Monday, February 16, 2015

ርእሰ አንቀጽ

ያንን ነቢይ የማትሰማ ነፍስ ትጠፋለች

በዘመናት ውስጥ ራሱን ያለ ምስክር ያልተወ እግዚአብሔር ለአባቶቻችን በቀድሞ ዘመን በተለያየ የመገለጽ ስልት በተለያየም ጐዳና ተናገረ ይላል የዕብራውያን መልእክት ጸሓፊ፡፡ በየዘመኑ በምሳሌ፥ በሕግ፥ በክህነት፥ በመሥዋዕት፥ በመቅደስ፥ በትንቢት፥ በተስፋ ቃል ተናግሮ ነበር፡፡ በአባቶች፥ በመሳፍንት፥ በነገሥታት፥ በካህናት፥ በነቢያት በኩል ተናግሮ ነበር፡፡ ተናግሮት የነበረውም ሁሉ ሊፈጸም ከነበረው ዕቅዱ አንዲት የውጣ እንደማትወድቅ የሚያመለክት ጥላ ነበር፡፡ ከጥላው በስተኋላ ሊገለጥ ያለው አካል ባይኖር ኖሮ ለጥላው መገለጥ ስፍራ ባልተገኘ ነበር፡፡ ስለዚህ ጥላውን ያስገኘ የአካሉ መኖር ነበር ማለት ነው፡፡

ከበስተኋላ እየመጣና እየቀረበ ላለው የአካል መገለጥ ግምት ያልሰጠ ሞኝ ወይም እብሪተኛ ሰው ይኖርን? ጥላውን እንደ አካል ቈጥሮና በጥላ ፍጹምነት አለ ብሎ የረካ ሰውስ ይገኛልን? ሆኖም ጥላው ከበስተኋላ አካል እንዳለው በመረዳት አካሉን የጠበቁ ሁሉ ብፁዓን የሚያሰኛቸውን ርካታ እንደሚያገኙ አይጠረጠርም፡፡