Monday, June 8, 2015

መሠረተ እምነት

ኢየሱስ ክርስቶስ የዐዲስ ኪዳን መካከለኛ
ክርስቶስ እርሱን ወክለው የሚያገለግሉ ካህናትን ሾሟልን?
ከነቅዐ ጥበብ
ባለፈው ዕትም በዚሁ ዐምድ ላይ በወጣው ጽሑፍ ውስጥ ከተነሡት ነጥቦች መካከል አንዱ፥ “ክርስቶስን የሚተካ ሌላ መካከለኛ አለን?” የሚል ነበር (ገጽ 6)። መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርገንና የአበውን ምስክርነት ጠቅሰን ክርስቶስን የሚተካ ሌላ መካከለኛ እንደሌለ ለማሳየት ሞክረናል። ቀደም ብለንም የክርስቶስን መካከለኛነት በሌሎች መካከለኞች የተኩ ወገኖች፥ መካከለኞቻቸው ያደረጓቸው ያንቀላፉ ቅዱሳንንና ቅዱሳን መላእክትን መሆኑን ተመልክተናል። የክርስቶስን መካከለኛነት ባንቀላፉ ቅዱሳን ብቻ ሳይሆን በሕይወት ባሉ “ካህናትየተኩበትም ሁኔታ አለ። ይኸውም የክርስቶስ ክህነት በውክልና ለሐዋርያት እንደ ተሰጠና “ሐዋርያትም የእርሱን መሥዋዕት በማቅረብ የእርሱን የክህነት ሥልጣን ወክሎ በመሥራት የማዳን ጸጋውን ለብዙዎች እንዳዳረሱ፥ “ይህንን ሥራ በመቀጠል ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ከመስበክ ጋር ሲወርድ ሲዋረድ በመጣላት የክርስቶስ የክህነት ሥልጣን መሠረት የምስጢራተ ቤተ ክርስቲያንን ጸጋ በክርስቶስ ስም ላመኑት ሁሉ ለማዳረስ ትጥራለች።” በማለት ይህንና ይህን የመሰለ መጽሐፍ ቅዱስ ከሚያስተምረው ውጪ የሆነ ትምህርት ያስተላልፋሉ (ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ምግባር፣ ከሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ፣ 1996፣ 233)።

ይኸው መጽሐፍ “ሥልጣነ ክህነት ለተመረጡት ብቻ ይሰጣል” በሚል ንኡስ ርእስ ሥር ያሰፈረው ሐተታ እንዲህ ብሏል። እንደ ብሉይ ኪዳን ሁሉ፥ “በዐዲስ ኪዳንም ሥልጣነ ክህነት ለተመረጡት ብቻ እንጂ ለአማኞች ሁሉ እንደማይሰጥና ለተመረጡት ብቻ እንጂ አማኞች ለሆኑት ሁሉ ለወንዶችም ለሴቶችም አይሰጥም። እንዲያማ ካልሆነ ክርስቶስ ከብዙዎች መካከል ለምን ዐሥራ ሁለቱን ከዚያም ሰባውን ደቀ መዛሙርት ብቻ መረጠ? ሐዋርያው ጳውሎስም የክህነት ሹመት ከመሰጠቱ በፊት በጥንቃቄ እንዲሆን በማሰብ መልካም ጠባያቸውንና አኗኗራቸውን በማስመልከት መመረጥና መሾም ስለሚገባቸው ካህናት መመሪያ አዘጋጅቷል (1ኛ ጢሞ. 3፥1-13፤ ቲቶ 1፥6-9)። በዚህም ምክንያት ፈጥኖ እጆቹን በመጫን ካህናትን እንዳይሾም ጢሞቴዎስን አስጠንቅቆታል (1ኛ ጢሞ. 5፥22)” (ገጽ 260፡261)። በዚህ ዕትም በጒዳዩ ላይ አተኲረን የክርስቶስን ብቸኛ መካከለኛነት እናስረዳለን።