በጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ቊጥር 3 ላይ የቀረበ
PDF:በኢትዮጵያ የእግዚአብሔር መንግሥት ታሪክ
PDF:በኢትዮጵያ የእግዚአብሔር መንግሥት ታሪክ
በቊጥር 2 የጮራ ዕትም እንደ ተገለጸው፥ የዕብራይስጡ ብሉይ ኪዳን “ኩሽ” ሲል ከካም ልጆች አንዱ የሆነው የኩሽ ነገድ በባለቤትነት ለሰፈሩባት የመሬት ክልልና ለነዋሪዎችዋ ለራሳቸው የሰጠው ስም እንደ ሆነ አንብበናል። ብሉይ ኪዳንን ወደ ጽርእ የተረጐሙት ሊቃውንት ኩሽ የሚለውን ቃል “ጥቊር” የሚያሰኝ ትርጕም እንዲኖረው “ኢትዮጵያ” በሚለው ጽርኣዊ ቃል መተርጐማቸውን ተረድተናል። ሰባ (ሰብዓ) ሊቃውንት የነገደ ኩሽ ጥቊረት የመጣው በሚኖሩበት ምድረ በዳ ካለው የፀሓይ ሐሩር መሆኑን ለመግለጽ ሲሉ፥ ነዋሪዎቹን ብቻ ሳይሆን መኖሪያ አገራቸውን ጭምር ኢትዮጵያ ማለታቸው፥ እንዲሁም በዕብራይስጡ የምድረ በዳ ትርጕም ያለውን ቃል ኢትዮጵያ እያሉ ወደ ጽርእ መመለሳቸው ለቃሉ የነበራቸውን ፅንሰ ሐሳብ እንደሚያመለክት የተሰጠውን ግምገማ ተረድተናል።
ከዚህም በመነሣትና በማያያዝ ኢትዮጵያ፥ የዛሬዪቱ ሱዳን (የቀድሞዪቱ ኑብያ) እና ግብጽ እርስ-በርስ የተገዛዙበት ጊዜ መኖሩን ከግምት በማስገባት፥
አንደኛ ለስሙ በዋና ባለቤትነት የምትታወቀው የዛሬዪቱ ኢትዮጵያ፥
ሁለተኛ በዐረብኛ ጥቊር የማለትን ትርጕም የያዘችው ሱዳን (የቀድሞ ኑብያ-ኢትዮጵያ)፥
ሦስተኛ የኩሽ ወንድም የሚጽራይም አገር የሆነችው ምስር (ግብጽ)፥
በወልም ሆነ በየግል ኢትዮጵያ የሚለውን ስም ሲጠሩበት እንደ ነበረ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጥቂት ጥቅሶችን በየተስማሚ ክፍሉ ማንበባችንን እናስታውሳለን።