Monday, June 20, 2016

ምላሽ የሚያሻው የክርስቶስ ጥያቄ - ትወደኛለህን? (ዮሐንስ 21)

ይህን ጥያቄ ስናነብ ወደ አእምሮአችን በቶሎ የሚመጣው ምንድን ነው? ምናልባት ምን ዐይነት ጥያቄ ነው? ብለን እናስብ ይሆናል፤ ወይም ጥያቄው የአፍቃሪ ጥያቄ አንደሚሆን ልንገምት እንችላለን። አሊያ እንደዚህ ተብሎ ይጠየቃል ወይ? ብለን ልንጠይቅም እንችላለን። ጥያቄው ረጅም ጊዜ ዐብሮን ከኖረ ሰው፥ በጣም ከሚያውቀንና ከምናውቀው ሰው፥ ለምሳሌ፥ ከባለቤታችን ወይም ከጓደኛችን ቢመጣስ ምን ይሰማናል? ያለ ጥርጥር ምን አይቶብኝ ይሆን? ወይም ምን አይታብኝ ይሆን? ምን ሰምቶብኝ/ምን ሰምታብኝ ይሆን? የሚሉ ጥያቄዎችን ሊያጭርብን ይችላል።
ጥያቄው “አዎን እወድሃለሁ” የሚል ምላሽን ለማግኘት ወይም መወደድን ለማወቅ የተጠየቀ ጥያቄ አይደለም። ጥያቄው ከፍቅረኛ፥ ከትዳር አጋር ወይም ከጓደኛ የመጣ ሳይሆን ከጌታችንና ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ በተለይም ለጴጥሮስ የቀረበ ጥያቄ ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ በወንጌሉ በ21ኛው ምዕራፍ አንደ ዘገበልን፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ያህል “ትወደኛለህን?” ሲል ጠይቆታል።

እወድሃለሁ
“ትወደኛለህን?” የሚለው ጥያቄ ፍቅርን ለማወቅ ወይም ለማረጋገጥ የሚጠየቅ ጥያቄ ቢሆንም፥ ዮሐንስ እንደ ጻፈው ጥያቄው ከዚያ የሚያልፍ መልእክት አለው። በርግጥ ትወደኛለህን? ተብሎ ሲጠየቅ ምላሹ አልወድህም የሚል አይሆንም። በክርስቶስና በጴጥሮስ መካከል የነበረውን ግንኙነት መለስ ብለን ስናስታውስ፥ ጌታ ደቀ መዛሙርቱን በሥጋ ልለያችሁ ነው፤ ልሄድ ነው ብሎ በነገራቸው ጊዜ፥ ጴጥሮስ ‘ተለይተኸን ወዴት ትሄዳለህ? የትም ብትሄድ ዐብሬህ እሄዳለሁ፤ ሞት እንኳ ቢመጣ ከአንተ አልለይም’ ያለው ሰው ነበር (ዮሐ. 13፥36-38)። ጌታ ለጴጥሮስ ንግግር የሰጠው ምላሽ፥ ‘እንኳ ነፍስህን ልትስጠኝ፥ ዶሮ ከመጮኹ በፊት ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ’ የሚል ነበር።

ፍቅር እንዴት ይገለጣል?
እንደሚታወቀው በዓለም ላይ የፍቅር መገለጫ አንድ ዐይነት አይደለም፤ ከማኅበረሰብ ማኅበረሰብ፥ ከባህል ባህል ይለያያል። የፍቅር መግለጫ ቋንቋ፥ የጋለ ጭብጨባ፥ እንባ፥ የቃል ንግግር፥ አበባ ማበርከት፥ መተቃቀፍ፥ መጨባበጥ፥ መሳሳም ሊሆን ይችላል። ከእነዚህ በአንዱ ወይም በሌሎች መንገዶች ፍቅር ይገለጣል። ጌታ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ መላልሶ ሲጠይቀው፥ ጴጥሮስም ሦሰት ጊዜ መላልሶ እወድሃለሁ ብሎታል። እንዲሁም በኋላ ላይ ግራ የገባው በሚመስል መልክ፥ በማዘንም ጭምር እንደምወድህ አንተ ታውቃለህ ብሎታል።

Monday, February 22, 2016

ፍካሬ መጻሕፍት

ከሕፃንነትህም ጀምረህ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን፥ መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ሊሰጡህ የሚችሉትን ቅዱሳን መጻሕፍትን ዐውቀሃል። የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይኾን ዘንድ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ኹሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል” (2 ጢሞ. 3፥15-17)፡፡
አንዳንዶች ይህን ጥቅስ ሲያነቡ ወይም ሲነበብ ሲሰሙ ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ወይም ዛሬ ላይ ኾነው ከአጠቃላዩ መጽሐፍ ቅዱስ ይልቅ በአእምሮአቸው ውስጥ በቶሎ የሚከሠቱት አዋልድ መጻሕፍት ናቸው፡፡ ይህም የኾነው ጥቅሱ ስለ አዋልድ መጻሕፍት የተጻፈ ስለ ኾነ አይደለም፤ አንዳንድ ሰዎች ጥቅሱን ደግመው ደጋግመው ስለ አዋልድ መጻሕፍት እንደ ተነገረ አስመስለው በአፍም በመጣፍም ስለሚጠቅሱት ነው እንጂ፡፡ “ዓምደ ሃይማኖት” የተሰኘ መጽሐፍ ይህን ጥቅስ ይጠቅስና፥ “እንግዲህ ድርሳናትም ኾኑ ገድላት ስለ እግዚአብሔር አዳኝነት፣ ታላቅነት የሚገልጹ ስለ ኾነ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው መኾናቸው የተረጋገጠ ነው፡፡ ጳውሎስ ስል[ድ]ሳ ስድስቱን መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ተጠቀም አላለም፡፡ ገደብ ሳያደርግ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው በቅዱሳን አባቶችም ኾነ በሌሎችም ክርስቲያኖች የተጻፉትንም መንፈሳዊ መጻሕፍት አለ እንጂ፡፡” ይላል (ብርሃኑ ጎበና 1995፤ ገጽ 37)፡፡
ምንም እንኳ መጽሐፉ የጳውሎስን መልእክት በማብራራት ስም ጳውሎስ ያላለውንና ሊል ያልፈለገውን ሐሳብ፣ እንዳለ አስመስሎ ቢያቀርብም፣ በዚህ ጽሑፍ የምናብራራው የጳውሎስ መልእክት ይህን ሐሳብ የሚቃረን እንጂ የሚደግፍ አይደለም፡፡ እርሱ እየ ተናገረ ያለው፦ “ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን መዳን የሚገኝበትን ጥበብ” ስለሚሰጡት ቅዱሳት መጻሕፍት ነው፡፡ እነዚህ ቅዱሳት መጻሕፍት መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ብቻ ሳይኾን ድኅነትን የተቀበለ የእግዚአብሔር ሰው “ፍጹምና ለበጎ ሥራ ኹሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ፥ … ለትምህርትና ለተግሣጽ፥ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር” የሚጠቅሙ ናቸው፡፡

Monday, February 1, 2016

ኦርቶዶክስ ማነው? (ማኅበረ ቅዱሳን ኦርቶዶክሳዊ ነውን?)

(ከላእከ ወንጌል ዘኢየሱስ)

 ሳትሞት ሞተች ብለው ምንም ቢቀብሯት
አትሞትም፤ አትሞትም፤ አትሞትም እውነት፤
እውነት የግዜር ገንዘብ እንደግዜር ባሕርይ
ዘላለም ሕያው ናት በምድር በሰማይ፡፡[1]
የዚህ ጽሑፍ ዋና ዐላማ በትምህርተ ሃይማኖት ኦርቶዶክስ ሳይሆኑ ኦርቶዶክስ ነን በማለት በልዩ ልዩ መንገድ ቤተ ክርስቲያናችንን እያወኩ ያሉ ማኅበራት እነርሱ እንደሚሉት ኦርቶዶክሳውያን አለመሆናቸውን ለምእመናን ማሳወቅ ነው፤ በተለይ ወጣቱ በትምህርተ ሃይማኖት ዕጥረት ምክንያት ቤተ ክርስቲያኑን በተገቢው መንገድ ስለማያውቅ በየዩኒቨርሲቲው በግቢ ጉባኤያት ስም ላጠመደው ማኅበር ምርኮኛ ሆኖ ይታያል፡፡ ስለዚህ ወጣቶች ከማኅበር ፍቅር ይልቅ የአንዲት፣ ቅድስት፣ ከሁሉ በላይ የሆነችና ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን ፍቅር እንዲያድርባቸው በዚህ ተከታታይ ጽሑፍ ለመርዳት እንሞክራለን፤ የእውነት አምላክ ልባችንን ለእውነት ብቻ ማስገዛት እንድንችል ይርዳን፤ አሜን፡፡
በዚህ ዘመን ኦርቶዶክስ ነን ባዮች ኦርቶዶክስ ለመሆን ባይቻላቸውም ለመባል ብዙ አማራጮችን በመጠቀም ላይ ናቸው፤ እነዚህ አማራጮችም በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አጥር ግቢ ውስጥ መሰባሰብ፥ ከኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠ ሕግ እንመራለን ማለት፥ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የቊርጥ ቀን ልጆች ነን በማለት በየመጽሔቱ፣ በየጋዜጣውና በኢንተርኔት መስበክ፥ ከቅዱስ ሲኖዶስና ከአባላቱ ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በላይ ለኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተቈርቋሪዎች ለመምሰል መሞከር፥ የእነርሱ ማኅበር አባላት ለመሆን የማይፈልጉ ኦርቶዶክሳውያን አባቶች፣ አገልጋዮችንና ምእመናንን ተሐድሶ ናቸው በማለት መክሰስና ማሳደድ፥ ሁሉንም የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅሮች ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጀምሮ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ድረስ ተሐድሶ እንደ ወረራቸውና ያልተወረረ የእነርሱ ማኅበር ብቻ ስለ ሆነ ሕዝቡ ቅዱስ ፓትርያርኩንም ሆነ ሌሎች አባቶችንና የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችን እንዲጠራጠር ማድረግና ብቸኛው የኦርቶዶክስ አለኝታ የማይጠረጠር ድርጅት የእነርሱ ማኅበር ብቻ መሆኑን መስበክ እንደ ሆነ ካደረግነው ክትትል ለመረዳት ችለናል፡፡

Sunday, January 17, 2016

ወትቀውም ንግሥት በየማንከ

“ወትቀውም ንግሥት በየማንከ
በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኁብርት
ስምዒ ወለትየ ወርእዪ ወአፅምኢ እዝነኪ”
“በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች።
ልጄ ሆይ፥ ስሚ እዪ ጆሮሽንም አዘንብዪ” (መዝ. 44/45፥9-10)

ይህን የመዝሙረ ዳዊት ጥቅስ በሚያነብብ በአብዛኛው ሰው አእምሮ ውስጥ በቶሎ የምትከሠተው ድንግል ማርያም ናት። ይህ የሆነው ጥቅሱ ስለ እርሷ የተነገረ ስለ ሆነ ግን አይደለም። ስለ እርሷ የተነገረ ነው ተብሎ ስለ ተወሰደ፥ በተደጋጋሚ ከእርሷ ጋር ተያይዞ ስለ ተነገረ፥ በየወሩ በ21 ለበዓለ ማርያም የሚዜም ምስባክ ስለ ሆነ ነው ስለ እርሷ የተነገረ ያህል እየተሰማን የመጣው። ቅድስት ድንግል ማርያምን ንግሥተ ሰማይ ወምድር ብለው የሚያምኑ ክፍሎች፥ ሐሳባቸውን በዚህ ጥቅስ ለማስደገፍ ይሞክራሉ። እርሷን በንጉሥ እግዚአብሔር ቀኝ እንደ ተቀመጠች ንግሥትም ይቈጥሯታል።

ቃሉ ስለ ማን እንደ ተነገረ ከመጽሐፉ ተነሥተን እንመልክት። ጥቅሱ ለሚገኝበት ለዚህ የመዝሙረ ዳዊት ክፍል የዐማርኛው የ1953ቱ ዕትም መጽሐፍ ቅዱስ “ለመዘምራን አለቃ፤ በመለከቶች፤ የቆሬ ልጆች ትምህርት፤ የፍቅር መዝሙር” የሚል ርእስ ተሰጥቶታል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለራሷ ባሳተመችው የ2 ሺሁ ዕትም መጽሐፍ ቅዱስም “ለመዘምራን አለቃ በመለከቶች የቆሬ ልጆች ትምህርት የፍቅር መዝሙር” በማለት ይህንኑ ርእስ ነው ያስቀመጠው።

Monday, January 4, 2016

ሐሰትን እውነት ለማድረግ መታገል ማንን ለመጥቀም?

መጽሐፍ ቅዱስ ከእግዚአብሔር የተላኩ ቅዱሳን ሰዎች የጻፉትና ምንም ማሻሻያ ሳናደርግ የምንቀበለው የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የምናምነውን፣ የምንቀበለውንና የምንታዘዘውን ወይም የምንኖርበትን እውነት የያዘ ብቸኛ ቅዱስ መጽሐፍ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ብቸኛው የክርስትና ትምህርትና ሥርዐት ምንጭና መመዘኛ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ከነቢያትና ከሐዋርያት የተቀበለችውና የተመሠረተችበት እውነት መጽሐፍ ቅዱስ በመኾኑም፣ እንደ ዐይን ብሌን ልትጠብቀው ይገባል፡፡

እንዲህ የተባለው በከንቱ አይደለም፤ ቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስ ከተጻፈበት ዘመን እየ ራቀች በሄደች መጠን መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት በማድረግ፣ እንዲሁም ከእዚያ ውጪ የኾኑ የተለያዩ ትምህርቶችን፣ ሥርዐቶችንና ልምምዶችን አዳብራለች፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳዊው ትምህርትና ልምምድ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት ከሌለው ትምህርትና ልምምድ ጋር እየተዛነቀ በሄደ ቍጥር ትምህርቷ ድብልቅ እየ ኾነ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊነቱ እየ ደበዘዘ እና ሌላ መልክ እየ ያዘ መሄዱ አልቀረም፡፡ በኋላ የተገኘው ድብልቅ ትምህርት፣ መሠረቷ የሆነውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርት ስፍራ እያስለቀቀው መጥቷል፡፡ ይባስ ብሎም መጽሐፍ ቅዱሳዊው ትምህርት ለቤተ ክርስቲያን ባይተዋር፣ ድብልቁና እንግዳው ትምህርት ደግሞ ባለቤት እየ ኾኑ ነው፡፡