Saturday, August 18, 2012

ጸሎት


(በጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ቊጥር 3 ላይ የቀረበ)


“ጌታ ሆይ እንጸልይ ዘንድ አስተምረን፡፡” (ሉቃ. 11፥1)

ከክርስትና ሕይወታችን አብዛኛው ክፍል የሚያዘው በጸሎት እንደሆነ የታወቀ ነው፡፡ ያለመታከት መጸለይ እንዲገባን የእግዚአብሔር ቃል ይመክረናል (ሉቃ. 18፥1-7)፡፡

ኑሮአችን በጥያቄና በችግር የተሞላ ስለሆነና ሁል ጊዜ የምንቀበለው ስለሚበዛ፥ ያለ ጸሎት ልንኖር አንችልም፡፡ ትንሽ ልጅ ሲርበው፤ ቊርሱን ምሳውን፥ እራቱን፤ ሲበርደው ልብሱን፥ መጠለያውን ይጠይቃል፡፡ ሲታመም ይቅበጠበጣል፥ ያለቅሳል፡፡ እንቅፋት ቢመታው፥ እሾኽ ቢወጋው፥ የጎረቤት ልጅ ቢያጠቃውና በእድገቱ ሂደት የሚያጋጥሙትን ዐዳዲስ ነገሮች ሁሉ የማወቅ ጥማቱን ለማርካት ጥያቄዎችን ይደረድራል፡፡ ትናንት ጠይቆ በተቀበለው ተጠቅሟል፥ አመስግኗልም፡፡ ሆኖም ትናንት ዐልፎአልና ዛሬ ለዐዲስ ጥያቄ ዐዲስ ምላሽ ይጠብቃል፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ክርስቲያንም በዚህ ተመሳሳይ ምክንያት ጸሎትን ማቋረጥ አይችልም፤ አያስታጕልም፡፡

Monday, August 13, 2012

ግጥም

Read in PDF
(በጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ቊጥር 3 ላይ የቀረበ)
                                        
                                        የትግል ምዕራፍ

በቀጭኑ መንገድ ሰዎች ባልበዙበት
መሰናክልና እንቅፋት ባለበት
ጀምረህ እንደ ሆን አቅንትህ መራመድ
ወደ ኋላ ሳትል ወደ ፊትህ ንጐድ፡፡

ጒዞህን ጀምረህ ጥቂት ዕልፍ ስትል
አለልህ እንቅፋት የሚጥር ለመጣል፡፡

አለልህ እርግጫ  አለልህ ኲርኲሙ
ሊጥልህ ይታገላል ሁሉም እንዳቅሙ፡፡

እርሱን ዐለፍ ብለህ በሥቃይ እንዳለህ
እምነት እሚፈታ ተራራ ታያለህ፡፡

ይህን ሁሉ ዐልፈህ መንገዱ ወለል ሲል
የመረረው ጒዞ ሲተካልህ በድል
ምዕራፉ ሲዘጋ ግፊውም ያከትማል፡፡

Sunday, August 5, 2012

አለቃ ነቅዐ ጥበብ

Read in PDF
በጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ቊጥር 43 ላይ የቀረበ
ትረካ፥ ከነቅዐ ጥበብ
በገጽ ጥበት ምክንያት በጮራ ቊጥር 42 ላይ የዚህ ዐምድ ጽሑፍ አልቀረበም ነበር። አንባቢ እንደሚያስታውሰው በቊጥር 41 ላይ ወጥቶ የነበረውንና በማኅበረ ቀናዕያንና በደቂቀ እስጢፋኖስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርት መካከል የተፈጠረውን ውዝግብ ለመፍታት የተደረገውን ጉባኤ የተመለከተውን ዘገባ የመጀመሪያ ክፍል፥ በጮራ ቊጥር 41 ላይ አውጥተን ነበር። የዚያን ጽሑፍ ተከታይ እነሆ!

በመርሐ ግብሩ መሠረት ማኅበረ ቀናዕያንን በመወከል ዲያቆን በለው፥ ደቂቀ እስጢፋኖስ መንፈሳዊ ኮሌጅን ወክሎ ደግሞ ደቀ መዝሙር በቃሉ በየተራና በመደማመጥ ሐሳባቸውን ካስተላለፉ በኋላ፥ በቀረቡት ሁለት ተቃራኒ ሐሳቦች ዙሪያ ታዳሚው አስተያየት እንዲሰጥ የመድረክ መሪው መጋቤ ወንጌል ኅሩይ እምአእላፍ ታዳሚውን ጋበዙ። የመናገር ዕድሉን ለማግኘት በርካታ እጆች ወጡ። ሁሉም ዐጠር ዐጠር አድርገው ሐሳባቸውን እንዲሰጡ ተደረገ። ሁለቱንም ወገኖች ደግፈውና ተቃውመው አስታያየቶች የሰጡ ነበሩ። ሁለቱን ከመደገፍም ከመቃወምም ርቀው ሚዛናዊ አስተያየት የሰጡም ነበሩ። እኛም ይጠቅማሉ ካልናቸው አስተያየቶች መካከል ጥቂቶቹን ከዚህ ቀጥሎ እናቀርባለን። በመጨረሻም አለቃ ነቅዐ ጥበብ የሰጡትን ሐሳብ በማካተት ዘገባችንን እናጠቃልላለን።