Saturday, December 21, 2013

ጋብቻ


የጋብቻ ትምህርት

“እግዚአብሔር መረጠ” (1ቆሮ. 1፥27)

“ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ልጁን ላከ፡፡” (ገላ. 4፥4) በአብርሃምና በሣራ፥ በይሥሐቅና በርብቃ፥ እንዲሁም በያዕቆብና በሚስቶቹ የጋብቻ ሕይወት ጥናታችን ውስጥ ግንኙታነቸው፥ ጥንካሬዎችና ድክመቶች እንደ ክርስቲያንነታችን ልንገነዘባቸው የቻልን የተለያዩ ትምህርቶች እንደ ነበሩ እናስታውሳለን፤ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር ውድ ልጁን በሕፃንነቱም ሆነ በወጣትነቱ ወቅት ሊያስተናግድ የሚችል ቤት ለመሥራት ምን ዐይነት ቤተ ሰብ መረጠ? እግዚአብሔር ለዚህ ታላቅ ነገር በሚመርጣቸው በእነዚህ ሰዎች ሕይወት ውስጥ እርሱን የሚያስደስቱ መልካም ባሕርያትን በርግጥ እናያለን፡፡ በዚህም የክርስቲያናዊ ጋብቻ ጥናታችንን መሆን በሚገባው መጠን ልናዳብረው እንችላለን፡፡

ፍሬ በአንድ ዕለት አይበስልም

ከጋብቻ ችግሮች ሁሉ የገንዘብ ዕጦት ዋናው እንደ ሆነ የሚታመን ቢሆን እግዚአብሔር ለልጁ እናት እንድትሆንለት ሀብታም ሴትን ወይም ባለጸጋ አሳዳጊ አባትን እንዳልመረጠ ልብ ማድረግ ይጠቅማል፡፡ ምክንያቱም ዮሴፍ፥ “ከናዝሬት መልካም ነገር ሊወጣ ይችላልንን?” በማለት ናትናኤል “በእውነት የእስራኤል ሰው” (ዮሐ. 1፥46) የተነገረላት የተናቀችዋ የናዝሬት ከተማ ኗሪ የሆነ ተራ ሠራተኛ ወይም ዕንጨት ጠራቢ ሰው ነበረና ነው፡፡ ማርያምም እንደ ዮሴፍ ሁሉ በናዝሬት ከተማ ትኖር የነበረች የዓለምን ነገር ገና ያልተገነዘበች ድንግል ነበረች፡፡ ልጇ የሚወለድበት ጊዜ ሲቀርብ ማርያምም ሆነች ዮሴፍ በራሱ ቅድመ አያቶች ከተማ በቤተ ልሔም በነበሩበት ጊዜም እንኳ ተመልሰው የሚገበቡት የራሳቸው የሆነ ንብረት ወይም ሀብት የነበረው የታወቀ ዘመድ አልነበራቸውም፡፡ ሕፃኑ የተወለደው በግርግም ውስጥ ነው፡፡ ሕፃኑን በቤተ መቅደስ ውስጥ ለጌታ ለመስጠት ወደ ኢየሩሳሌም ሲሄዱ መሥዋዕት ይዘው የሄዱት “ሁለት የዋልያ ወይም ሁለት የዕርግብ ጫጩቶችን” ነበር፡፡ እንደዚህ ዐይነቱ ስጦታ የጠቦት መሥዋዕት ማቅረብ የማይችሉ እጅግ የደኸዩ ሰዎች የሚያቀርቡት መሥዋዕት እንደነበር በሕግ መጽሐፍ ተጠቅሷል (ዘሌ. 12፥8)፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ከሰብአ ሰገል ጕብኝት ቀጥሎ በዚያን ጊዜ የይሁዳ ንጉሥ ከነበረው ከሄሮድስ የጭካኔ ሥራ ለማምለጥ ዮሴፍና ማርያም ወደ ግብጽ እንዲሄዱ ተነገራቸው፡፡ በዚያን ጊዜ ምናልባት ለችግራቸው ይሆናቸው ዘንድ የወርቅ ስጦታዎችን፥ ዕጣንና ከርቤ በእግዚአብሔር ርዳታ ሳያገኙ አልቀሩም፡፡ ለዚህ በተለየ መንገድ ለተመረጠ የኑሮ ጉድኝት በገንዘብ ችግር ምክንያት መጠለያ መጥፋቱ እግዚአብሔር፥ “የዚህን ዓለም ብልጽግና” አለመምረጡን የሚያመለክት ነው፡፡ ይህን ያደረገው ምናልባት ሁለቱ ዮሴፍና ማርያም ለሚያስፈልጋቸውና ለሚያጋጥማቸው ችግር ሁሉ በትሕትና መንፈስ በእርሱ ላይ ተደግፈው እንዲኖሩ በመፈለጉ ነው፡፡ “ገንዘብ ስለሌለን በኑሮአችን ውስጥ ሙሉ በሙሉ ለእግዚአብሔር መታዘዝ አንችልም” በሚል ሐሳብ የሚፈተኑ ክርስቲያን ባለትዳሮች ካሉ ከዚህ ቤተ ሰብ አኗኗር ይማሩ፡፡

Tuesday, December 10, 2013

መጽሐፍ ቅዱስ


የመጽሐፍ ቅዱስ ጠቅላላ ዕውቀት

መጽሐፈ ባሮክ
ካለፈው የቀጠለ

መግቢያ
ባሮክ የነቢዩን የኤርምያስን ቃል እየሰማ ይጽፍ የነበረ ወይም በዐጭር ቃል ኤርምያስንና የቃሉን ባለቤት እግዚአብሔርን በጸሓፊነት ያገለገለ የእግዚአብሔር ሰው እንደ ነበረ ይታወቃል (ኤር. 36፥1-8፤ 27፥32)፡፡

በኤርምያስ አንደበት እንደ ተነገረው የእግዚአብሔር ቃል፥ ናቡከደነፆር ያዘመተው የከለዳውያን ጦር ሠራዊት ምድረ ይሁዳን ከወረረ፥ የኢየሩሳሌምን ከተማ ከነቅጥሯ ከደመሰሰ፥ የቤተ መቅደሱን መገልገያ ዕቃዎች ከወሰደና ቤተ መቅደሱን ካቃጠለ በኋላ፥ የሕዝብ አለቆችንና ባለሙያዎችን ወደ ባቢሎን አፈለሰ፡፡ የደረሰውን ጥፋት አስቀድሞ በመተንበዩ በይሁዳ ንጉሥ በሴዴቅያስ ተግዞ የነበረውን ኤርምያስንም በነጻነት በፈለገው ስፍራ እንዲኖር ፈቀደለት (ኤር. 38፥17-18፤ 39፥11-14፤ 40፥1-6)፡፡

Tuesday, December 3, 2013

መሠረተ እምነት

ኢየሱስ ክርስቶስ ዐዲስ ኪዳን መካከለኛ
በጮራ ቊጥር 40 ላይ፡-
·        ኢየሱስ አሁን ጠበቃ ነው ወይስ ዳኛ?
·        1ዮሐ. 2፥1-2 ስለ ማን ይናገራል?
·        የኢየሱስ ጠበቃነት በምድራዊ ጥብቅና ይመዘናልን?
·        ኢየሱስ በአብ ቀኝ መቀመጡ መካከለኛነቱን አስቀርቶታልን?
·        ቅዱሳን መካከለኞች አይደሉምን?  
በሚሉ ዐምስት ንኡሳን አርእስት ሥር የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ መሆኑን ከእግዚአብሔር ቃል ማስረጃዎችን በማቅረብ ማብራሪያ ተሰጥቷል። በዚህ ዕትም ደግሞ የዕብራውያንን መልእክት መሠረት በማድረግ የክርስቶስን መካከለኛነት እንመለከታለን። በቅድሚያ ግን ለዐዲስ ኪዳን መካከለኛ ለሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ጥላና ምሳሌ ስለ ሆኑት የብሉይ ኪዳን መካከለኞች ስለ ነበሩት ሊቃነ ካህናት መሠረታውያን ነገሮችን እንዳስሳለን። ከዚህ በፊት ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናትነት በጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ቊጥር 23 በስፋት መጻፉን ለአንባብያን መጠቈም እንወዳለን።

የካህናት ሹመትና አገልግሎት በብሉይ ኪዳን
የዕብራውያን መልእክት “ሊቀ ካህናት ሁሉ ስለ ኀጢአት መባንና መሥዋዕትን ሊያቀርብ ከሰው ተመርጦ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ ስለ ሰው ይሾማልና፤” (ዕብ. 5፥1) በማለት፥ ስለ ሊቀ ካህናት ማንነት፣ ሊያሟላ ስለሚገባው መስፈርትና ስለሚሰጠው አገልግሎት የሚናገር ቃል እናነባለን። በዚህ ጥቅስ ውስጥ ሊቀ ካህናት ሆኖ የሚሾመው፡-
·        ከሰው ተመርጦ መሆኑን፣
·        ስለ ኀጢአት መባንና መሥዋዕትን ለማቅረብ መሆኑን እና
·        ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ ላይ ስለ ሰው የሚሾም መሆኑን
እንገነዘባለን። ጥቅሱ ስለ ብሉይ ኪዳን ካህናት ማንነት፣ ስለሚሾሙበት ምክንያትና ስለሚወክሉት ወገን ይናገራል ማለት ነው። “ከሰው ተመርጦ” የሚለው፥ ሊቀ ካህናት የሚሆነው የመላእክት ወገን ሳይሆን የሰው ወገን መሆኑን ሲያስረዳ፥ መራጩም አካል ሌላ [እግዚአብሔር] እንጂ ካህኑ ራሱን በራሱ ሊመርጥ ወይም ሊሾም እንደማይችል ያመለክታል። “እንደ አሮንም በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር ማንም ክብሩን ለራሱ የሚወስድ የለም” (ቊጥር 4)።

Thursday, November 21, 2013

ርእሰ አንቀጽ

ይህን ዓመት ደግሞ ተዋት!

የእያንዳንዱ ቅጽበት፥ ሰኮንድ፥ ደቂቃ ትዝታ ይህን ያህል ጐልቶ በተናጠል በአእምሮኣችን ባይመዘገብም፤ በሰዓት፥ በቀን፥ ከዚያም በወርና በዓመት እየተጠቃለለና የራሱን ድምር ትዝታ እየተወ ሲያልፍ ኖሮአል፡፡ ያለፈው ሁሉ ታሪክ ሆኖአል፤ ተጽፎአል፤ ተነቦም መዝገብ ቤት ይቀመጥ ተብሏል፡፡ አብዛኛው ሰው ባለፈው ቀን ትዝታ ላይ ሙሉ ጊዜውን ከሚያሳልፍ ይልቅ በሚመጣው ቀን ምን እንደሚያጋጥመው ዐውቆ ለመዘጋጀት በእጅጉ ይጥራል፡፡ ብርቱ ፍላጎትም ያለው ስለ ወደ ፊቱ ዕቅድ መሳካት ነው፡፡ ይህንም የሰው ልጅ ፍላጎት የተረዱ ብልጣብልጥ የኅብረተሰብ አባላት መጪውን ዕድልህን ልንነግርህ እንችላለን እያሉ የዋሁን ሕዝብ ለዘመናት ገንዘቡንና ጊዜውን በዘበዙት፤ ሥነ ልቡናውንም ሰለቡት፡፡

እንደዚህ የመሳሰለው አካባቢያዊ ተጽዕኖ ከሚቀሰቅሰው ውስጣዊ ግፊት የተነሣ ሰዎች ከአሮጌው ዓመት ትዝታ ይልቅ ለመጪው ጊዜ ምን ይሁንታ ቅድሚያ ይሰጣሉ፡፡ ስለዚህም ለመጪው ዓመት ብሩህ ተስፋ እውን መሆን ሲሉ ጠንክሮ ለመሥራት በሙሉ ዕውቀታቸውና ኀይላቸው ይዘጋጃሉ፡፡ ስለዚህም በየዓመቱ መጀመሪያ ለዐዲሱ ዓመት እንኳን አደረሰህ! አደረሰሽ! በመባበል የመልካም ምኞት መግለጫ ይለዋወጣሉ፡፡ ስለ ዐዲሱ ዓመት እንጂ ስላለፈው ግድ የሚኖረው ያለ አይመስልም፡፡ ላለፈው ክረምት ቤት አይሠራለትምና፡፡

Thursday, November 14, 2013

መሠረተ እምነት


ከነቅዐ ጥበብ
ባለፈው ዕትም ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት በቀረበው ጽሑፍ፦ አምላክ ሰው የሆነበትን ምክንያት፣ ቃል ሥጋ የመሆኑን አስፈላጊነት፣ የክርስቶስ አዳኝነትና መካከለኛነት ተያያዥ መሆናቸውን በማብራራት፥ የኢየሱስ ክርስቶስን መካከለኛነት ለማስተባበል በዚህ ዘመን የሚነዙ የስሕተት ትምህርቶችን ለመጠቈም ተሞክሯል፡፡ በዚሁ መሠረት ኢየሱስ አሁን ፈራጅ እንጂ አማላጅ አይደለም የሚለውንና ሮሜ 8፥34 ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት የሚያስተምረውን በመጠኑ ተመልክተናል፡፡ በዚህ ዕትም ደግሞ ተከታዩ ክፍል ይቀርባል፡፡

ኢየሱስ አሁን ጠበቃ ነው ወይስ ዳኛ?
ወደ መጽሐፍ ቅዱስ እውነት ለመድረስ ከራሱ ከመጽሐፍ ቅዱስ መጀመር የግድ ነው፡፡ "ትንሽ ቆሎ ይዞ ወደ አሻሮ መጠጋት" እንደሚባለው ብሂል፥ የራስን አመለካከት ወይም ሌላ ምድራዊ ተመክሮን ይዞ ወደ መጽሐፍ ቅዱስ መጠጋት፥ የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ለመቀበል ሳይሆን፥ መጽሐፍ ቅዱስን ለራስ ሐሳብ ደጋፊ አድርጎ ለማቅረብ ያለመ አካሄድ ነው፡፡

Sunday, November 3, 2013

የዘመን ምስክር


በዚህ ዐምድ ለቤተ ክርስቲያን መሻሻልና መለወጥ የተጋደሉ፥ ለአገርና ለወገን የሚጠቅም መልካም ሥራን የሠሩ አበውን ሕይወትና የተጋድሎ ታሪክ አሁን ላለውና ለቀጣዩ ትውልድ አርኣያ እንዲሆን እናስተዋውቃለን፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ (1902-1971 ዓ.ም.)
ያለ መንፈስ ቅዱስ አብርሆት የእግዚአብሔርን ቃል ማስተዋልና መለወጥ እንደማይቻል የታወቀ ነው። እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ሲናገር፥ ሰው ሊሰማ ይችላል፤ ነገር ግን ያ ሰው ቃሉን የሚያስተውለውና በቃሉ ተለውጦ ዐዲስ ፍጥረት የሚሆነው፥ የተዘጋው የልቡናው በር በእግዚአብሔር ቃል ሲንኳኳና በመንፈስ ቅዱስ አብርሆት መከፈት ሲችል ብቻ ነው። ልድያ የተባለችው የትያጥሮን ሴት፥ ጳውሎስ የሚናገረውን ታዳምጥ ዘንድ ጌታ ልቧን ከፍቶላት ነበርና በሰማችው ቃል ሕይወቷ ተለወጠ (ሐ.ሥ. 16፥14-15)። የቅዱስ ጳውሎስ ድርሻ ቃሉን መናገር እንጂ እርሷን ማሳመን አልነበረም፤ ልቧን ከፍቶ ቃሉን እንድታደምጥና በቃሉ እንድታምን ያደረገው ጌታ ነው። ይህ ትናንትም ሆነ ዛሬ እግዚአብሔር ሰዎችን ለመለወጥና ዐዲስ ፍጥረት ለማድረግ የሚጠቀምበት ድንቅ አሠራሩ ነው።

መማርና ማወቅ ለሰው መልካም ነገሮች ቢሆኑም፥ የእግዚአብሔርን እውነት ለማስተዋል ግን ከላይ እንደ ተገለጸው የመንፈስ ቅዱስ አብርሆት ያስፈልገዋል። የፍጥረታዊ ሰው ልብ ብርሃን እግዚአብሔር እስኪበራበት ድረስ ጨለማ ነው (ሮሜ 1፥21፤ ኤፌ. 5፥8)። በዚህ ጨለማ ልብ ውስጥ እግዚአብሔር ካልበራ (መዝ. 118፥27) በቀር ፍጥረታዊው ሰው እግዚአብሔርንም ሆነ የእግዚአብሔርን ፈቃድና ሐሳብ ሊገነዘብ አይችልም (1ቆሮ. 2፥14)። ስለዚህ ሰው ያስተውል ዘንድ እግዚአብሔር በጨለመው የሰው ልብ ውስጥ ብርሃኑን ያበራል (መዝ. 18፥28፤ 2ቆሮ. 4፥4-6)። ሰውም በልቡ በበራው ብርሃን እየተመራ የእግዚአብሔርን እውነት ያስተውላል (መዝ. 36፥9)።

Monday, October 28, 2013

ንግባዕኬ ኀበ ጥንተ ነገር



ወደ ቀደመው ነገር እንመለስ በተሰኘው በዚህ ዐምድ መጽሐፍ ቅዱሳዊውን ትምህርት የበረዙና የከለሱ የስሕተት ትምህርቶችን ከመጽሐፍ ቅዱሳዊው እውነት ጋር አንባቢው እንዲያነጻጽር ይቀርባሉ፡፡ 
         
         ማኅሌተ ጽጌ                                     መጽሐፍ ቅዱስ                                                      
በከመ ይቤ መጽሐፍ ማእከለ ፈጣሪ ወፍጡራን፡፡                አሐዱ እግዚአብሔር ወአሐዱ ኅሩይ ማእከለ እግዚአብሔር ወሰብእ
ለዕረፍት ዘኮንኪ ትእምርተ ኪዳን፡፡                              ኢየሱስ ክርስቶስ ዘኮነ ሰብአ፡፡ ዘመጠወ ርእሶ ቤዛ ኵሉ፡፡
ሰንበተ ሰንበታት ማርያም ዕለተ ብርሃን፡፡          
ብኪ ይትፌሥሑ ዘገነተ ጽጌ ጻድቃን፡፡                              ትርጕም፡-
ወብኪ ይወፅኡ ኃጥኣን እምደይን፡፡                               አንድ እግዚአብሔር አለና፤ በእግዚአብሔርና በሰው መካከል
                                                                      ያለው መካከለኛው ደግም አንድ አለ፡፡
ትርጕም፡-                                                           እርሱም ሰው የሆነ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፤ ራሱንም ለሁሉ ቤዛ ሰጠ፡፡
መጽሐፍ እንዳለ በፈጣሪና በፍጡራን መካከል                                                               (1ጢሞ. 2$5-6)፡፡
ለዕረፍት የምልክት ኪዳን የሆንሽ
የሰንበታት ሰንበት ማርያም ሆይ!
አንቺ የብርሃን ዕለት ነሽ፡፡
አበባ በሞላበት ገነት ውስጥ ያሉ ጻድቃን በአንቺ ደስ ይላቸዋል፡፡
በአንቺም ኃጥኣን ከሥቃይ ስፍራ (ከሲኦል) ይወጣሉ




     
(ዘአለቃ ታየ ገብረ ማርያም)
አልቦ ካልዕ ስም ወአልቦ ካልዕ ፍኖት
እንበለ ስሙ ለክርስቶስ ዘይወስድ ኀበ ሕይወት
ወኢበመኑሂ እምፍጡራን ኢይትረኃው አንቀጸ ገነት
ኢበቅዱሳን አበው ወኢበመላእክት
እስመ ሎቱ ለባሕቲቱ ዘሰማይ መንግሥት
(ከመዝሙረ ክርስቶስ  ገጽ 71 የተወሰደ)

ትርጕም
ሌላ ስምና ሌላ መንገድ የለም፤
ወደ ሕይወት የሚወስድ ያለ ክርስቶስ ስም፡፡
ከፍጡራን በማንም የገነት በር አይከፈትም
በቅዱሳን አበው ወይም በመላእክት
የእርሱ ብቻ ነውና ሰማያዊው መንግሥት፡፡

(በጮራ ቍጥር 39 ላይ የቀረበ)

Monday, October 14, 2013

መሠረተ እምነት


ክርስቶስ ኢየሱስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ

መንደርደሪያ
በሕክምናው ዓለም በሰው ውስጥ ያሉና የተለያዩ በሽታዎችን የሚያመጡ ተሐዋስያን ለምሳሌ፡- ባክቴሪያዎች በተለያዩ ምክንያቶች ከሚገድላቸው መድኀኒት ጋር የሚላመዱበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡ ከመድኀኒቱ ጋር ከተላመዱ ደግሞ የመድኀኒቱን የፈዋሽነት ዐቅም ያዳክማሉ፡፡ ሊያጠፉትም ይችላሉ፡፡ በዚህ ምክንያት የበሽተኛው ጤና ይቃወሳል፡፡ እንዲህ በሚሆንበት ጊዜ ጠቢባኑ$ ተሐዋስያኑ ከመድኀኒቱ ጋር የተላመዱበትን ምክንያት በመለየት መፍትሔ ይፈልጋሉ፡፡ ከመፍትሔዎቹ አንዱ ከቀድሞው የተሻለ ፈዋሽነት ያለውና ተሐዋስያኑን ሊያጠፋ የሚችል መድኀኒት መቀመም ወይም ማዘጋጀት ነው፡፡

ስለ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መካከለኛነት መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽና በማያሻማ መንገድ ያስተምራል፡፡ ይሁን እንጂ ይህን እውነት ለማስተሐቀር (ለማቃለል) የሚሞክሩ ከሓድያንና መናፍቃን ትናንት ነበሩ፤ ዛሬም አሉ፤ ለወደ ፊቱም ይኖራሉ፡፡ በጮራ መንፈሳዊ መጽሔት በተለያዩ ዕትሞች ስለ ክርስቶስ መካከለኛነት በልዩ ልዩ መንገድ ትምህርት ሲቀርብ መቈየቱን አንባብያን ያስታውሳሉ ብለን እናምናለን፡፡ ይሁን እንጂ ከመድኀኒቱ ጋር እንደሚላመዱ ተሐዋስያን$ በርእሰ ጕዳዩ ላይ ዛሬም መልካቸውን የቀየሩና የሚያደናግሩ የሚመስሉ ኢመጽሐፍ ቅዱሳውያን ትምህርቶች እንዳዲስ እየቀረቡ ይገኛሉ፡፡ በተለያዩ መንገዶች እየተስተባበለ ያለውን የክርስቶስን መካከለኛነት$ በአሁኑ ጊዜ እየቀረበ ካለበት ስልት አንጻር፣ መጽሐፍ ቅዱስ በሚያስተምረውና የቤተ ክርስቲያን አበውም መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርገው በሚሰጡት ምስክርነት ላይ የተመሠረተ ትምህርት ማቅረብ አስፈልጓል፡፡

Friday, October 4, 2013

ርእሰ አንቀጽ


እስከ መቼ?

የሰው ልጅ በኑሮው ውስጥ እውነተኛ ፍርድን ይፈልጋል፡፡ የክፉዎች ተራ ሲያበቃና እውነት ስፍራዋን ስትይዝ ማየት ይናፍቃል፡፡ እውነትን ሁሉም ጥቁር ካባ ሲያለብሳት፥ እውነተኞች ጥላሸት ሲቀቡ ማየት ለእውነተኞች ሕመም አለው፡፡ እውነት በሌለበት ፍርድ የለምና እውነትና ፍርድ በጠፋበት ዓለም ላይ እውነተኞች ፍርድን ከሰማይ ይናፍቃሉ፡፡ የሰማዩ ፍርድ የዘገየ ሲመስልም እስከ መቼ? ይላሉ፡፡ ዐልፎ ዐልፎ የእውነት ጊዜ ብልጭ ይልና ብዙ ሳያጣጥሙት ቶሎ ድርግም ይልባቸዋል፡፡ የሐሰት ዘመን ሲረዝምባቸውም በሐዘን ድምፅ እስከ መቼ? ይላሉ፡፡

ሰው ስለ እውነት ከእግዚአብሔር ካልተማረ÷ ኑሮው የሚያስተምረው ጥቂቱን ነው፡፡ የእድሜ ርዝማኔም በራሱ የእውነትን ዕውቀት ለመግለጽ የሚያደርገው አስተዋፅኦ ብዙ አይደለም፡፡ የታሪክ ክምርም ወደ እውነት አያደርስም፡፡ ወደ እውነት ለመድረስ እግዚአብሔር የዘመን ደወል ያደረጋቸውን እውነተኞቹን መምህራን ማድመጥ ይጠይቃል፡፡

Tuesday, October 1, 2013

መጽሐፍ ቅዱስ


የመጽሐፍ ቅዱስ ጠቅላላ ዕውቀት

ከሁሉን መርምር

በአንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥራዝ በብሉይ ኪዳን መጨረሻ ከገጽ 721-1037 በሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ጥራዞች የማይገኙ መጻሕፍት በመጨመራቸው ተጨንቀውና ግራ ተጋብተው ያውቃሉን? “ተጨማሪ (ዲዮትሮካኖኒካል) የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት” በሚል የክፍል መጠሪያ የተጨመሩት መጻሕፍት ዐሥራ ዐምስት ናቸው፡፡

በውሳኔ የተጨመሩት መጻሕፍት የሚገኙበት ጥራዝ በአንዳንድ ሰዎች ዘንድ እንደ ሙሉ መጽሐፍ ቅዱስ ሲቈጠር እነርሱ የሌሉበት ጥራዝ ግን “ጐዶሎ መጽሐፍ ቅዱስ” ተብሎ ሲጠራ ተሰምቷል፡፡

Monday, September 23, 2013

አለቃ ነቅዐ ጥበብ


አለቃ ነቅዐ ጥበብና አገልግሎታቸው

አለቃ ነቅዐ ጥበብ በመካከል ካለችው ከአሮጌዋ አትሮንስ ፊት ለፊት ተቀምጠዋል፡፡ አለቃ ደምፀ ቃለ አብ በስተቀኛቸው የኔታ ማኅተመ ሥላሴም በስተግራ አጐዛና ሰሌን በተነጠፈበት መደብ ላይ ጕብ ብለዋል፡፡ ቀሳውስት፥ ዲያቆናትና ምእመናን የአለቃን እልፍኝ አጨናንቀዋታል፡፡ ከጥማት ለመርካት በምንጭ ዙሪያ የተሰለፉ ዋልያዎችን ሁኔታ የሚያስታውስ ትዕይነት ነበር (መዝ. 41/42፥1)፡፡

በጉባኤው የተገኙ ዐዳዲስ ታዋቂ ዕድምተኞችም ነበሩ - መሪ ጌታ ንዋይ ሲሞን፥ አጋፋሪ ዕንባቆም ኀይለ ልዑልና ተማሪ የማነ ብርሃን፡፡ የሁሉም ዐይኖች በመሪ ጌታ ንዋይ ሲሞንና በአለቃ ነቅዐ ጥበብ ላይ በየተራ ያርፉ ነበር፡፡

Saturday, September 14, 2013

ጋብቻ


የጋብቻ ትምህርት

የእግዚአብሔር ሥራ ምን ጊዜም መልካም ነው
የሰው ባሕርይ ከቤተ ሰቡ የተወረሱ ድክመቶችን የሚያንጸባርቀው በሁለት ተቃራኒ መንገዶች ሊሆን ይችላል፡፡ የአባቶች ድክመቶች ምናልባት ባለማወቅ የሚደጋገሙና የበለጠ እየተባባሱ የሚሄዱ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ወይንም በራሳቸው ውሳኔ ወደ ሰፋ ልዩነት የተሻለ እንቅስቃሴ ለማድረግ በሚፈልጉ ተከታይ ትውልዶች ግልጽ ተቃውሞ ይገጥማቸው ይሆናል፡፡

አብርሃም ልጅ ስላልወለደ ተጨንቆ በአንድ ወቅት አባ ወራነቱን ትቶ የሣራን አስተሳሰብ በመከተል ድክመቱን ሲገልጥ፥ ልጁ ይሥሐቅ ከሚስቱ ከርብቃ ጋር ስለ ልጆቻቸው የሚጸናና የሚዘወተር አለመግባባትን ለመቈጣጠር ባለመቻሉ የባሰውን ድክመት አሳየ፡፡ የይሥሐቅ ታናሽ ልጅ ያዕቆብ ግን በወላጆቹ የተለመደ ድክመት እንዳይደገም በሌላ አቅጣጫ ሲሄድ በዚህ ጽሑፍ እንመለከታለን፡፡

Wednesday, September 4, 2013

የዘመን ምስክር


በዚህ ዐምድ ለቤተ ክርስቲያን መሻሻልና መለወጥ የተጋደሉ፥ ለአገርና ለወገን የሚጠቅም መልካም ሥራን የሠሩ አበውን ሕይወትና የተጋድሎ ታሪክ አሁን ላለውና ለቀጣዩ ትውልድ አርኣያ እንዲሆን እናስተዋውቃለን፡፡


አለቃ ታየ ገብረ ማርያም (1853 - 1916 ዓ.ም.)
አይሁድ መሲሑን ይጠባበቁ የነበሩ ሕዝብ ናቸው፤ መሲሑ ሲመጣ ግን አልተቀበሉትም፡፡ የመሲሑን ደቀ መዛሙርትም አሳድደዋል፡፡ እነርሱን መስሎ የሚኖረውን ሰው እውነተኛ አይሁዳዊ ሲሉ፥ ዐዲስና እንግዳ ትምህርትን ሳያመጣ በመጽሐፋቸው የተገለጠውንና እነርሱ ያላስተዋሉትን እውነት የሚያምነውንና የሚኖረውን የመሲሑን ተከታይ ደግሞ መናፍቅ እያሉ ሲኰንኑ ኖረዋል፡፡

ሳውል፥ በጊዜው በሕዝብ ሁሉ ዘንድ የከበረ የሕግ መምህር በነበረው በገማልያል እግር ሥር ተቀምጦ የተማረ ሊቅ እንደ መሆኑ በዚያው ሥርዐት ሲኖር እጅግ የተከበረ ሰው ነበረ (ፊል. 3፥5-6)፡፡ ክርስቶስ ከተገለጠለትና በወንጌል አምኖ የእርሱው አገልጋይ ከሆነ በኋላ ግን፥ የቀድሞ ክብሩን ዐጥቶ አሳዳጁ ሲሰደድና ሲንገላታ፥ አለሥራውም ክፉ ስም ሲወጣለት ነበር፡፡ ቀድሞ ያከበሩት ወገኖች፥ “ይህ ሰው በሽታ ሆኖ በዓለም ባሉት አይሁድ ሁሉ ሁከት ሲያስነሣ፥ የመናፍቃን የናዝራውያን ወገን ሆኖ አግኝተነዋልና፤ መቅደስንም ሊያረክስ ሲሞክር ያዝነው” (ሐ.ሥ. 24፥1-9) ሲሉ በሐሰት ከሰዉታል፡፡ እርሱም ለቀረበበት ክስ በሰጠው ምላሽ፥ “በሕጉ ያለውን በነቢያትም የተጻፉትን ሁሉ አምኜ የአባቶቼን አምላክ እነርሱ ኑፋቄ ብለው እንደሚጠሩት መንገድ አመልካለሁ፡፡ እነዚህም ራሳቸው ደግሞ የሚጠብቁት ጻድቃንም ዐመፀኞችም ከሙታን ይነሡ ዘንድ እንዳላቸው ተስፋ በእግዚአብሔር ዘንድ አለኝ ” (ቊጥር 10-21) ብሏል፡፡

Monday, August 26, 2013

ርእሰ አንቀጽ



ደጁ ለጌታ ይከፈት


ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስ በክቡር ደሙ የዋጃት የብቻው ገንዘቡ ናት። እንደ ተጻፈውም፣ “አካሉና ሁሉን በሁሉ የሚሞላ የእርሱ ሙላቱ ናት(ኤፌ. 1፥23) የቤተ ክርስቲያን መሠረት ክርስቶስ ነው፤ ማእከሏም ክርስቶስ ነው፤ ራሷም ክርስቶስ ነው። ቤተ ክርስቲያንን ቤተ ክርስቲያን የሚያሰኛት ቅሉ ክርስቶስን መሠረቷ፣ ማእከሏና ራሷ ማድረጓ ነው፤ ያለ ክርስቶስ ከሆነች ግን “ቤተ ክርስቲያን ነኝ” ማለቷ መንፈሳዊ ትርጕም ያጣል። ብዙ ነገር አለኝ ብትል እንኳ ያለ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ባዶ ስብስብ ትሆናለች። ክርስቶስን ኹለንተናዋ ያላደረገች ቤተ ክርስቲያን እንዴት ምስኪን ናት!

በምድር ላይ የምትገኘው ቤተ ክርስቲያን፣ ራሷንና ጌታዋን ክርስቶስን ከውስጧ አስወጥታ በራሷ ነገር ልትሞላና እርሱን በአፍኣ (በደጅ) ልታቆመው ትችላለች። በራእየ ዮሐንስ ውስጥ ከተጠቀሱት ሰባት አብያተ ክርስቲያናት መካከል የሎዶቅያ ቤተ ክርስቲያን ይህን ትልቅ ስሕተት ፈጽማ ነበር። ለዚህ ነው ጌታ፣ “እነሆ በደጅ ቆሜ አንኳኳለሁ፤ ማንም ድምፄን ቢሰማ ደጁንም ቢከፍትልኝ፥ ወደ እርሱ እገባለሁ፤ ከእርሱም ጋር እራት እበላለሁ፤ እርሱም ከእኔ ጋር ይበላል” ሲል ለቤተ ክርስቲያኒቱ የክፈችልኝ መልእክት ያስተላለፈው (ራእ. 3፥20)።

የሎዶቅያ ቤተ ክርስቲያን ጌታዋን ከውስጧ አውጥታ በደጅ እንዲቆም ለምን አደረገች? ለቤተ ክርስቲያኒቱ መልአክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባስተላለፈው የንስሓ መልእክት ውስጥ እንደ ዘረዘረው፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ለእኔ ጌታ አያስፈልገኝም ባይ ሳትሆን አልቀረችም። ጌታ ከውስጧ ወጥቶ በደጅ እንዲቆም ያደረገውም ዋና ነገር ይህ እንደ ሆነ መገመት አያስቸግርም። ጌታ እንደ ተመለከታት ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ “ሀብታም ነኝና ባለጠጋ ሆኜአለሁ፤ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም” ባይ ነበረች፤ ይሁን እንጂ፦ ጐስቋላ፣ ምስኪን፣ ድኻ፣ ዕውር፣ የተራቈተችም መሆንዋን አላወቀችም ነበር (ቍጥር 17)። ባለጠጋ ሳትሆን ባለጠጋ ነኝ፤ ብዙ የጐደላት ነገር እያለ አንዳች አያስፈልገኝም ማለቷና ጌታን በደጅ ማቆሟ የቤተ ክርስቲያኒቱ ውድቀት ከፍ ያለ መሆኑን ያሳያል። አፍቃሪዋ ጌታ ግን ወደ እርሷ ለመግባት በደጅ ቆሞ እያንኳኳ ነበር። ለእርሷ ያልታወቃት ጕስቍልናዋ፣ ምስኪንነቷና ድኽነቷ እንዲወገድና በብልጽግና እንዲተካ “በእሳት የነጠረውን ወርቅ”፣ የለበሰች ሲመስላት ኀፍረቷ እንዳይገለጥ “ነጭ ልብስን”፣ የምታይ ሲመስላት ለታወሩት ዐይኖቿ የምትኳለውን ኵል ከእርሱ እንድትገዛ መክሯታል (ቍጥር 18)። ለቤተ ክርስቲያኒቱ መልአክ “ከእኔ እንድትገዛ እመክርሃለሁ” ነው ያለው፤ ይህም የቤተ ክርስቲያን ችግር የሚፈታውና ጕድለቷ የሚሟላው ከጌታ ዘንድ ብቻ መሆኑን ያሳያል።




እንደ ሎዶቅያ ቤተ ክርስቲያን ዛሬም ጌታን ከውስጧ ያወጣችውና በአፍኣ ያቆመችው፣ የእርሱን ስፍራም በሌሎችና በምድራዊ ጕዳዮች ያስያዘች፣ ያለች ሲመስላት የሌለች፣ ባለጠጋ እንደ ሆነች የምታስብ፣ ነገር ግን የተጐሳቈለች፣ ዐይናማ ነኝ ስትል ማየት የተሳናት ቤተ ክርስቲያን መፍትሔዋን ከሌላ ዘንድ ብትፈልግ ችግሯን ማባባስ እንጂ መፍትሔ አታመጣም። መፍትሔው ሳታመነታና ሳትዘገይ “አታስፈልገኝም” ብላ በአፍኣ ያቆመችውን ጌታዋን አሁኑኑ ይቅርታ ጠይቃ ደጇን ከፍታለት ግባ ማለት ይገባታል። በተሰጣት ዕድል ተጠቅማ ደጇን ካልከፈተችለት ግን ፍጻሜዋ የከፋ ይሆናል። “በራድ ወይም ትኩስ እንዳይደለህ ሥራህን ዐውቃለሁ። በራድ ወይም ትኩስ ብትሆንስ መልካም በሆነ ነበር። እንዲሁ ለብ ስላልህ፥ በራድም ወይም ትኩስ ስላልሆንህ ከአፌ ልተፋህ ነው” የሚል ብርቱ ማስጠንቀቂያ ለሎዶቅያ ቤተ ክርስቲያን መሰጠቱን መዘንጋት የለብንም (ቍጥር 15-16)።
  
በማሕልየ መሓልይ ውስጥ እንደምናነበው፣ ውዷ በደጅ ቆሞ እኅቴ፥ ወዳጄ፥ ርግቤ፥ መደምደሚያዬ ሆይ፥ በራሴ ጠል፥ በቈንዳላዬም የሌሊት ነጠብጣብ ሞልቶበታልና ክፈችልኝ” ሲላት በጊዜው፣ “እኔ ተኝቻለሁ፤ ልቤ ግን ነቅቷል” የምትለው ሙሽራዪቱ የውዷ ቃል መሆኑን ብታውቅም ተነሥታ ላለመክፈት ምክንያቶቿን በመደርደር፣ “ቀሚሴን አወለቅሁ እንዴት እለብሰዋለሁ? እግሬን ታጠብሁ እንዴት አሳድፈዋለሁ?” እያለች ጊዜያቶችን አሳለፈች። ለራሷ ምቾት እንጂ በጠልና በሌሊት ነጠብጣብ ለራሰው ውዷ ቅድሚያ አልሰጠችውም። እርሱም እንዳልከፈተችለት ባየ ጊዜ ማንኳኳቱን ትቶ ፈቀቅ አለ። ዘግይታ ግን ተነሣችና ከፈተችለት፤ ይሁን እንጂ ውዷን አላገኘችውም። ብትጠራውም አልመለሰላትም። እርሱን ፍለጋ በሌሊት ብትወጣም የተረፋት በከተማዪቱ ጠባቂዎች መደብደብ፣ መቍሰልና የዐይነ ርግብ መሸፈኛዋን መነጠቅ ሆነ። ከዚያ የጠፋውን ውዷን የማፈላለጉን ሥራ ቀጠለች (ማሕ. 5፥2-8)። ዛሬም ቤተ ክርስቲያን በደጅ ቆሞ ለሚያንኳኳው ውዷ ለክርስቶስ ደጇን መክፈት አለባት። ካልከፈተችለት ውዷ ፈቀቅ ሊል ይችላል። ያለእርሱ የምታደርገው ማንኛውም እንቅስቃሴዋ ሁሉ ከንቱ፣ ምድራዊና እዚሁ ምድር ላይ ቀሪ ነው የሚሆነው።

ቤተ ክርስቲያን በልዩ ልዩ ምክንያት ውዷን ክርስቶስን ከውስጧ አውጥታ በደጅ አቁማዋለች። የራሷን ዝናና ጥንታዊነት ስትተርክ፣ “እኔ ከሁሉ ቀዳሚ ነኝ፤ ሁሉ አለኝ፤ አንዳች አያስፈልግኝም” ስትል፣ በገዛ ደሙ የዋጃትን የእርሱን ብቸኛ ቤዛነት መስበክ ትታ ሌሎችን ቤዛዎች አድርጋ ስትሰብክ፣ እስትንፋሰ እግዚአብሔር የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስን ብቻ መመሪያዋ ማድረግ ሲገባት፣ እርሱን ቸል ብላ ሌሎች ድርሳናትን መመሪያዋ ስታደርግ፣ በእርሷ ዘንድ ስፍራ ያላገኘው ጌታ ከውስጧ ወጥቷል። በደጅ ቆሞም እንድትከፍትለትና እንዲገባ እያንኳኳ ይገኛል። ይሁን እንጂ ቤተ ክርስቲያን፣ በማሕልየ መሓልይ ላይ እንደ ተጠቀሰችው ሙሽሪት፣ ለሚያንኳኳው ጌታ ላለመክፈት፦ ጥንታዊነቴ፣ ታሪኬ፣ ትውፊቴ፣ አስተምህሮዬ፣ ሥርዐቴ፣ ባህሌ፣ ልማዴ፣ ወዘተ. እያለች ውዷን ላለማስገባት በደጅ አቁማው እያንገራገረች ትገኛለች። ቤተ ክርስቲያን የእነዚህ ሁሉ ዕሴቶች ባለቤት ብትሆንም፣ ዕሴቶቹን ለጌታ ክብር ካላዋለቻቸውና የእርሱን አዳኝነት ላልሰሙት ለማሰማት ካልተጠቀመችባቸው ጥቅም የላቸውም፤ እዚሁ በምድር ላይ ቀሪዎች ናቸው። ይሁን እንጂ ጌታ ዛሬም ከውስጧ አውጥታ በደጅ ያቆመችውን ቤተ ክርስቲያን፣ “እነሆ በደጅ ቆሜ አንኳኳለሁ፤ ማንም ድምፄን ቢሰማ፥ ደጁንም ቢከፍትልኝ፥ ወደ እርሱ እገባለሁ፤ ከእርሱም ጋር እራት እበላለሁ፤ እርሱም ከእኔ ጋር ይበላል” ሲል የፍቅር ድምፁን እያሰማት ይገኛል (ራእ. 3፥20)።

እኛም የክርስቶስ ሙሽራ የሆንሽ ቤተ ክርስቲያን ሆይ! የክርስቶስ ብቻ እንጂ የሌሎች ልትሆኚ አይገባሽም። በአፍኣ ቆሞ ለሚያንኳኳውና ከአንቺ ጋር እራት ለመብላት ለሚፈልገው ለውድሽ ለክርስቶስ ደጁን ክፈቺለትና ወደ አንቺ ይግባ ማለት እንወዳለን። የቤተ ክርስቲያን አባቶችንና ደጁን ለጌታ የዘጉበትንም ሁሉ ከዘማሪ ዳዊት ጋር በመተባበር፣ “እናንት መኳንንቶች፥ በሮችን ክፈቱ፥ የዘላለም ደጆችም ይከፈቱ፥ የክብርም ንጉሥ ይግባ” እንላቸዋለን። “ይህ የክብር ንጉሥ ማን ነው?” ሲሉ ቢጠይቁን መልሳችን ይህ ነው፤ “እግዚአብሔር ነው፥ ብርቱና ኀያል፥ እግዚአብሔር ነው፥ በሰልፍ ኀያል። … የጭፍሮች አምላክ እግዚአብሔር፥ እርሱ የክብር ንጉሥ ነው።” ስለዚህ “እናንተ መኳንንቶች፥ በሮችን ክፈቱ፥ የዘላለም ደጆችም ይከፈቱ፥ የክብርም ንጉሥ ይግባ” (መዝ. 23/24፥7-10)።

(በጮራ ቍጥር 45 ላይ የቀረበ)


Sunday, August 25, 2013

ማስታወቂያ


ጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ቍጥር 45 ለንባብ በቅቷል




*   ርእሰ አንቀጽ
“ደጁ ለጌታ ይከፈት” በሚል ርእስ በቀረበው መልእክት ውስጥ ቤተ ክርስቲያን ከውስጧ አውጥታ በደጅ ያቆመችውንና “ክፈችልኝ” እያለ የሚያነኳኳውን ጌታዋን እንድታስገባው ጥሪ ያስተላልፋል፡፡ እንዲህ በማለት፦
“የክርስቶስ ሙሽራ የሆንሽ ቤተ ክርስቲያን ሆይ! የክርስቶስ ብቻ እንጂ የሌሎች ልትሆኚ አይገባሽም። በአፍኣ ቆሞ ለሚያንኳኳውና ከአንቺ ጋር እራት ለመብላት ለሚፈልገው ለውድሽ ለክርስቶስ ደጁን ክፈቺለትና ወደ አንቺ ይግባ ማለት እንወዳለን። የቤተ ክርስቲያን አባቶችንና ደጁን ለጌታ የዘጉበትንም ሁሉ ከዘማሪ ዳዊት ጋር በመተባበር፣ ‘እናንት መኳንንቶች፥ በሮችን ክፈቱ፥ የዘላለም ደጆችም ይከፈቱ፥ የክብርም ንጉሥ ይግባ’ እንላቸዋለን።”

መሠረተ እምነት
“ስለዚህ እኛ ከአሁን ጀምሮ ማንንም በሥጋ እንደሚሆን አናውቅም፤ ክርስቶስንም በሥጋ እንደ ሆነ ያወቅነው ብንሆን እንኳ፥ አሁን ግን ከእንግዲህ ወዲህ እንደዚህ አናውቀውም” (2ቆሮ. 5፥16) የሚለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል ለስሕተታቸው መሸፈኛነት በተሳሳተ መንገድ እየጠቀሱ፣ የክርስቶስን መካከለኛነት እያስተባብሉና የተዋሕዶን ትምህርት እየበረዙ ላሉ ወገኖች ትምህርተ ተዋሕዶን መሠረት ያደረገ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡

*  የዘመን ምስክር
የዚህ ዕትም የዘመን ምስክር አባ ወልደ ትንሣኤ ግዛው በኋላም ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው በተሰጣቸው ሀብተ ፈውስ እና ሀብተ ስብከት ለብዙ ምእመናን በረከት ሆነው ማለፋቸው የተዳሰሰበት ጽሑፍ ቀርቧል፡፡ “እኔ ሰው ሲፈወስ ደስ ይለኛል፤ ስለዚህ እግዚአብሔር የፈውስ ስጦታ እንዲሰጠኝ በልጅነቴ ለምኜው ነበር። እግዚአብሔርም የለመንሁትን ሰጥቶኛል። እኔም በክርስቶስ ኀይል የታመሙትን እፈውሳለሁ፥ ለወደ ፊቱም በዚሁ ሥራዬ ለመቀጠል እፈልጋለሁ” ማለታቸው ተዘግቧል፡፡

 ፍካሬ መጻሕፍት
    “ልጆችዋ ይነሣሉ፥ ምስጋናዋንም ይናገራሉ … መልካም ያደረጉ ብዙ ሴቶች አሉ፥ አንቺ ግን ከሁሉ ትበልጫለሽ።” (ምሳ. 31፥28፡29) ለሚለው ጥቅስ ዐውዳዊ ፍቺ ተሰጥቷል፡፡ ጥቅሱ በተሳሳተ አተረጓጐም ለማርያም የተሰጠበትን መንገድ በመፈተሽ ጥቅሱ ለማርያም የተነገረ አለመሆኑን ዋቢዎችን በመጥቀስ ይሞግታል፡፡

*  ታላላቅ መንፈሳውያን ቃላት
ፍቅር የተሰኘውን መንፈሳዊ ቃል የሚያብራራ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርት ቀርቧል፡፡

ሌሎችም ጽሑፎች የተካተቱበትን ጮራ መንፈሳዊ መጽሔት ቊጥር 45ን ገዝተው ቢያነቡ ትልቅ መንፈሳዊ በረከት እንደሚያገኙ ጥርጥር የለንም፡፡

Wednesday, August 21, 2013

የመዳን ትምህርት



ካለፈው የቀጠለ
ድሩም ማጉም ኢየሱስ ክርስቶስ የሆነውን ደኅንነት
ሰው እንዴት የራሱ ሊያደርገው ይችላል?

ከላይ እንዳነበብነው ይህ ቀረው የማይባለውን ሰውን የማዳን ሥራ፥ እግዚአብሔር ከፍ ባለ መለኮታዊ ጥበብ ዐቅዶት በነበረው መሠረት በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል አጠናቆታል፡፡ ዛሬ ሰውን ለማዳን የሚታቀድም ሆነ የሚደረግ አንድም ነገር አልተተወም፡፡ አሁን የሚቀር ቢኖር በሰው ደረጃ መፈጸም የሚገባው የተፈጸመውን “በእምነት መቀበል” ብቻ ነው፡፡ ከወንጌላውያን አንዱ የሆነው ዮሐንስ የእግዚአብሔርና የሰው ልጅ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ የተጠናቀቀውን የሰውን ደኅንነት በወንጌሉ ውስጥ ከፍተኛ ስፍራ በመስጠት ከጻፈ በኋላ የሰው ድርሻም ምን መሆን እንዳለበት ሳይገልጽልን አላለፈም፡፡

ወንጌላዊው፥ መዳንን የሚፈልግ ሰው ወደ ቅድስት ሀገር ይሂድና የታሪክ ቦታዎችን ይጐብኝ፤ ወይም ወርቅ ብር ይክፈልና ይግዛ፤ ወይም ሰባት ዓመት በራሱ ይቁምና ይጸልይ፤ ወይም በአንዱ በረሓ ውስጥ ገብቶ በረኃብና በጥም ራሱን ይግደል፤ ወይም …  አላለም፡፡ እንደዚህማ ባለ መንገድ የሰው ነፍስ ልትድን ብትችል ኖሮ፥ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ተለዋጭ ሆኖ ይሞት ዘንድ ባላስፈለገ ነበር፡፡ ራሱ ጌታችን ኢየሱስ ያስተማረውን መሠረት በማድረግ ወንጌላዊው ዮሐንስ በወንጌሉ ጽፎ ያስተላለፈልን ትምህርት የሚለው እንዲህ ነው፡፡

Friday, August 16, 2013

የመዳን ትምህርት





“እኔ ጐስቋላ ሰው ነኝ … ማን ያድነኛል?”
በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፡፡ (ሮሜ 7፥24-25)

ከናሁ ሠናይ 
ካለፈው የቀጠለ

ሰውን የማዳን ሥራ በጌታችን በአምላካችንና በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ተጀምሮ በራሱ በኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተጠናቀቀ ካለፈው ዕትም ያነበብነውን እናስታውሳለን፡፡ ሰውን የማዳን ሥራን ከኀጢአተኛው የሰው ዘር የተወለደ ማንኛውም ሰው ሊያከናውነው አይችል የነበረ መሆኑን፥ በመላክትም እንኳ ሊሠራ የማይችል እንደ ነበረ ካነበብነው ተረድተን እዚህ ደርሰናል፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሰው ነፍሱን ለማዳን ቤዛ የመስጠት ግዴታ ያለበትና ያላገኘ መሆኑን ሲያመለክት፥ ሰው ዓለምን ሁሉ ቢገዛ ከሚገዛው ዓለም ሁሉም ለነፍሱ ቤዛ የሚሆንለት ማግኘት ካልቻለ፥ ዓለምን በመግዛቱ ምን ተጠቀመ? አለ፡፡ ዓለም ሁሉ ሲባልም የምናውቀውንና የማናውቀውን ዓለም ሁሉ ቢገዛም፥ ከሚገዛው ዓለም ሁሉም ለነፍሱ ቤዛ የሚሆን ማግኘት ካልቻለ ገሃነመ እሳት መውረድ አልቀረለትምና፥ ሰው ዓለምን ሁሉ የራሱ የማድረጉና ያለማድረጉ ውጤት ነፍሱን በሚመለከት ልዩነት እንደሌለው አመስጥሮ አስረዳ፡፡

Saturday, July 27, 2013

መሠረተ እምነት

ከነቅዐ ጥበብ

ካለፈው የቀጠለ

ማስገንዘቢያ፡- ሥላሴን በመካድ ከሰባልዮሳውያን ቀጥሎ የሚታወቁት አርዮሳውያን፣ እግዚአብሔር በማለት በግእዝና በዐማርኛ የሚጠራው መለኮታዊ ስም እንደ ዕብራይስጡ፣ “ይሆዋ ወይም ያህዌ” መባል አለበት የሚል አቋም በመያዝ ስለ ተነሡ በዚህ ስም አንተርሰውና አስታክከው የሚነዙትን ሐሰተኛ ትምህርት ከመሠረቱ ጀምሮ ለማፈራረስ ሲባል በዚህ ርእስ በሚቀርበው መሠረታዊ የክርስትና ትምህርት “ይሆዋ ወይም ያህዌ” የሚለውን ቃል መጠቀም የቃላት መደናገርን ያስወግዳል ተብሎ ታምኖበታል፡፡

“ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናና ዛሬ፥ ለዘላለምም ያው ነው፡፡ እስመ ኢየሱስ ክርስቶስ ውእቱ ዘትማልም፥ ወዮም ውእቱ፥ ወእስከ ለዓለም፡፡” ሲል የሚያስተምረው መጽሐፍ ቅዱስ ነው ዕብ. 13፥8፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ መተርጉማንም “ትናንት” የሚለው ቃል በሁለት ክፍል ሊታዩ የሚገባቸውን የወቅት ምዕራፎችን ያሳስበናል ይላሉ፡፡ ሲተነትኑትም፡-
አንደኛ፥ ዓለም ከመፈጠሩ፣ ዘመንም ከመቈጠሩ አስቀድሞ የነበረውንና የጊዜ መነሻ ያልነበረውን የወልድን የአኗኗር ብሉየ መዋዕልነት፥ (የዕድሜ ባለጸጋነቱን) ያመለክታል ይላሉ፡፡

Thursday, July 11, 2013

ክርስትና በኢትዮጵያ



የእግዚአብሔር መንግሥት ታሪክ

ካለፈው የቀጠለ

ሦስተኛ፥ የመሰብሰቢያ ሕንጻ ማሠራቱ

ታላቁ ሐዋርያችን ፍሬምናጦስ በእርሱ ስብከት መነሻ በጌታ ያመኑትን በአንድ መንፈሳዊ ጉባኤ (ቤተ ክርስቲያን) አሰባሰበ፡፡ ማኅበረ ጽዮን ሰማያዊት ተብላ ለተሠየመችው ማኅበረ ምእመናን አመራር ሰጪ አካል የሆነ ድርጅት አቋቋመ፡፡ ለድርጅቱ ሥራ መንፈሳውያን አገልጋዮችን መርጦ በመሾም ማኅበሩን አጠናከረ፡፡ ይህን ሁሉ እያሟላ ካደራጀ በኋላ ፊቱን የመለሰው ለመሰብሰቢያና ለጽሕፈት ቤት የሚሆን ሕንጻ ወደ ማሠራት ነበር፡፡ ክርስትና ከሐዋርያት ዘመን ጀምሮ ከተሰበከባት ከግሪክ የመጣ እንደ መሆኑ መጠን፣ ሕንጻው የት ይሠራ ለሚለው ጥያቄ ፍሬምናጦስ መልስ ነበረው፡፡ ቀደም ብሎ ይሠራበት የነበረውን ትውፊት መሠረት በማድረግ የማኅበረ ጽዮን ሰማያዊት አስተዳደር ማእከልን በአክሱም መመሥረት ነበረበት፡፡

ስለዚህ ለሚጠፉት ሞኝነት፣ ለሚድኑት ግን የእግዚአብሔር ኀይል የሆነው የክርስቶስ የመስቀሉ ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ በተሰበከባትና ፍሬ ባፈራባት በመዲናዋ በአክሱም ለማኅበሩ በማእከልነት የሚያገለግለው ሕንጻ እንዲሠራ ተወሰነ፡፡ እንደዚህ ላለው ጕዳይ በምርጫው ብቸኛ ሆኖ የሚቀርበው በአንድ ሀገር ወይም አውራጃ ለመጀመሪያ ጊዜ “መስቀል የተተከለበት ነው” ተብሎ ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው ታሪካዊ ስፍራ ለወንጌል ሥርጭትና ለምእመናን መንፈሳዊ አስተዳደር ማእከል በመሆን እንዲያገለግል ይደረጋል ማለት ነው፡፡

Tuesday, June 25, 2013

ክርስትና በኢትዮጵያ



 የእግዚአብሔር መንግሥት ታሪክ

ከነቅዐ ጥበብ
ካለፈው ቀጠለ

በፍሬምናጦስ አገልግሎት ክርስትና በኢትዮጵያ ፍሬ ማፍራት ጀምሮ እንደ ነበረ ባለፈው ዕትም አንብበን ነበር፡፡ በአዳኝነቱ ኢየሱስ፥ ሰውንና እግዚአብሔርን በአንድ አካል በማገናኘቱና ለፍጹምና ዘላቂ ኅብረት በማብቃቱ ዐማኑኤል፤ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል በተመሠረተ ኅብረት ላይ ለሚከናወነው የንጉሥነት፣ የነቢይነትና የክህነት አገልግሎት በመሠየሙ ክርስቶስ የተባለው፥ የእግዚአብሔርና የሰው ልጅ የሆነው የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ወንጌል በተሰበከባት በሳባ ኢትዮጵያ መዲና በአክሱም ከተማ “ጽዮን” ወይም “ማኅበረ ጽዮን ሰማያዊት” የተባለችው ቤተ ክርስቲያን (ማኅበረ ምእመናን) ተቋቁማ እንደ ነበረ ተመልክቶ የነበረውን እናስታውሳለን፡፡

ቤተ ክርስቲያን የሚለው ቃልም በዕብራ ይስጡ ኳሃል፥ በግሪክኛው አቅሌስያ ምስጢርና ዘይቤ ሲፈታ ጉባኤ ምእመናንን እንደሚያመለክት ተገልጾ ነበር፡፡ በዚህም መሠረት ከሁለት ቍጥር ጀምሮ ብዛት ያላቸውን ያቀፈ፥ ከዚያም በላይ በመላው ዓለም የነበሩትን፣ ያሉትንና ገናም የሚኖሩት በክርስቶስ ደም የተዋጁትን ምእመናን ሁሉ ያቀፈች ለክርስቶስ አካልነት፣ ለክርስቶስ ሙሽሪትነት፣ በእግዚአብሔር ጸጋ የበቃችውን የቦታ ክልል የማይጋርዳትን፣ ከጾታ፣ ከዕድሜ፣ ከወገን ሁሉ የተጠራችውንና የተመረጠችውን አንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንደሚገልጽ አንብበን የነበረውን እናስታውሳለን፡፡

Sunday, June 16, 2013

የዘመን ምስክር

በዚህ ዐምድ ለቤተ ክርስቲያን መሻሻልና መለወጥ የተጋደሉ፥ ለአገርና ለወገን የሚጠቅም መልካም ሥራን የሠሩ አበውን ሕይወትና የተጋድሎ ታሪክ አሁን ላለውና ለቀጣዩ ትውልድ አርኣያ እንዲሆን እናስተዋውቃለን፡፡


ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ቀዳማዊ የወንጌል እስረኛ (1888 - 1974 ዓ.ም.)
በዘመናት ውስጥ የተፈጸመና ታሪክ የመዘገበው መልካምም ሆነ ክፉ ሥራ ሊረሳ አይችልም፡፡ ለጊዜው እውነት እንደ ሐሰት ይቈጠር$ ሐሰት ደግሞ የእውነትን ስፍራ ይቀማ ይሆናል፡፡ በደካሞች ግምትም እውነት ርቆ ሊቀበርና የሐሰት ዐፈር ሊጫነው ይችላል፡፡ እውነት ግን ለጊዜው እንጂ ተቀብሮ ሊቀር፥ ፈጽሞ ሊሰወርና ሊረሳ አይችልም፡፡ እውነት ሲወጣ ቀድሞ ተሰጥቶት የነበረው ዝቀተኛ ግምት ይለወጣል፡፡ በተቃራኒው ሐሰትም ከተሰቀለበት የክብር ማማ ላይ ይወርዳል፡፡ የብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የተጋድሎ ታሪክ ከተቀበረበት መውጣቱና ተገቢውን ስፍራ ማግኘቱ እውነትና እውነተኞች ተቀብረው እንደማይቀሩ ያሳያል፡፡    

የባለ ታሪኩ ማንነት
የተወለደው በ1888 ዓ.ም. በቀድሞው የኤርትራ ጠቅላይ ግዛት በሐማሴን አውራጃ፣ በላምዛ ሠሓርቲ ወረዳ፣ ዓዲ ቀሺ በተባለው ስፍራ ነው፡፡ ገብረ አብ ይባላል፡፡ የመጀመሪያ ደረጃ የቤተ ክህነት ትምህርቱን ተምሮ ወደ ትግራይ በመሄድ፥ በዓድዋ አውራጃ ዓዲ አቡን ከነበሩት ግብጻዊ ጳጳስ ከአቡነ ቄርሎስ ዲቁና ተቀበለ፡፡ ከዚያ ኤርትራ ውስጥ በሚገኘው አቡነ እንድርያስ ሠፍኣ ገዳም ገብቶ የግእዝን ትምህርት፣ የአበውን ግብረ ገብና ሥርዐተ ገዳምን እየተማረና እያገለገለ ዐምስት ዓመታትን ካሳለፈ በኋላ መነኰሰ፡፡

አባ ገብረ አብ የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍትን ምስጢር ለመረዳት ጽኑ ፍላጎት ነበራቸው፡፡ ወደዚያው ለመድረስም ቅኔን ከነአገባቡ ተምረዋል፡፡ ፀዋትወ ዜማንና መዝገብ ቅዳሴንም በሚገባ የተማሩ ሲሆን በቅዳሴ መምህርነት ተመርቀዋል፡፡ በ1911 ዓ.ም. ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ከግብጻዊው ሊቀ ጳጳስ ከአቡነ ማቴዎስ የቅስናን ማዕርግ ተቀበሉ፡፡ ወዲያው በቀድሞው የሐረር ጠቅላይ ግዛት የሚገኘውንና በግራኝ ጊዜ የጠፋውን የአሰቦት ደብረ ወገግ ገዳም እንዲያቀኑ ተላኩ፡፡

መጽሐፍ “በእግዚአብሔር ደስ ይበልህ የልብህንም መሻት ይሰጥሃል” (መዝ. 36(37)፥4) እንደሚል፥ ከእርሳቸው ስምንት ቀን ያህል ቀድመው ወደ ቦታው ከመጡና አለቃ ገብረ መድኅን ከተባሉ የሐዲሳትና የሃይማኖተ አበው መምህር ጋር ተገናኙ፡፡ ይህም ሐዲሳትን ለመማር የነበራቸውን ጽኑ ፋላጎት ለማርካት የተፈጠረ ትልቅ ዕድል በመሆኑ፥ ከእርሳቸው ጉባኤ ሐዲሳትን እየቀጸሉ ጥቂት እንደ ቈዩ፥ በእኒሁ መምህር ምክንያት ወደ ኢየሩሳሌም የሚሄዱበት በር ተከፈተላቸው፡፡

Thursday, June 6, 2013

ርእሰ አንቀጽ


እግዚአብሔር አይዘበትበትም

ገበሬ በመኸር ሊሰበስብ የሚችለው ያንኑ የዘራውን ዐይነት አትርፎና አትረፍርፎ እንደ ሆነ ለማስገንዘብ፥ ያልዘራነውን እንሰበስባለን ብላችሁ በእግዚአብሔር አትቀልዱ፤ እግዚአብሔር ሊዘበትበት አይገባም ሲል የእግዚአብሔር መንፈስ በሐዋርያ ጳውሎስ በኩል አስተማረ (ገላ. 6፥7-9)፡፡ እየበቀለና እያደገ ለአዝመራ ደርሶ የምናጭደውና በትርፍ የምንሰበስበው ያንኑ የዘራነውን የእህል ዐይነት ነው፡፡ ጓያ የዘራ የስንዴ ምርት፥ ባቄላ የዘራም የጤፍ ምርት እግዚአብሔር ይሰጠኛል ብሎ አይጠብቅ፡፡ ነገ እንዲያገኝ የሚፈልገውን የምርት ዐይነት ካወቀ ለዚያ አዝመራ የሚያበቃውን ዘር ዛሬ መዝራት አለበት፡፡ ሌሎች ሰዎችም ሊያገኙ የማይችሉትን እንደሚያገኙ አስመስሎ ኢ ሕጋዊ ባልሆነ መንገድ እንዲደክሙ መምራት ለሁሉም እንደየሥራው የሚከፍል እግዚአብሔር ጻድቅ ፈራጅ የሆነበትን የቅድስናውን ባሕርይ የለወጠ አስመስሎ ማስተማር ነውና በእግዚአብሔር አንቀልድ፡፡ ይህ ዐይነቱ ተልእኮ መጥፎ ምርት ለመሰብሰብ የሚያበቃ መጥፎ ዘር መዝራት ነውና፡፡ ምድራዊ ዳኛ እንኳ ጸያፍና ነውር የሚለው፥ እንዲያውም የሚያፍርበት አድልዎኛነትና ፍርድን ማዛባት በእግዚአብሔር ዙፋናዊ ችሎት ይሠራበታል ከማለት የበለጠ ድፍረት ከቶ የለም፡፡ ስለዚህ በምኞታችንና በንግግራችን እውነቱን እውነት፥ ሐሰቱንም ሐሰት ነው እንበል፡፡ ይህን አለማለት በሰይጣን ጐራ መሰለፍ ነውና (ማቴ. 5፥37)፡፡

በአለቃ ስም ከሚነገሩ ቀልዶች መካከል አንዱን እዚህ ብንጠቅስ ተገቢ ስፍራው ይመስለናል፡፡ በርኩሳን መናፍስት አገልጋይነቱ ሰዎችን ሲያሳስት የኖረ ሰው ሞተ፡፡ ሥራውንና የደለበ ሀብቱን ቤተ ሰቡ ወረሰ፡፡ ወራሾቹም የኀጢአት ስርየት ይገዙለት ዘንድ ከዕለተ ሞቱ ጀምሮ በዐርባው፥ ከዚያም በኋላ በሰማኒያው፥ በመንፈቁና በየዓመቱ በከፍተኛ የገንዘብ ወጪ ጸሎተ ፍትሐት አስደረጉለት፡፡ ከዐርባው ድግስ ተቋዳሾች መካከል አንዱ አለቃ ስለ ነበሩ፥ በአጠገባቸው ተቀምጦ ይመገብ የነበረ ሌላው አለቃን ጠየቃቸው፡፡ “ሟቹ ንስሓ አልገባም፤ ወራሾቹ ሀብቱን ወርሰዋል፤ ሥራውንም ቀጥለዋል፤ አሁን እኛ የጸሎታችን ዋጋ የሆነውን ድግስ የምንመገበው ለሟቹ ነፍስ ስርየት አሰጥተናል፤ ርግጠኞች ነን ብለን ነውን? ርግጠኛ ባልሆነ የስርየት ሽያጭስ አንጠየቅምን? ቢላቸው፤
“እኛ እንብላ እያልን ማራት ማራት፤
አምላክ ከፈለገ ገነት ይጨምራት፤
ካልፈለገም ደግሞ እንጦርጦስ(ሲዖል) ያውርዳት፡፡” በማለት መለሱለት ይባላል፡፡ በእውነት እንዲህ ተብሎ ከሆነ ኀላፊነት ከማይሰማው ኅሊና የመነጨ አነጋገር ነው፤ አያሥቅም፡፡

Friday, May 17, 2013

አለቃ ነቅዐ ጥበብ

ካለፈው የቀጠለ

በምን ተስኖት ቤት ዐድረው ከወጡት ሰዎች መካከል በሌላ አቅጣጫ የሄዱትም እንደዚሁ በተመሳሳይና በሌሎች የወቅቱ ሁኔታ በፈጠራቸው ነጥቦች ላይ ይከራከሩ ነበር፡፡ ሐሳባቸውን በውይይት እያጠነከሩና እየተስማሙ መጥተው በመጨረሻ በአንዳንድ ነጥብ ላይ ለመግባባት አልቻሉም፡፡ ከብዙ ውይይት በኋላ ያስቸገሯቸውንና አልታረቅ ያሏቸውን ነጥቦች በሚከተለው ሁኔታ አጠቃለሏቸው፡፡

 1. ምን ተስኖት በሰይጣን መንፈስ እንደሚሠራ እናውቃን፤ ከጥንቈላ፣ ከሟርት፣ ከአስማተኛነት ጋር የእግዚአብሔር መንፈስ ግንኙነት የለውምና፥ ለእግዚአብሔር ብቻ ሊቀርብ የሚገባውን ክብር፣ አምልኮት፣ ስግደትና ዝማሬ የሚቀበለው በምን ተስኖት ያደረ ራሱን የእግዚአብሔር ተገዳዳሪ ያደረገው ሰይጣን ነው፡፡ ታዲያ ሰይጣን በምን ተስኖት ቤት ሲመለክ የሚያድርበትን ዕለት በየወሩ ለሚካኤልና ለገብርኤል መታሰቢያ በሚከበሩ በዓላት ለምን አደረገው?

Friday, May 10, 2013

አለቃ ነቅዐ ጥበብ


ጭውውት
አለቃ ነቅዐ ጥበብና ቤተሰባቸው

የተደበላለቀ የአነስተኛ ከበሮዎች ድምድምታና ዝየራ የሌሊቱን ጸጥታ ተዳፍሮታል፡፡ ዐልፎ ዐልፎ እልልታ የተቀላቀለበት ያላቋረጠ ጭብጨባ ከበሮውን አጅቦታል፡፡ በመደብ፣ በዕድሜ፣ በጾታ፣ በጐሣ፣ በሥራና በዕውቀት ደረጃም የተሰባቀለ ሕዝብ ወደ አዳራሹ ራስጌ ከመጋራጃው ውጪ የቆመ አስተናባሪ አደግድጎ ሥርዐተ ማሕሌቱን ይመራል፡፡ በቅልጥፍናቸውና ከሰው ጋር በሚያደርጉት ፈጣን ትውውቅ የሚደነቁ፣ ነገር ግን ገራገር ያገር ቤት ሰው የሚመስሉ ወጣቶች በየባለጕዳዩ መካከል ተቀምጠዋል፡፡ እነርሱም በዜማውና በጫጫታው መካከል በየአጠገባቸው ላለ ባለጉዳይ ለመምጣት ምክንያት የሆነውን ችግራቸውን እያስተዛዘኑ በለሆሳስ (በሹክሹክታ) ያወሩለትና በለውጡ የእርሱን ጕዳይ ያደምጣሉ፡፡

ከጉባኤው መካከል አንዳንዱ ሰው በዝየራው፣ በእልልታው፣ በከበሮውና በጭብጨባው ውስጥ በአጠገቡ ወደሚገኘው ሰው ጆሮ በመጠጋት የአቶ ምንተስኖትን ታሪክ ሹክ ይለዋል፡፡ ከሚወራው ታሪክ አብዛኛው መቼ? የት? ለማን? እንደ ተደረገ የማይታወቅ፣ እንዲያው በይለፍ ይለፍ እየተናፈሰና እየተጋነነ የሚወራ ነው፡፡ ማንም ሰው ልብ ያላለው የኪስ ያይደለ የልብ ዳበሳም እየተቀላጠፈ ነበር፡፡ እነዚያ ልብሰ አዳፋ ንግግረ ጐልዳፋ ያገር ቤት ሰው የሚመስሉት ወጣቶች አሁንም ስፍራቸውን እየለዋወጡ በየሰው መካከል ገብቶ መቀመጥን እንደ ተያያዙት ነበር፡፡ የራሳቸውን ጕዳይ በመጫወት የሌላውን ጠይቆ በማውጣጣት በዕሴት ያልተመጣጠነ ልውውጥ ያካሂዳሉ፡፡ በልዋጭ ከሚያጠናቅሩት ዘገባ ዋናው ያባለጕዳዩን ስምና የመጣበትን ችግር ማወቅን ነበር፡፡ የዝየራው፣ የእልልታው፣ የከበሮውና የጭብጨባው ድምፆች ተደበላልቀው በአየር ላይ እኔ-እበልጥ እኔ-እበልጥን ለማስወሰን ፍልሚያ እያካሄዱ የሚመስልበት ውድቀቱ ሌሊት የተደፈረውን መብቱን ለማስከበር አቤቱታውን እያቀረበ ነበር፡፡

Sunday, April 21, 2013

የመዳን ትምህርት



ካለፈው የቀጠለ
የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወት

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመፀነስና በመወለድ ኀጢአተኛ ባሕርይን ስላልወረሰ ከሰይጣን ቍራኛነት ነጻ ነበረ፡፡ ሁሉን እንዲገዙ ሥልጣን ተሰጥቷቸው የነበሩት አዳምና ሔዋን ሁሉን ከሚያስገዛው ሥልጣናቸው ጋር ለሰይጣን በማደራቸው ምክንያት ሰይጣን የእነርሱን የገዥነት ሥልጣን እንዲወርስና የዚህ ዓለም ገዥ፥ የዚህ ዓለም አምላክ እንዲሆንና እንዲባል አበቁት (ዮሐ. 12፥31፤ 16፥11፤ 2ቆሮ. 4፥4)፡፡ ምድርንና ከእርሷ ሥርዐተ ተፈጥሮ ጋር የተያያዘውን ሁሉ ለመግዛት ከተሰጣቸው ሥልጣን ጋር በሰይጣን ገዥነት ሥር በወደቁት በእነዚህ ወላጆቻችን ምክንያት ሰይጣን ምንም የዚህ ዓለም ገዥ ወይም አምላክ ቢባልም በዚህ ዓለም ውስጥ ከአዳምና ከሔዋን ዘር ተወልዶ ሳለ፥ ኀጢአተኛ ባሕርይን በመንፈስ ቅዱስ አሠራሩ ለይቶ በመተውና ባለመውረሱ ምክንያት ብቻ ሰይጣን በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ አለኝ የሚለው የሥልጣን ጥያቄ አልነበረም (ዮሐ. 14፥30)

ኀጢአተኛ ባሕርይን ሳይወርስ ከድንግል ማርያም ተወልዶ ፍጹም ሰው የሆነው ቃል (ሥግው ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ) በልደት ፍጹም ቅዱስ እንደ ሆነ ሁሉ በኑሮውም ሁሉ በሰውና በአባቱ ፊት ፍጹም ቅዱስ ነበረ (ሉቃ. 2፥40-52)፡፡ በጠላትነት የተነሡበት ሁሉ እንኳ እርሱን የሚከሱበት ምክንያት ስሕተት አላገኙበትም (ሉቃ. 23፥13-17፤ ዮሐ. 8፥46፤ 18፥38፤ 19፥4-6)፡፡ በቃሉም ፍጹም ቅዱስ እንደ ነበረ የእግዚአብሔር ቃል ይመሰክራል (ኢሳ. 53፥9፤ 1ጴጥ. 2፥22-23)፡፡

Thursday, April 11, 2013

የመዳን ትምህርት



ከናሁ ሠናይ
ካለፈው የቀጠለ

በኀጢአት ውስጥ የተዘፈቀውን የሰውን ዝርያ ከኀጢአቱና ኀጢአቱ ካመጣበት ፍርድ ለማዳን፥ ለመቀደስና ዓለም ሳይፈጠር ታቅዶለት ወደ ነበረው የክብር ስፍራ ለመመለስ (ማቴ. 25፥34) እግዚአብሔር የተጠቀመበት መንገድ

1.     ጻድቅና ቅዱስ አፍቃሪም በሆነው በአምላካችን ዙፋናዊ ችሎት ኀጢአትን ለመቅጣት ተገቢ የሆነው ፍርድ እንዲፈጸም፡፡
2.    ከምድር ዐፈር ለተሠራው ሰው ለሥጋና ለደሙ ብቻ ሳይሆን ከእግዚአብሔር እስትንፋስ ለመጣች ሕያዊት ነፍሱ በዕሴት የተመጣጠነ ልዋጭ (ቤዛ) መስጠት ተገቢ ሆኖ እንደ ተገኘ ባለፈው ጮራ ቍጥር 5 በዚሁ ርእስ ስር ገልጠን የነበረ መሆኑን አንባቢ ያስታውሳል፡፡

ከዚህ በማያያዝም ከእግዚአብሔር በታደለው የመዓርገ ተፈጥሮ ከፍተኛነት የተነሣ
ሀ. ከዓለምና በውስጡ ካሉት የሀብት ክምችቶች ሁሉ፥
ለ. በሥጋና በደም ከሚንቀሳቀሱ እንስሳት፥ አራዊት፥ አዕዋፍ፤ በባሕርም ከሚርመሰመሱ ፍጥረታት ሁሉ፥
ሐ. መናፍስት ሆነው ከተፈጠሩት ሠራዊተ መላእክት ሁሉ ለሰው በዕሴት የተመጣጠነ ተውላጥ (ቤዛ) እንዳልተገኘለት፤ ነገር ግን ሰው ለሆነው ወልደ እግዚአብሔር (ሥግው ቃል) ብቻ ይህ ጕዳይ የሚቻልና የሚገባም ሆኖ እንደ ተገኘ (ራእ. 5፥1-14) በዚያው ክፍል መቅረቡ ይታወቃል፡፡