት (የራሱ በኾነ ምልአተ አካል) የሚታወቀውን ቃል እንድትፀንስና እንድትወልድ ከተወረሰው አዳማዊ ባሕርይ የማንጻቱንና የመቀደሱን ሥራ እንደሚያከናውኑ የምሥራች ተነገራት። እርሷም ለመልእክተኛው እንዳልከው ይኹን፤ እኔ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የማገልገል ባሪያው ነኝ አለች። ዓለምን ለማዳን እግዚአብሔር ባወጣው ዕቅድ ተስማሚነቷን በእሺታ ንግግሯ ገለጸች። (ሉቃ. 1፥26-38)።

ከፀነሰችም በኋላ በማኅፀኗ የተሸከመችው ፅንስ ለእርሷ አምላኳም መድኀኒቷም እንደ ኾነ መሰከረች፤” ወትትሐሠይ መንፈስየ በአምላኪየ ወመድኀኒየ፤ እስመ ርእየ ሕማማ ለዓመቱ” አለች። ለእርሷም ኾነ ለሌላ ሰው ኹሉ በልጇ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ካልኾነ በቀር መዳን በሌላ በማንም በኩል እንደማይገኝ ያወቀችውን አሳወቀች (ሉቃ. 1፥46-48፤ ሐ.ሥ. 4፥12)።

Tuesday, January 2, 2018

ዕቅበተ እምነት

“መድሎተ ጽድቅ” በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን  ክፍል ዐምስት

READ PDF

ጮራ ቍጥር 49 ለንባብ በቅቷል። በመጽሔቱ ላይ ከወጡ ጽሑፎች መካከል አንዱ ለ"መድሎተ ጽድቅ" የተሰጠው ምላሽ ቀጣይ ክፍል ይገኝበታል። ጽሑፉ እነሆ፥ (ይህ ክፍል በመጽሔቱ ላይ ክፍል ሦስት ተብሎ ነው የተገለጸው ምክንያቱ ደግሞ የሚስተር ዳዊት ስቶክስ ታሪክ በዘመን ምስክር ዐምድ ላይ ስለወጣ ነው)

ባለፈው ዕትም “መድሎተ ጽድቅ”፣ እኛ በመሰለን እንደምናምን አድርጎ አንባቢን ለማሳሳት ያቀረባቸው ማስረጃዎች፣ በተሳሳተና በአሻጥር መንገድ ያቀናበራቸው መኾናቸውን በበቂ ማስረጃዎች አስደግፈን ማቅረባችንን ተከትሎ፣ በርካታ አንባብያን በምላሹ መደሰታቸውን ገልጸውልናል። ለዛሬው ደግሞ ይኸው “መድሎተ ጽድቅ” በገጽ 35-42 ላይ “1.1.2. በሐሰት መናገር” በሚለው ንኡስ ርእስ ሥር እኛ በሐሰት እንደምንናገር አድርጎ የጻፈውን እንመረምራለን።
በጽሑፉ መጀመሪያ ላይ “ሌላው የተሐድሶዎች መገለጫ በሐሰት መናገር (ውሸት) ነው። ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማታምነውንና የማትቀበለውን እንደምታምን እያስመሰሉ በሐሰት መጻፍና መናገር ዋና ጠባያቸው ነው። ለአብነት የሚከተሉትን እንመልከት፦” ብሎ ከተቀበረ መክሊት ላይ የሚከተለውን ጠቅሷል፦ በሌላ በኩል እግዚአብሔር በእርሷ ታላቅ ነገርን ሊያደርግ ከአንስተ ዓለም የመረጣትና ያከበራት የጌታችን እናት ቅድስት ማርያምን ልንመለከት እንችላለን። በመልአኩ ብሥራት እንደ ተገለጠው ጸጋ የሞላባት ናት። ይህ ማለት ግን እንደ እግዚአብሔር በኹሉ ስፍራ ትገኛለች፤ ኹሉን ታውቃለች ወደሚል ድምዳሜ አያደርሰንም። … በእርግጥ በፈጣሪና ፍጡራን መካከል ያለውን የባሕርይና የዕውቀት ልዩነት ካላወቅን ትልቅ ስሕተት ውስጥ እንወድቃለን። ፍጡራንን ከፈጣሪ ጋር አስተካክለው የሚያዩ ክፍሎች ችግርም ይኸው ነው። (ገጽ 164-5)።”  (መድሎተ ጽድቅ ገጽ 38)።
የተቀበረ መክሊት በሕዝቡ ዘንድ ያለውን አመለካከትና በዚያ ላይ የተመሠረተውን ሕይወት በተመለከተ ላሰፈረው ሐሳብ “መድሎተ ጽድቅ” ምላሽ ሲሰጥም፦
“… ከንቱ የሐሰት ውንጀላ ነው” ብሏል። አስከትሎም፣ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም የምትሰጠው ክብር ግልጽና የታወቀ ነው። እርሱም መልዕልተ ፍጡራን መትሕተ ፈጣሪ ማለትም ከፍጡራን በላይ ከፈጣሪ በታች የሚል ነው። ከዚህ ውጭ ግን ‘እንደ እግዚአብሔር በኹሉ ስፍራ ትገኛለች ኹሉን ታውቃለች’ የሚል እምነትም ኾነ አስተምህሮ የለም። በኹሉ ስፍራ መገኘት (ምሉዕ በኵለሄነት) እና ኹሉን ዐዋቂነት (ማእምረ ኵሉ መኾን) የእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቦች ብቻ መኾናቸው የታወቀ ነው። ስለዚህ ቅድስት ቤተ ርስቲያን ፈጣሪና ፍጡርን አሳምራ ለይታ የምታውቅ ናት እንጂ ‘ፍጡራንን ከፈጣሪ እኩል ማድረግና ማስተካከል’ የሚለው አይመለከታትም። … እኛ ይህን የቅድስት ቤተ ክርስቲያን እምነት እየገለጽን ያለነው፣ ወደፊትም በየጉዳዩ የምንገልጸውና ምስክር የምንጠቅሰው ከመጽሐፍ ቅዱስና ከቀደምት ኦርቶዶክሳውያን አባቶች ትምህርት ስለ ኾነ እናንተም ከእነዚህ ምስክር አለን የምትሉ ከኾነ ማቅረብ እንጂ በስማ በለውና በይመስላል፣ እንዲሁም ደግሞ በግል ጸሎትና ለታሪክ፣ እንዲሁም ይህን ለመሳሰለው ተግባር ያሉትን ነገሮች በመጥቀስ አይደለም” ብሏል (ዝኒ ከማሁ)።