Saturday, August 31, 2019

የዘመን ምስክር

READ PDF

አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ
ካለፈው የቀጠለ
መዝገበ ቃላት
ኪ.ወ.ክ. ሲነሡ ከስማቸው ጋር ተያይዞ በዋናነት የሚነሣው ዕውቅ ሥራቸው “መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ” ነው። የዚህ ንባቡ በግእዝ፣ ፍቺው በዐማርኛ የኾነ መዝገበ ቃላት ሥራ ጀማሪ በእርሳቸው ብርዕ፣ “በሮማውያን ዘንድ የከበሩ ትምህርት ከጥፈት ያስተባበሩ፥ በትምርታቸውም የተደነቁና የታወቁ፥ በሀገራቸው ግን እንደ ነቢያት የተናቁ እንደ ሐዋርያት የተጠቁ፥ እንደ ዮሴፍም ወንድሞቻቸው ጠልተው ተመቅኝተው ለማይረባ ዋጋ የሸጧቸው የአንኮበሩ ሊቅ” በማለት የተገለጡት መምህር ክፍለ ጊዮርጊስ ወልደ አባ ተክሌ ሲኾኑ፣ ፈጻሚው ደግሞ ኪ.ወ.ክ. መኾናቸው በመጽሐፉ ላይ ተጠቅሷል።

“ሥራን መንቀፍ በሥራ ነው እንጂ በቃል ብቻ መንቀፍ አይበቃም” የሚል ዐቋም የነበራቸው መምህር ክፍለ ጊዮርጊስ ይህን የግስ (የመዝገበ ቃላት) መጽሐፍ ለማዘጋጀት የተነሣሡት፣ ዲልማን የተባለው የውጭ አገር ሊቅ ያዘጋጀውን የግእዝ ግስ ከተመለከቱ በኋላ፣ በተለይ በሞክሼ ፊደላት (ሀሐኀ፣ ዐአ፣ ሠሰ እና ጸፀ) አጠቃቀም ላይ የታየውን ጕድለት በሥራቸው ለመንቀፍ (ትክክለኛውን ለማሳየት) ነው። ኾኖም ዲልማን የውጭ ዜጋ ኾኖ ግእዝን አጥንቶ መዝገበ ቃላት በማዘጋጀቱ ከፍ ያለ አክብሮትና አድናቆት እንደ ቸሩትም በመዝገበ ቃላታቸው ውስጥ እናነባለን። ሞክሼዎቹ ፊደላት እንደ ቀድሞው የድምፅ ልዩነት ባይኖራቸውም የመልክ ልዩነት ስላላቸውና ምስጢራቸውና ስማቸውም እንደ መልካቸው የተለያየ ስለ ኾነ ያ ተጠብቆ መጻፍ አለበት ይላሉ።

Thursday, August 29, 2019

የዘመን ምስክር


አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ
መግቢያ
በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ በተለይ የነገረ ሃይማኖት፣ የቋንቋና ሥነ ጽሑፍ፣ የባሕረ ሐሳብም (የዘመን ቍጥር) ጉዳይ ሲነሣ በጕልሕ ከሚጠቀሱት ሊቃውንት መካከል፣ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ግንባር ቀደም ናቸው። አንዳንዶች ስማቸውን በአኅጽሮት (ባጭሩ) ኪ.ወ.ክ. እያሉ ይጠራሉ። እኒህ የነገረ መለኮት፣ የሰዋስውና የመዝገበ ቃላት ሊቅ በዋናነት ነገረ ክርስቶስን አስመልክቶ በሚከተሉትና በኢትዮጵያ ቀዳሚው ኦርቶዶክሳዊ ባህለ ትምህርት በኾነውና ተቃዋሚዎቹ “ሦስት ልደት” (ጸጋ) እያሉ በሚጠሩት ባህለ ትምህርት ምክንያት በሥልጣን ላይ ያለው ቡድን በአንዳንድ ሥራዎቻቸው እየተጠቀመ ስማቸውን ግን በተገቢው መንገድ ለማንሣትና ተገቢውን ስፍራ ለመስጠት ቢቸገርም፣ ሊቅነታቸውን ግን በምንም መንገድ ሊያስተባብል አይችልም።

አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ከነገረ ክርስቶስ በተጨማሪ በአንዳንድ አስተምህሮቶችና ታሪኮች ላይም ለየት ያሉና አነጋጋሪ የሆኑ ጉዳዮችን በድፍረት ያቀርባሉ። ከዚህ የተነሣ እርሳቸውን ለማጣጣል የሚሞክሩ አንዳንድ ደፋሮች ባይጠፉም፣ እውነትን ደፍረው በመናገራቸውና እውነትን ይዘው ለብቻቸውም ቢኾን በመቆማቸው ተከታዮችና ደጋፊዎችን አላጡም። ስለ እርሳቸው ሊነገርና ሊጻፍ የሚገባው ብዙ ነገር ቢኖርም ጥቂቱንም እንኳ እንጻፍ ብንል ብዙ ይኾናል። በዚህ ጽሑፍ የገጠመንም ይኸው ነው። ለመኾኑ እኒህ ሊቅ ማናቸው? ሥራዎቻቸውስ የትኞቹ ናቸው? ለአገርና ለቤተ ክርስቲያን መታደስ ምን አበረከቱ? የሚሉትንና የመሳሰሉትን ጉዳዮች ቀጥሎ እንቃኛለን።