Monday, February 22, 2016

ፍካሬ መጻሕፍት

ከሕፃንነትህም ጀምረህ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን፥ መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ሊሰጡህ የሚችሉትን ቅዱሳን መጻሕፍትን ዐውቀሃል። የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይኾን ዘንድ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ኹሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል” (2 ጢሞ. 3፥15-17)፡፡
አንዳንዶች ይህን ጥቅስ ሲያነቡ ወይም ሲነበብ ሲሰሙ ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ወይም ዛሬ ላይ ኾነው ከአጠቃላዩ መጽሐፍ ቅዱስ ይልቅ በአእምሮአቸው ውስጥ በቶሎ የሚከሠቱት አዋልድ መጻሕፍት ናቸው፡፡ ይህም የኾነው ጥቅሱ ስለ አዋልድ መጻሕፍት የተጻፈ ስለ ኾነ አይደለም፤ አንዳንድ ሰዎች ጥቅሱን ደግመው ደጋግመው ስለ አዋልድ መጻሕፍት እንደ ተነገረ አስመስለው በአፍም በመጣፍም ስለሚጠቅሱት ነው እንጂ፡፡ “ዓምደ ሃይማኖት” የተሰኘ መጽሐፍ ይህን ጥቅስ ይጠቅስና፥ “እንግዲህ ድርሳናትም ኾኑ ገድላት ስለ እግዚአብሔር አዳኝነት፣ ታላቅነት የሚገልጹ ስለ ኾነ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው መኾናቸው የተረጋገጠ ነው፡፡ ጳውሎስ ስል[ድ]ሳ ስድስቱን መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ተጠቀም አላለም፡፡ ገደብ ሳያደርግ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው በቅዱሳን አባቶችም ኾነ በሌሎችም ክርስቲያኖች የተጻፉትንም መንፈሳዊ መጻሕፍት አለ እንጂ፡፡” ይላል (ብርሃኑ ጎበና 1995፤ ገጽ 37)፡፡
ምንም እንኳ መጽሐፉ የጳውሎስን መልእክት በማብራራት ስም ጳውሎስ ያላለውንና ሊል ያልፈለገውን ሐሳብ፣ እንዳለ አስመስሎ ቢያቀርብም፣ በዚህ ጽሑፍ የምናብራራው የጳውሎስ መልእክት ይህን ሐሳብ የሚቃረን እንጂ የሚደግፍ አይደለም፡፡ እርሱ እየ ተናገረ ያለው፦ “ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን መዳን የሚገኝበትን ጥበብ” ስለሚሰጡት ቅዱሳት መጻሕፍት ነው፡፡ እነዚህ ቅዱሳት መጻሕፍት መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ብቻ ሳይኾን ድኅነትን የተቀበለ የእግዚአብሔር ሰው “ፍጹምና ለበጎ ሥራ ኹሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ፥ … ለትምህርትና ለተግሣጽ፥ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር” የሚጠቅሙ ናቸው፡፡

Monday, February 1, 2016

ኦርቶዶክስ ማነው? (ማኅበረ ቅዱሳን ኦርቶዶክሳዊ ነውን?)

(ከላእከ ወንጌል ዘኢየሱስ)

 ሳትሞት ሞተች ብለው ምንም ቢቀብሯት
አትሞትም፤ አትሞትም፤ አትሞትም እውነት፤
እውነት የግዜር ገንዘብ እንደግዜር ባሕርይ
ዘላለም ሕያው ናት በምድር በሰማይ፡፡[1]
የዚህ ጽሑፍ ዋና ዐላማ በትምህርተ ሃይማኖት ኦርቶዶክስ ሳይሆኑ ኦርቶዶክስ ነን በማለት በልዩ ልዩ መንገድ ቤተ ክርስቲያናችንን እያወኩ ያሉ ማኅበራት እነርሱ እንደሚሉት ኦርቶዶክሳውያን አለመሆናቸውን ለምእመናን ማሳወቅ ነው፤ በተለይ ወጣቱ በትምህርተ ሃይማኖት ዕጥረት ምክንያት ቤተ ክርስቲያኑን በተገቢው መንገድ ስለማያውቅ በየዩኒቨርሲቲው በግቢ ጉባኤያት ስም ላጠመደው ማኅበር ምርኮኛ ሆኖ ይታያል፡፡ ስለዚህ ወጣቶች ከማኅበር ፍቅር ይልቅ የአንዲት፣ ቅድስት፣ ከሁሉ በላይ የሆነችና ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን ፍቅር እንዲያድርባቸው በዚህ ተከታታይ ጽሑፍ ለመርዳት እንሞክራለን፤ የእውነት አምላክ ልባችንን ለእውነት ብቻ ማስገዛት እንድንችል ይርዳን፤ አሜን፡፡
በዚህ ዘመን ኦርቶዶክስ ነን ባዮች ኦርቶዶክስ ለመሆን ባይቻላቸውም ለመባል ብዙ አማራጮችን በመጠቀም ላይ ናቸው፤ እነዚህ አማራጮችም በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አጥር ግቢ ውስጥ መሰባሰብ፥ ከኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠ ሕግ እንመራለን ማለት፥ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የቊርጥ ቀን ልጆች ነን በማለት በየመጽሔቱ፣ በየጋዜጣውና በኢንተርኔት መስበክ፥ ከቅዱስ ሲኖዶስና ከአባላቱ ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በላይ ለኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተቈርቋሪዎች ለመምሰል መሞከር፥ የእነርሱ ማኅበር አባላት ለመሆን የማይፈልጉ ኦርቶዶክሳውያን አባቶች፣ አገልጋዮችንና ምእመናንን ተሐድሶ ናቸው በማለት መክሰስና ማሳደድ፥ ሁሉንም የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅሮች ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጀምሮ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ድረስ ተሐድሶ እንደ ወረራቸውና ያልተወረረ የእነርሱ ማኅበር ብቻ ስለ ሆነ ሕዝቡ ቅዱስ ፓትርያርኩንም ሆነ ሌሎች አባቶችንና የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችን እንዲጠራጠር ማድረግና ብቸኛው የኦርቶዶክስ አለኝታ የማይጠረጠር ድርጅት የእነርሱ ማኅበር ብቻ መሆኑን መስበክ እንደ ሆነ ካደረግነው ክትትል ለመረዳት ችለናል፡፡