Sunday, April 26, 2020

ዕቅበተ እምነት


መድሎተ ጽድቅ በመድሎተ ጽድቅ ሲመዘን
ክፍል ዐምስት
“መድሎተ ጽድቅ” ለተሰኘውና እንደ ስሙ ኾኖ ላልተገኘው መጽሐፍ ባለፉት አራት ተከታታይ ዕትሞች ምላሽ እየሰጠን መቈየታችን ይታወቃል። በዚህ ዕትምም ምላሽ መስጠታችንን እንቀጥላለን። መጽሐፉ ባሰፈረው ቅደም ተከተል መሠረት የዚህ ዕትም ምላሽ በዋናነት በእኛ ጽሑፎች ላይ ለቀረበው ትችት የተሰጠ ምላሽ ሳይኾን፣ አጠቃላይ ነገር ላይ በማተኰር ጸሓፊው መርሕ ብሎ ላሰፈረው፣ ከመጥቀስ ባለፈ እርሱ ግን ለማይመራበት ጽሑፍ ምላሽ እንሰጣለን።
በ“መድሎተ ጽድቅ” ገጽ 46 ላይ «1.2 መኃትወ ታሪክ ዘመናፍቃን» በሚለው ዐቢይ ርእስ ሥር በሚገኘው «1.2.1.1 ሃይማኖት ምንድነው?» በሚለው ንኡስ ርእስ ሥር ስለ ሃይማኖት ምንነት በቀረበው ሐተታ ውስጥ የተነሡ አንዳንድ ነጥቦችን እንመለከታለን። በመጀመሪያ የምንመለከተው፣ “እግዚአብሔር ሃይማኖትን ሰጠ እኛ ደግሞ ተቀበልን። የሰው ልጅ ሃይማኖትን ይቀበላል እንጂ ሃይማኖትን ሊሠራ ወይም ሊያሻሽል አይችልም። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‘የሰጠኸኝን ቃል ሰጥቻቸዋለሁና፤ እነርሱም ተቀበሉት’ በማለት የገለጸው ይህን ነው። ዮሐ. 17፥8 እንዲሁም ‘ከዓለም ለሰጠኸኝ ሰዎች ስምህን ገለጥሁላቸው’ ያለው ለዚህ ነው። ስሙንም ማንነቱንም ሊገባን በሚችለው መጠን የገለጠልን ራሱ እግዚአብሔር ነው እንጂ ሃይማኖት የሰው ልጅ በምርምር የደረሰበት አይደለም። ዮሐ. 17፥6።