Sunday, February 18, 2018

ልዩ ልዩ



የጮራ መንፈሳዊ መጽሔት 25ኛ ዓመት የምሥረታ ክብረ በዓልን ምክንያት በማድረግ የቀረበ ጽሑፍ

አቀድም አእኵቶቶ ለእግዚአብሔር በእንተ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ(ሮሜ 18) በእንዲህ መሰሉ ክርስቲያናዊ ክብረ በዓል ላይ ቃለ አኰቴት መቅደሙ አያስገርምም። ደግሞስ እንደ ክርስቲያን በኹሉና ስለ ኹሉ ማመስገን ይገባን የለምን? ስለ ኾነም ከኹሉ አስቀድመን በነገር ኹሉ የረዳንን ልዑል እግዚአብሔርን በኢየሱስ ክርስቶስ እናመሰግነዋለን።

ቀጥሎስ? እንኳን ደስ አላችሁ። የማኅበረ በኵር አባላትና አገልጋዮች፥ የጮራ መንፈሳዊ መጽሔት መሥራቾች፥ አዘጋጆች፥ ዐምደኞች፥ የራእዩ ደጋፊዎችና በዚች መጽሔት አገልግሎት የተጠቀማችሁ ኹሉ እንኳን ለዚህ ቀን አደረሳችሁ።

መግቢያ

አገራችን ኢትዮጵያ የሚታዩና የሚዳሰሱ ቀደምት የሥልጣኔ አሻራዎች ባለቤት መኾኗ የታወቀ ነው። በአስገራሚ ኪናዊ ጥበብና ውበት የተገነቡ ዘመን ተሻጋሪ የሥነ ሕንጻ ባለቤት ናት። በሥነ ጽሑፋዊ ቅርሶችም ረገድ የራሷ ፊደል ያላት ብቻ ሳይኾን ቀደምት ጽሑፎችን አበርክታለች። ለጽሑፍ ሥራ እንግዳ ኾናም አልኖረችም። በጥንታዊውም፥ በመካከለኛውም ኾነ በዘመናዊው ታሪካችን ወቅት በተከሠቱ ኹነቶችና ባጋጠሙን ውስጣዊም ኾነ ውጫዊ ፈተናዎች የወደሙትን ሳንቈጥር፥ በርካታ የሥነ ጽሑፍ ውጤቶች አካብተናል። እግዚአብሔር ይመስገን።

Friday, February 2, 2018

ወቅታዊ ጉዳይ

                           እውን ኢየሱስ (ሎቱ ስብሐት) “ሰይጥኗልን?”
ግቢያ
በየዘመኑ ኑፋቄንና ልዩ ወንጌልን የሚያስተምሩ ሰዎች በዋናነት ሐሳባቸው የሚያጠነጥነው የእውነተኛው ወንጌል ማእክል በኾነው በክርስቶስና በማዳን ሥራው ላይ ነው። ከክርስቶስና ከመስቀሉ ሥራ ላይ ዐይንን ማንሣት በቤተ ክርስቲያን፣ በአገር፣ በትውልድ፣ በቤተ ሰብ … ላይ የሚያመጣውን ድንዛዜ ዲያብሎስ በትክክል ያውቃል። ስለዚህ በየዘመናቱ ተመሳሳይ ክሕደቶችን ዘመን ቀመስ በማድረግና ከሰዎች ፍላጎት ጋር በማስተሳሰር፣ ይዘታቸውን በመለዋወጥና ሰፋ በማድረግ ሲያመጣ እናስተውላለን።

የስሕተቶቹ መልካቸውና ምንጫቸው ከኹለት አቅጣጫ ሊታይ ይችላል፤ የመጀመሪያው ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገረውን በትክክል ካለማጥናት ሲኾን፣ ኹለተኛው ደግሞ ሰውን ማእከል ያደረገውና የተዛባው የስሕተት ትምህርታቸው፣ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር ዝቅ የሚያደርግ ኾኖ ስለሚገኝ፣ ይህ እርሱን ያለመውደድ ውጤት ነው ብሎ መደምደም ይቻላል። ስለዚህም ስሕተታቸውን ስንቃወምና ኹለተኛውን ሐሳብ ለማፍረስ ስንሠራ፣ የዋሃንንና ባለማስተዋል የሳቱትን በርኅራኄ ለመመለስና ለማቅናት ደግሞ የፊተኛውን ሐሳብ እንይዛለን።

ዛሬ በኢትዮጵያ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ከሚታመሱባቸው የስሕተት ትምህርቶች መካከል “የእምነት እንቅስቃሴ” አንዱ ነው። ይህ የስሕተት ትምህርት በ1980ዎቹ ብቅ ብሎ በጊዜው ብዙ ትርምስ ፈጥሮ፣ በኋላ ላይ ከስሞ እንደ ነበር የሚታወስ ነው። ከኹለት ዐሥርት ዓመታት በኋላ ግን እንደ ገና በማንሠራራት ወደ ቤተ ክርስቲያን መድረክ ተመልሶ ቤተ ክርስቲያንን እያወከ ይገኛል።