Monday, September 28, 2015

የክርስቶስ ተከታዮችና መለያቸው

መስበኪያ ቦታ የሚል ፈቺ ባለው በዚህ ዐምድ ወንጌል ይሰበካል፡፡
መምሬ ባሮክ
ሰዎች ከጥንት ጀምሮ ለሚያምኑበት ነገር መለያ ወይም መታወቂያ ማበጀታቸው የተለመደ ነው፡፡ የጥንት ክርስቲያኖች በግሪኩ መስቀልና “ክቱስ” (የዓሳ ምስል) የክርስቲያንነታቸው መታወቂያ ነበር፡፡ በቅርቡ ኮሚኒስቶች ማጭድና መዶሻ የሚያምኑበት ነገር መገለጫ ሆነው አገልግለዋል፡፡ በእናት ቤተ ክርስቲያንም አንድ ሰው ክርስቲያን መሆኑን ለመግለጽ በአንገቱ ላይ ማተብ (ክር) ማሰሩ የተለመደ ትውፊት ነው፡፡

ከጌታ ዕርገት በኋላ ስለ ሐዋርያት÷ የሐዋርያት ሥራ 4÷13 የክህናት አለቆች በድርጊታቸው ከኢየሱስ ጋር እንደ ነበሩ ዐወቋቸው ሲለን÷ ምዕራፍ 11÷26 ደግሞ እነዚህ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ለመጀመሪያ ጊዜ በአንጾኪያ “ክርስቲያን” እንደ ተባሉ ይነግረናል፡፡ ለመሆኑ አንድ የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይ ወይም ደቀ መዝሙር መታወቂያው ምንድን ነው? ብንል÷ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ዐሥራ ዐምስት ላይ ያስተማረው ይህን እውነት የሚገልጥ ነው፡፡ እንደምናውቀው የዮሐንስ ወንጌል ከምዕራፍ 13 እስከ ምዕራፍ 17 ጌታ በሕማማቱ ሳምንት ያስተማረው ትምህርት ሲሆን÷ እንደሚሰናበት ሰው ለደቀ መዛሙርቱ አደራና መመሪያ የሰጠባቸው ምዕራፎች ናቸው፡፡ በእነዚህ ምዕራፎች ተለይቶአቸው የሚሄድ በመሆኑ ደቀ መዛሙርቱ ማዘናቸውንና ጌታም እነርሱን ማጽናናቱን÷ ተልእኮውንም አስረግጦ መግለጡንና ሊያደርጉ የሚገባቸውንም ማሳሰቡን እናነባለን፡፡ ከእነዚህ ዐምስት ምዕራፎች በተለይ ምዕራፍ ዐሥራ ዐምስት ላይ አጽንኦት የሰጠው የእርሱ ተከታዮች (ደቀ መዛሙርት) በሌሎች ሊታወቁ ወይም ሊገለጡ ስለሚችሉባቸው ሦስት መሠረታውያን መለያዎች ነው፡፡ 

Sunday, September 20, 2015

ኢየሱስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ

ስለ ጌታችን፥ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት ባለፉት ተከታታይ ዕትሞች ትምህርቶች ሲተላለፉ ቈይተዋል። ዛሬ የመጨረሻውን ክፍል የምንመለከት ሲሆን፥ “የክርስቶስ መካከለኛነት በሥጋ ወደሙ በኩል የሚፈጸም ነው” የሚለውን የአንዳንዶች አመለካከት በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ለመመርመር እንሞክራለን። በርግጥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፥ “ክርስቶስ መካከለኛ ነው ማለት ሥጋ ወደሙ መካከለኛ ነው ማለት ነው” ብላ እንደምታስተምር በግልጥ የተጻፈ ነገር አልተገኘም። በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የሚሰብኩ አንዳንድ ሰባክያን ግን ትምህርቱን ባፍም በመጣፍም ሲያስተምሩት መገንዘብ ችለናል።

መምህር ታሪኩ አበራ የተባሉ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ምሩቅ “ኢየሱስ ማነው?” በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ፥ “ዛሬ ኢየሱስ ለእኛ ጠበቃ ነው ስንል በሰማይ ከዲያብሎስ ጋር፥ ዕለት በዕለት የሚጨቃጨቅ የሚከራከር ጠበቃ ሆኖ አይደለም፤ አንድ ጊዜ በፈጸመው የማዳን ሥራ የጌታን ሥጋና ደም ከተቀበልን … ያ ሥጋና ደም … ጠበቃ ሆኖ ከዲያብሎስ ክስ ነጻ ያወጣናል። ለዚህ ነው ሥጋዬን የበላ ደሜን የጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው ያለው” ሲሉ ጽፈዋል (ገጽ 119 አጽንዖት የግል)። እርሳቸው እንዲህ ያሉት፥ “ልጆቼ ሆይ፥ ኀጢአትን እንዳታደርጉ ይህን እጽፍላችኋለሁ። ማንም ኀጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን፤ እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው” (1ዮሐ. 2፥1) ለሚለው መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል ማብራሪያ እሰጣለሁ ብለው ነው።

Monday, September 7, 2015

ብዙ ተስፋ


ተስፋ የሚለው ቃል ሲጠራ በራሱ ተስፋ ይለመልማል። ልብ በሐሤት ይሞላል። የሰው እግር በድል የሚራመደው ልቡ በተስፋ ሲሞላ ነው። ተስፋ ከሌለ እግር ሽባ ይሆናል። ተስፋ ግን ሽባውን እግር የሚያረታ፥ ከተጠበቀው በላይ የሚያራምድ ነው። ተስፋ ያጣ ሰው ምንም ሳይሆን ብዙ የሆነ ይመስለዋል። ገና ቀን ሳለ ሌሊት መስሎት ይተክዛል። ትጥቁና ስንቁ እያለ ጦርነቱን በሽንፈት /በበቃኝ/ ይደመድማል። ተስፋ መዳረሻ ነው። ከምሳ ሰዓት በኋላ እስከ እራት ያለው ጊዜ ረጅም ነው። ሠርክ ላይ ትንሽ ምግብ ይቀመሳል። ያ መክሰስ ወይም መዳረሻ ነው። ተስፋም እንዲሁ ነው። እግዚአብሔር ያሰበልን ነገር ላይ ለመድረስ መዳረሻ /መቈያ/ ነው።

ተስፋ በመጀመሪያ በፅንሰቱ ኋላም በልደቱ ደስ ያሰኛል። ተስፋ ያደረጉት ነገር ሲፈጸም ልብ ሙሉ ይሆናል፤ መኖርም ምክንያታዊ ይመስላል። እግዚአብሔር የተስፋ አምላክ፥ የተስፋ መሠረት፥ የተስፋ ፍጻሜ ነው። እግዚአብሔር ተስፋን የሚሰጠው ከራሱ የፍቅርና የቸርነት ባሕርይ በመነሣት ነው። ይህ ሁለት ነገሮችን ያስተምረናል።
1.    ተስፋን የሰጠን በራሱ ፈቃድ ስለ ሆነ ለመፈጸም አይቸገርም።
2.   የተስፋ መነሻ ፍቅር ነው፤ ፍቅር ሲኖረን ቸሮች ብቻ ሳይሆን ባለተስፋም እንሆናለን።