Sunday, October 25, 2015

" ... የናቁሽም ሁሉ ወደ እግርሽ ጫማ ይሰግዳሉ፤ ..." (ኢሳ. 60፥14)

“ወይመጽኡ ኀቤኪ እንዘ ይፈርሑ ወያመጽኡ አምኀ ደቂቆሙ እልኩ እለ አምዕዑኪ ወይሰግዱ ቅድመ መከየደ እግርኪ ወትሰመዪ ሀገረ እግዚአብሔር ቅዱሰ እስራኤል ጽዮን - የአስጨናቂዎችሽም ልጆች አንገታቸውን ደፍተው ወደ አንቺ ይመጣሉ፥ የናቁሽም ሁሉ ወደ እግርሽ ጫማ ይሰግዳሉ፤ የእግዚአብሔርም ከተማ፥ የእስራኤል ቅዱስ የሆንሽ ጽዮን ይሉሻል” (ኢሳ. 60፥14)።?
ውሸት ሲደጋገም እውነት ይሆናል የሚል ፍልስፍና ያላቸው ወገኖች አሉ። እንዲህ ለማለት ያበቃቸው በተደጋጋሚ የሚያቀርቡትን ውሸት፥ ሰዎች እውነት ነው ብለው የተቀበሏቸው ስለ መሰላቸው ነው።  ውሸት፥ ውሸት ነው፤ እውነት ደግሞ እውነት ነው። ዐሥር ወንፊት ቢደራረብ አንድ ብልቃጥ ውሃ መያዝ እንደማይችል ሁሉ፥ ውሸት የቱንም ያህል የእውነት ጠብታ ቢጨመርበት ድምር ውጤቱ ውሸት ነው ውሸት በምንም ተኣምር ወደ እውነትነት የሚለወጥበት ዕድል ከቶ የለም፤ አለ ከተባለ ግን እውነትን አለማወቅ፣ እውነትን ማራከስና ዋጋ ማሳጣት ይሆናል። ስለዚህ ውሸት ሲደጋግም እውነት ይመስላል እንጂ እውነት ሊሆን በፍጹም አይችልም።
ኢሳ. 60፥14 ስለ ማን ይናገራል?
ስድሳ ስድስት ምዕራፎች ያሉት ትንቢተ ኢሳይያስ በሦስት ዐበይት ክፍሎች ሊከፈል እንደሚችል የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ይናገራል (1972፣ ገጽ 149)። የመጀመሪያው ክፍል ከምዕራፍ 1-39 ድረስ ያለው ሲሆን፥ ነቢዩ ኢሳይያስ በነበረበት ዘመን የተከናወኑትን ድርጊቶች መሠረት በማድረግ የተጻፈ ነው። ሁለተኛው ክፍል ደግሞ፥ ከምዕራፍ 40-55 ድረስ ያለውና ከኢሳይያስ ዘመን በኋላ ስለ ተፈጸመው ስለ ባቢሎን ምርኮ የተነገረ ትንቢት ነው። የመጨረሻው ክፍልም ከምዕራፍ 55-66 ደግሞ ወደ ፊት ማለትም ከባቢሎን ምርኮ ፍጻሜ በኋላ ስለሚሆነው የጽዮን ክብር ይናገራል። በመነሻው ላይ የተጠቀሰው ጥቅስ የተወሰደውም በዚህ በሦስተኛው ክፍል ከሚገኘው ትንቢተ ኢሳይያስ ምዕራፍ 60 ቊጥር 14 ላይ ነው።

Monday, October 19, 2015

“ልበ ነጹሖች ብፁዓን ናቸው፥ እግዚአብሔርን ያዩታልና” (ማቴ. 5፥8)

ከደምፀ ቃለ አብ

ጌታችን አየሱስ ክርስቶስ በተራራው ላይ ያስተማራቸው ትምህርቶች ደስታ ለሞላበት አኗኗር መሠረት ናቸው፡፡ ትምህርቶቹ በተራራ ላይ የተሰበኩ ሲሆኑ የመንፈሳዊ ከፍታም መገለጫዎች ናቸው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት ለማደግ ምትሐታዊ ቊጥሮች የምስጢር ቊልፎች የሉም፡፡ የመንፈሳዊ ከፍታ መመዘኛው የተራራው ስብከት ነው፡፡ የተራራው ስብከት የውስጥ መጠይቅ በመሆኑ ሰው ራሱን የሚያይበትና የሚያስውብበት ልዩ ክፍል ነው፡፡ በተራራው ስብከት ዓለም ትልቅ ስፍራ የምትሰጣቸው ነገሮች ውድቅ ሆነዋል፡፡ ዓለም፡-
*     ራስህን አክብር ትላለች፤ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- በመንፈስ ድኾች የሆኑ ብፁዓን ናቸው$ መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና (ማቴ. 5፥3) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ደግሞ ራስህን አክብር፤ ዓለም ያንተ ናትና የሚል ይመስላል፡፡
*     ደስተኛ ብቻ ሁን ትላላች፤ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- የሚያዝኑ ብፁዓን ናቸው$ መጽናናትን ያገኛሉና፥ማቴ. 5$4) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ደግሞ፡- ደስተኛ ብቻ ሁን፤ ስለ ሌላው ምን አገባህ ትላለች፡፡
*     በደልን አትርሳ ትላለች፡፡ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- የዋሆች ብፁዓን ናቸው፥ ምድርን ይወርሳሉና (ማቴ. 5፥5) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ደግሞ፡- በደልን አትርሳ፤ አጥምደህ ያዘው፤ ላንተ ይገዛልና ትላላች፡፡
*     እንደ ጊዜው ኑር ትላለች፡፡ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- ስለ ጽድቅ የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው፥ ይጠግባሉና (ማቴ. 5፥6) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ደግሞ፡- ተመሳስለህ ኑር፤ ከሁሉም ትጠቀማለህ ትላለች፡፡
*     ተቀበል እንጂ የአንተን አታካፍል ትላለች፡፡ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- “የሚምሩ ብፁዓን ናቸው፥ ይማራሉና” (ማቴ. 5፥7) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ግን፡- “አጠራቅም ይበዛልሃል” የሚል ነው፡፡
*     ንጽሕናህን ጠብቅ ትላለች፡፡ የተራራው ስብከት ደግሞ፡- ልበ ንጹሖች ብፁዓን ናቸው እግዚአብሔርን ያዩታልና” (ማቴ. 58) ይላል፡፡ የዓለም ስብከት ግን፡- “ውስጥህን ማንም አያውቅም፤ ውጫዊ ንጽሕናህን ጠብቅ” ይላል፡፡

Monday, October 12, 2015

አለቃ ነቅዐ ጥበብ

ትረካ፡- ከነቅዐ ጥበብ

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ታሪካቸው የተመዘገበው ኒቆዲሞስና ዮሴፍ ዘአርማትያስ (ዮሐ. 3፥2፤ 19፥38) ያደርጉት እንደ ነበረው፥ መሪጌታ ብርሃነ መስቀልም ጨለምለም ሲል ራሳቸውን ለወጥ አድርገው ወደ አለቃ ነቅዐ ጥበብ እየሄዱ ከሚማሩ ስውር ደቀ መዛሙርት መካከል አንዱ ነው፡፡ በሚያገለግልበት ደብር ውስጥ እርሱ ከሚኖርበት የመቃብር ቤት ጥቂት ዕልፍ ብሎ በሚገኘው በሌላው መቃበር ቤት ውስጥ ለሚኖረው ባልንጀራው ለመሪጌታ በትረ ጽዮን ግን ወዴት እንደሚሄድ አይነግረውም ነበር፡፡ ምክንያቱም ካሁን ቀደም በወንጌል ስለ ተገለጠው የእግዚአብሔር ጽድቅ ሊያስረዳው ቢሞክር፥ ፍጹም ተቃዋሚና እርሱንም አሳልፎ ሊሰጠው የሚችል ዐይነት ሰው ሆኖ ስለ ተመለከው፥ በሌላው ጕዳይ ካልሆነ በቀር ለጊዜው በዚህ ነገር ዳግም ላያነጋግረው ወስኖ ነበር፡፡

ብዙ ጊዜ እንደ ነገ የሚቆሙትን የማሕሌት ቀለም እንደ ዛሬ ዐብረው ሲመለከቱ፥ የወንጌልን እውነት ለመግለጥ በር የሚከፍት ቃል ካጋጠመው፥ ወይም ከእግዚአብሔር ቃል ፍጹም ተቃራኒ የሆነ ስሕተት ካገኘ አያልፍም፤ በዚያ መነሻነት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ ውይይትና ክርክር ያደርጉ ነበር፡፡ ባለማቋረጥ የሚንጠባጠብ የውሃ ጠብታ ከታች ያለውን ዐለት እንደሚቦረቡረው፥ መሪጌታ ብርሃነ መስቀል በመሪጌታ በትረ ጽዮን ጆሮ የሚያንቈረቊረው መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነት ከጊዜ ወደ ጊዜ ልቡን እየሸረሸረው መምጣቱ አልቀረም፡፡ ይሁን እንጂ የያዘውን ነገር በቀላሉ ለመልቀቅ ስለሚቸገርና ሽንፈትም ስለሚመስለው በቶሎ እጅ አይሰጥም፡፡ በዚህ ሁኔታ ብዙ ጊዜያት አልፈዋል፡፡

Tuesday, October 6, 2015

የራስ ኩራት

በግር አይቀመስ፣
በአፍ አይዳሰስ፣
በእጅ አይተነፈስ፣
ፊኛ ደም አይረጭም፣
ኩላሊት አይፈጭም
ጥፍርም አያጎርስም፣
አይኬድ በምላስ፣
በጥርስ አይለቀስ፡፡
ልብ አያጨበጭብ፣
አያስብም ቅንድብ፣
ሳንባም አይዋብ፡፡
ዐይንም አይሰማ፣
ጆሮ አይል እማማ፣
ደም አያጠልቅ ጫማ፡፡
የጅ ጣት ቀለበት፣
አይከተት ባንገት፣
ጉትቻ የጆሮ፣
አይሆን ለጉሮሮ፣
ጉርም በየተራ
አይጎርስም እንጀራ፡፡
ሰልካካ አፍንጫ
አይችልም ሩጫ፡፡
ደረት . . . ሱሪ ለብሶ
እግር ከንፈር ነክሶ
ጣፊያን ተንተርሶ
ተረከዝ ተናዶ
ግንባር ከስር ወርዶ
ትከሻ ሲሳለቅ
ወገብ እንባ ሲለቅ
ባት ሲተፋ ምራቅ
ማነው ይህን ያየ፤
እንደዚህ የለየ፤
ይሄ ሁሉ ድንቅ!
ታይቶም አይታወቅ፡፡
ደግሞ ይሄ ብሶ
ጥርስ ምላስ ነክሶ
ፍርድ ቤት ተከሶ
እግር እግርን ገጭቶ
በደንብ ተመታቶ
ሲለያይ ተፋቶ
እጅ ካፍ ተጣልቶ
ሳያጎርሰው ቀርቶ
አላየሁም ከቶ፡፡
ጨጓራ ለአንጀት
ምግብ ሳይልክለት
ለራሱ በልቶበት
ሟጦ ጨርሶበት፡፡
ልብ ደም ሳይሰጠው
ኩላሊት ሲያፋጠው
በቡጢ ሲመታው
መቼ ታየ ለሰው፡፡
ቅንድብ አይን ሲገጭ
ዐይን ሲነጫነጭ
በውሳኔ እንዲላጭ
ሲሳልለት ምላጭ
ማን ያውቃል ሰምቶ፤
በጆሮው አጣርቶ፤
መዳፍም ቀንቶበት
ጣት ሲያጠልቅ ቀለበት
አጡዞት በቡጢ
ብሎትም መናጢ
መዝልጎ ቆንጥጦ
ገዝቶትም ረግጦ
ማነው ይህን ያየ፤
እንደዚህ የለየ፤
ሁሉም አለው ሥራ
ለራሱ ሚያኮራ፡፡
ጆሮም ማዳመጡ
እግርም መሯሯጡ
እጅም መዳሰሱ
ምላስም መቅመሱ
ሳንባም መተንፈሱ
ጨጓራም መፍጨቱ
አፍንጫም ማሽተቱ
አይንም መልከት መልከት
ይሄ ነው ሚያምርበት
የሌላው ይቅርበት
የራሱ ነው ኩራት፡፡
ዐይን ቢል አላይም
አፍንጫ አላሸትም
እጅ አይወጣውም
ስጦታው የለውም
ሁሉም አለው ሥራ
ለራሱ ሚያኮራ
ብርቱና ጠንካራ፡፡

(ከአዲስ መስቀሌ)


በጮራ ቍጥር 39 ላይ የቀረበ