Thursday, November 21, 2013

ርእሰ አንቀጽ

ይህን ዓመት ደግሞ ተዋት!

የእያንዳንዱ ቅጽበት፥ ሰኮንድ፥ ደቂቃ ትዝታ ይህን ያህል ጐልቶ በተናጠል በአእምሮኣችን ባይመዘገብም፤ በሰዓት፥ በቀን፥ ከዚያም በወርና በዓመት እየተጠቃለለና የራሱን ድምር ትዝታ እየተወ ሲያልፍ ኖሮአል፡፡ ያለፈው ሁሉ ታሪክ ሆኖአል፤ ተጽፎአል፤ ተነቦም መዝገብ ቤት ይቀመጥ ተብሏል፡፡ አብዛኛው ሰው ባለፈው ቀን ትዝታ ላይ ሙሉ ጊዜውን ከሚያሳልፍ ይልቅ በሚመጣው ቀን ምን እንደሚያጋጥመው ዐውቆ ለመዘጋጀት በእጅጉ ይጥራል፡፡ ብርቱ ፍላጎትም ያለው ስለ ወደ ፊቱ ዕቅድ መሳካት ነው፡፡ ይህንም የሰው ልጅ ፍላጎት የተረዱ ብልጣብልጥ የኅብረተሰብ አባላት መጪውን ዕድልህን ልንነግርህ እንችላለን እያሉ የዋሁን ሕዝብ ለዘመናት ገንዘቡንና ጊዜውን በዘበዙት፤ ሥነ ልቡናውንም ሰለቡት፡፡

እንደዚህ የመሳሰለው አካባቢያዊ ተጽዕኖ ከሚቀሰቅሰው ውስጣዊ ግፊት የተነሣ ሰዎች ከአሮጌው ዓመት ትዝታ ይልቅ ለመጪው ጊዜ ምን ይሁንታ ቅድሚያ ይሰጣሉ፡፡ ስለዚህም ለመጪው ዓመት ብሩህ ተስፋ እውን መሆን ሲሉ ጠንክሮ ለመሥራት በሙሉ ዕውቀታቸውና ኀይላቸው ይዘጋጃሉ፡፡ ስለዚህም በየዓመቱ መጀመሪያ ለዐዲሱ ዓመት እንኳን አደረሰህ! አደረሰሽ! በመባበል የመልካም ምኞት መግለጫ ይለዋወጣሉ፡፡ ስለ ዐዲሱ ዓመት እንጂ ስላለፈው ግድ የሚኖረው ያለ አይመስልም፡፡ ላለፈው ክረምት ቤት አይሠራለትምና፡፡

Thursday, November 14, 2013

መሠረተ እምነት


ከነቅዐ ጥበብ
ባለፈው ዕትም ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት በቀረበው ጽሑፍ፦ አምላክ ሰው የሆነበትን ምክንያት፣ ቃል ሥጋ የመሆኑን አስፈላጊነት፣ የክርስቶስ አዳኝነትና መካከለኛነት ተያያዥ መሆናቸውን በማብራራት፥ የኢየሱስ ክርስቶስን መካከለኛነት ለማስተባበል በዚህ ዘመን የሚነዙ የስሕተት ትምህርቶችን ለመጠቈም ተሞክሯል፡፡ በዚሁ መሠረት ኢየሱስ አሁን ፈራጅ እንጂ አማላጅ አይደለም የሚለውንና ሮሜ 8፥34 ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት የሚያስተምረውን በመጠኑ ተመልክተናል፡፡ በዚህ ዕትም ደግሞ ተከታዩ ክፍል ይቀርባል፡፡

ኢየሱስ አሁን ጠበቃ ነው ወይስ ዳኛ?
ወደ መጽሐፍ ቅዱስ እውነት ለመድረስ ከራሱ ከመጽሐፍ ቅዱስ መጀመር የግድ ነው፡፡ "ትንሽ ቆሎ ይዞ ወደ አሻሮ መጠጋት" እንደሚባለው ብሂል፥ የራስን አመለካከት ወይም ሌላ ምድራዊ ተመክሮን ይዞ ወደ መጽሐፍ ቅዱስ መጠጋት፥ የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ለመቀበል ሳይሆን፥ መጽሐፍ ቅዱስን ለራስ ሐሳብ ደጋፊ አድርጎ ለማቅረብ ያለመ አካሄድ ነው፡፡

Sunday, November 3, 2013

የዘመን ምስክር


በዚህ ዐምድ ለቤተ ክርስቲያን መሻሻልና መለወጥ የተጋደሉ፥ ለአገርና ለወገን የሚጠቅም መልካም ሥራን የሠሩ አበውን ሕይወትና የተጋድሎ ታሪክ አሁን ላለውና ለቀጣዩ ትውልድ አርኣያ እንዲሆን እናስተዋውቃለን፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ (1902-1971 ዓ.ም.)
ያለ መንፈስ ቅዱስ አብርሆት የእግዚአብሔርን ቃል ማስተዋልና መለወጥ እንደማይቻል የታወቀ ነው። እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ሲናገር፥ ሰው ሊሰማ ይችላል፤ ነገር ግን ያ ሰው ቃሉን የሚያስተውለውና በቃሉ ተለውጦ ዐዲስ ፍጥረት የሚሆነው፥ የተዘጋው የልቡናው በር በእግዚአብሔር ቃል ሲንኳኳና በመንፈስ ቅዱስ አብርሆት መከፈት ሲችል ብቻ ነው። ልድያ የተባለችው የትያጥሮን ሴት፥ ጳውሎስ የሚናገረውን ታዳምጥ ዘንድ ጌታ ልቧን ከፍቶላት ነበርና በሰማችው ቃል ሕይወቷ ተለወጠ (ሐ.ሥ. 16፥14-15)። የቅዱስ ጳውሎስ ድርሻ ቃሉን መናገር እንጂ እርሷን ማሳመን አልነበረም፤ ልቧን ከፍቶ ቃሉን እንድታደምጥና በቃሉ እንድታምን ያደረገው ጌታ ነው። ይህ ትናንትም ሆነ ዛሬ እግዚአብሔር ሰዎችን ለመለወጥና ዐዲስ ፍጥረት ለማድረግ የሚጠቀምበት ድንቅ አሠራሩ ነው።

መማርና ማወቅ ለሰው መልካም ነገሮች ቢሆኑም፥ የእግዚአብሔርን እውነት ለማስተዋል ግን ከላይ እንደ ተገለጸው የመንፈስ ቅዱስ አብርሆት ያስፈልገዋል። የፍጥረታዊ ሰው ልብ ብርሃን እግዚአብሔር እስኪበራበት ድረስ ጨለማ ነው (ሮሜ 1፥21፤ ኤፌ. 5፥8)። በዚህ ጨለማ ልብ ውስጥ እግዚአብሔር ካልበራ (መዝ. 118፥27) በቀር ፍጥረታዊው ሰው እግዚአብሔርንም ሆነ የእግዚአብሔርን ፈቃድና ሐሳብ ሊገነዘብ አይችልም (1ቆሮ. 2፥14)። ስለዚህ ሰው ያስተውል ዘንድ እግዚአብሔር በጨለመው የሰው ልብ ውስጥ ብርሃኑን ያበራል (መዝ. 18፥28፤ 2ቆሮ. 4፥4-6)። ሰውም በልቡ በበራው ብርሃን እየተመራ የእግዚአብሔርን እውነት ያስተውላል (መዝ. 36፥9)።